Saturday, September 6, 2025

እይታ | Perception

                                                    ስሜታዊነት እና እምነት

    እምነት በስሜት አይገነባም ። እምነት ሲሞቀን የምንገነባው ፣ ሲበርደን ደግሞ የምናፈርሰው ወረት አይደለም ። ስናገኝም ስናጣ ፣ ቢደላንም ባይደላንም ፣ በክፉም ሆነ በበጎ ሁኔታ ውስጥ ይዘን የምንገኘው ማንነት ነው ። ድህነትም ባለጸግነትም ፣ መሀይምነትም ምሁርነትም እምነትን አያስጥልም ። እምነት በፈተና ብዛትም አይፈርስም ። እንዲያውም ፈተና እምነት የሚጠነክርበት ወጌሻ ነው ። ስሜታዊነት የእምነት ተቃራኒ ነው ። ስሜታዊ ሰዎች ሲያገኙ ሌላ ፣ ሲያጡ ደግሞ ሌላ ሰው ናቸው ። ሲያተርፉ አመስጋኝ ሲከስሩ ወቃሽ ናቸው ። ሲሞላ እብሪተኛ ሲጎድል ደግሞ ትሁት ናቸው ። ስሜታዊ ሰዎች ሲደሰቱ ይሆናል ፣ ሲያዝኑ ደግሞ አይሆንም ማለት ይቀናቸዋል ። እምነት ግን በሀዘንም ሆነ በደስታ ይሆናል ማለት ነው ። ስሜታዊነት መለወጥ ሳይሆን መለዋወጥ ነው ። እምነት በሂደት አንድ ጊዜ ሊለወጥ ይችላል ። በአንድ ቀን ግን ሺ ጊዜ አይለዋወጥም ። ስሜታዊነት በአንድ ጀምበር ብዙ ጊዜ መለዋወጥ ነው ። በአንድ ቀን ውስጥ ሶስት ወይም አራት ሰው መሆን ነው ። በአንድ አካል ውስጥ ብዙ ሰው መሸከም ነው ። ጥዋት እና ማታ ፣ ቀንና ጨለማ ሲፈራረቁ አብሮ መፈራረቅ ነው ስሜታዊነት ። ስሜታዊ ሰዎች በአጭሩ እምነት የለሽ ናቸው ማለት ይቻላል ።

    እምነት ሙሉነት ነው ። የሚያምን ሰው ልበ ሙሉ ነው ። በወዳጅም በጠላትም ፊት ያው ነው ። ለጠላት ፈርቶ የሚቀይረው ነገር አይኖርም ። ለወዳጅ አዝኖ የሚለውጠው ነገር የለም ። ምክንያቱም እምነት እውቀት ላይ ነው የሚመሰረተው ። እውቀት ደግሞ እውነት ላይ ነው የሚመሰረተው ። ስለዚህ በእምነት መኖር ለማንም ሳይሆን ለእውነት መወገን ነው ። እውነት ሁል ጊዜም እውነት ነው ። በጊዜ መቀየር ውስጥ አብሮ አይቀየርም ። ጥዋት እውነት የነበረው ከሰአት ውሸት አይሆንም ። ትላንት እውነት የነበረው ነገ ውሸት አይሆንም ። በዘመን ብዛት እውነት አያረጅም ። ከዚህ በተቃራኒ ስሜታዊነት ባዶነት ነው ። ነፋስ ወደ ፈለገው አቅጣጫ  እንደሚወስደው ባዶ ፈስታል መሆን ነው ። በስሜታዊነት ውስጥ ይዞ መልቀቅ እንጅ ይዞ መጽናት የለም ። ለቆ መያዝ ፣ ይዞ መልቀቅ የተለመደ ነው ። በአንዴ ሙሉ መሆን ፣ ከዚያ ደግሞ ወዲያው ባዶ መሆን የሜታዊነት ውጤት ነው ። በጣም የሚያሳዝነው ስሜታዊ ሰዎች ፣ መርጦ መያዝም ሆነ መልቀቅ አይችሉም ። ሲይዙም ሲለቁም ሳይመርጡ ነው ። ወይ ባዶ አልያም ሙሉ የሚሆኑትም ለዚያ ነው ። ስለዚህ በአግባቡ መቀበልም ሆነ መስጠት አይችሉም ። 

    ስሜታዊ ሰዎች ዘመድ ሲያዩ ሙሉ ይሆናሉ ። ባዳ መሀል ሲገኙ ባዶ ይሆናሉ ። ሲያገኙ ልባቸውን ያሳብጣሉ ። ሲያጡ ደግሞ ይጎብጣሉ ። በሰው መተማመን ይችላሉ ፣ በራሳቸው መተማመን ግን አይችሉም ። አይደለም የማይችሉትን የሚችሉትን መስራት ይፈራሉ ። ሰዎች በእነርሱ ችሎታ እያመኑ ፣ እነርሱ ግን ያላቸውን ችሎታ አምነው አይቀበሉም ። ሁል ጊዜም ውጪያዊ ማረጋገጫ ( external validation ) ይፈልጋሉ ። በራስ ሞራል ሳይሆን በሰው ሞራል መስራት ይወዳሉ ። የሚያሞግስ ሲኖር ወዲያው ይሞቃሉ ። ሲወቀሱ በቅጽበት ቅዝቅዝ ይላሉ ። ሲደነቁ በፍጥነት ይሮጣሉ ። ሲተቹ ደግሞ ለመራመድ ይዘገያሉ ። ጥንቸል የነበሩት ኤሊ ይሆናሉ ። ስሜታዊ ሰዎች ፎርጅድ ባትሪ ናቸው ። ቻርጅ ሲደረግ ወዲያው የሚሞላ ፣ ሲነቀል ደግሞ ዜሮ የሚሆን የደከመ ባትሪ ናቸው ። ወለል ብሎ የተከፈተ ወይም ጥርቅም ብሎ የተዘጋ በራፍንም ይመስላሉ ። ልባቸውን ገርበብ ማድረግ አይችሉም ። የመጣውን ነገር ወይ በሙሉ ይቀበሉታል አልያም ምኑንም አይቀበሉትም ። በእምነት መኖር ግን ልብን ገርበብ ማድረግ ነው ። መርጦ መቀበል እና መጣል ነው ። እንደፍላሽ የሚጫነውን ሁሉ መቀበል ሳይሆን ፣ እንደወንፊት እያጣሩ መውሰድ ነው ። ጉድለትን እየሞሉ መሄድ እንጅ በአንዴ ሙሉ ወይም ባዶ መሆን አይደለም ። 

    እምነት ሚዛናዊነት ነው ። እምነት ውስጥ እውነትነት አለ ። እውነትነት ውስጥ ደግሞ ሚዛናዊነት አለ ። በእምነት መኖር ፍትሀዊ ያደርጋል ። ምክንያቱም ሰው በእምነት ሲኖር በአጀብም ብዛት ሆነ ፣ በወጀብም ፍርሀት ከእውነት አይሸሽም ። በአጀብ ብዛት ጽንፍ አይዝም ። በወጀብ ፍርሀት ጥግ አይዝም ። መሀል ላይ እውነትን ይዞ ነው የሚገኘው ። እውነት ደግሞ ከምንም በላይ ወሳኝ ሚዛን ነው ። ያለ እውነት ሚዛናዊ ያለ እምነት ፍትሀዊ መሆን ከባድ ነው ። ከዚህ በተቃራኒ ስሜታዊነት ኢ-ሚዛናዊነት ነው ። ስሜታዊ ሰዎች አጀብ ሲበዛ እውነቱን ሳያጣሩ ጽንፍ ይይዛሉ ። ወጀብ ሲገጥማቸው ደግሞ እውነቱን ሽምጥጥ አድርገው ይክዳሉ ። እነርሱ ወደ ነፈሰው የሚነፍሱ ነፍስ አልባ ፈጥረቶች ናቸው ። ለእነርሱ ሚዛን እውነት ሳይሆን ብዛት ነው ። እውነት ደግሞ በብዙ ልብ ውስጥ ሳይሆን በንጹህ ልብ ውስጥ ነው የሚገኘው ። ስሜታዊ ሰዎች ንጹህ ልብ የላቸውም ። ምክንያቱም መርጠው መቀበል አይችሉም ። መምረጥ አለመቻል ንጽህናን ያሳጣል ። ንጽህና በሌለበት ሚዛናዊነት ፈጽሞ አይታሰብም ። ሚዛናዊ ለመሆን ከዘረኝነትም ከጽንፈኝነትም ንጹህ መሆን ያስፈልጋል ። ስሜታዊነት ወይ ዘረኛ አልያም ጽንፈኛ ያደርጋል ፣ ሚዛን ያስታል ።

    የስሜት ብስለት የእምነት ውጤት ነው ። ምክንያቱም የሚያምን ሰው ከጊዜያዊ ስሜት ይልቅ ለዘላቂ ስሜት ተገዥ ነው ። ዘላቂ ስሜት የስሜት ብስለት ማሳያ ነው ። ጊዜያዊ ስሜት ግን የስሜት ብስለት ሳይሆን የስሜት ስለት ነው ። በጊዜያዊ ስሜት ተነሳስተው ያለሙ ሳይሆን ያጠፉ ብዙ ናቸው ። የገነቡ ሳይሆን ያፈረሱ ጥቂት አይደሉም ። በግ ሳይሆን ሰው ያረዱ ቁጥራቸው ቀላል አይደለም ። በስሜት ለመብሰል በእምነት መጠንከር ግድ ነው ። በትእግስት የሚያምን ሰው በንዴት ቶሎ ቱግ አይልም ። በትህትና የሚያምን ሰው ለቁጣ አይቸኩልም ። በየዋህነት የሚያምን ሰው በቂም ራሱን ሲመርዝ አይኖርም ። በቅንነት የሚያምን ለነገር ፈጣን አይሆንም ። በልባምነት የሚያምን ሁሉን በመቀበል እና በመስጠት አይኖርም ጠንቃቃ ነው ። እምነት የቀደመው ስሜት ጠቃሚ ነው ። እምነትን የቀደመ ስሜት ግን ጎጂ ነው ። ስሜት ለእምነት ሲገዛ የሰው ልጅ ክብሩ ከፍ ይላል ። እምነት ለስሜት የተገዛ እለት ግን የሰው ልጅ ክብሩ ዝቅ ይላል ። ስለዚህ ስሜትን ለእምነት እንጅ ፣ እምነትን ለስሜት አናስገዛ ።

   '' ስሜታዊነት በአንድ እግር መቆም ነው ። እምነት ግን በሁለት እግር መቆም ነው ። ''              

           

Tuesday, August 12, 2025

እይታ | Perception

                                                            የማያዛልቅ ነገር

    የማያዛልቅ ነገር ጊዜያዊ ነው ። መጨረሻ የሌለው ቅጽበታዊ ነገር ነው ። አለ ሲባል የሚጠፋ ፣ ጠፋ ሲባል የሚኖር አወዛጋቢ ነገር ነው ። የማያዛልቅ ነገር ስሜትን የመናጥ አቅም አለው ። ስሜትን ሰቅዞ በመያዝ ሰውን በቀላሉ ምርኮ ማድረግ ይችላል ። በቶሎ የሚለመድ ግን በቀላሉ የማይላቀቅ መንቻካ ነው ። አያዛልቅም ግን ደግሞ አይላቀቅም ። የማያዛልቅ ነገር ክብርን ፍቅርን ስሜትን ስልጣንን ጊዜያዊ ነው የሚያደርገው ። የማያዛልቅ ነገር መርህ አይመቸውም ። መርህ ደግሞ ለማያዛልቅ ነገር ቦታ የለውም ። መርህ የማይለዋወጥ ወጥ ነገር ነው ። የማያዛልቅ ነገር ግን ጋጠወጥ ነው ። በመርህ መኖር ፣ በህግና በስርዓት መኖር ነው ። ለማያዛልቅ ነገር መገዛት ፣ ህገወጥ እና ስርዓት አልበኛ ያደርጋል ። 

    መርህም ሆነ ስርዓት በሂደት ነው የሚገነቡት ። በአንድ ጀምበር የማይለመዱ ፣ ውድ ነገሮች ( quality ) ናቸው ። ወድ ስለሆኑ ሰውንም ውድ ክብሩንም ዘላለማዊ ማድረግ ይችላሉ ። ቅጽበታዊ ነገር ርካሽ ነው ። ለቅጽበታዊ ነገር መገዛት ርካሽነት ነው ። ጥራት የጎደለው እቃ ርካሽ እንደሚሆነው ፣ ለማያዛልቅ ነገር የሚገዛ ሰው ርካሽ ነው የሚሆነው ። ወርቅ መሆን የሚችለው መዳብ ይሆናል ። ሸክላ መሆን የነበረበት ገል ይሆናል ። ሊቅ መሆን የነበረበት ደቂቅ ይሆናል ። ምሁር መሆን የሚችለው መሀይም ይሆናል ። ባለጸጋ መሆን የሚችለው ደሀ ይሆናል ። ክቡር መሆን የሚችለው ወራዳ ይሆናል ። ምክንያቱም መርህ አልባ ሰዎች ጎደሎ ናቸው ።

     ለማያዛልቅ ነገር መገዛት በጉድለት ውስጥ መኖር ነው ። እየጎደሉ ሙሉ መሆን አይቻልም ። እያነሱ መብዛት አይኖርም ። እየገደሉ ማዳን የማይታሰብ ነው ። በመርህ መኖር የጎደለን እየሞሉ መሄድ ነው ። በሂደት መልካም ነገርን ማሳደግ ፣ ክብርንም መጨመር ነው ። በመርህ ውስጥ የጎደለ ይሞላል ፣ ያነሰ ይበዛል ፣ የተዋረደ ከፍ ይላል ፣ የተበላሸ ሁሉ ይስተካከላል ። ለጊዜያዊ ነገር መገዛት ግን መስተካከል የሌለው መበላሸት ነው ፣ መመለስ የሌለው መውጣት ነው ፣ መዳን የሌለው መታመም ነው ፣ መነሳት የሌለው መውድቅ ነው ። በመርህ መኖር መጀመሪያ ያማል ፣ መጨረሻው ግን ያምራል ። ጊዜያዊ ነገር መጀመሪያ ያምራል ፣ መጨረሻ ለይ ግን ያማል ። ሰው ደግሞ መጀመሪያው አማረም አላመረም ችግር የለውም ። መጨረሻው ሲያምር ነው ደስ የሚለው ። ተከብሮ ከመዋረድ ፣ ተዋርዶ መከበር ይሻላል ። ይህ የሚሆነው በመርህ መኖር ሲቻል ነው ።  

    ዓላማ እና የማያዛልቅ ነገር አይዋደዱም ፣ ሆድና ጀርባ ናቸው ። የማያዛልቅ ነገር ለዓላማ እንቅፋት ነው ። ዓላማ ደግሞ ለጊዜያዊ ነገር አለርጂ ነው ። በዓላማ መኖር ሩቅ አስቦ ሩቅ ለማደር መታገል ነው ። ለማያዛልቅ ነገር መገዛት ቅርብ አስቦ ቅርብ ማደር ነው ። ዓላማ የማይታየውን ማሳየት ይችላል ። በዓላማ መኖር ከሚታየው በላይ ለማይታየው ነገር ዋጋ መስጠት ነው ። በማያዛልቅ ነገር መሸነፍ ለማይታየው ሳይሆን ለሚታየው ነገር ዋጋ መስጠት ነው ። ለሚታይ ነገር መገዛት እንጭጭነት ነው ። ለማይታይ ነገር መገዛት ግን ብስለት ነው ። ሰው እምነተ ጠንካራ የሚሆነው ፣ እምነቱን በሚያየው ነገር ላይ ሲመስርት ሳይሆን ፣ በማይታይ ነገር ላይ ሲመሰርት ነው ። እምነተ ደካሞች በሚታይ ነገር ያምናሉ ። እምነተ ጠንካሮች በሚታይም በማይታይም ነገር ያምናሉ ። ተጠራጣሪዎች በሚታየውም በማይታየውም ቶሎ አያምኑም ።

   በጊዜያዊ ነገር ማመን ፣ እምነተ ደካማ መሆን ነው ። የዓላማ ሰዎች ግን እምነተ ጠንካሮች ናቸው ። ለዓላማ መኖር ከቅርቡ ይልቅ የሩቁን መመልከት ነው ። ለማያዛልቅ ነገር እጅ መስጠት የሩቁን ሳይሆን የቅርቡን ማየት ነው ። የቅርቡን ማየት ሙሉ በሙሉ ስህተት ነው ማለት አይደለም ። የቅርብ ነገሮች ዋጋ የሚኖራቸው ፣ ለሩቁ ነገር ግብዓት ሲሆኑ ነው ። ሩቅ ላለ ነገር ግብዓት መሆን ያልቻለ ቅርብ ነገር ፣ ዋጋ ያሳጣል እንጅ ዋጋ አያሰጥም ። ዋጋው ይወርዳል እንጅ ከፍ አይልም ። ወርቅ የሚሆነው መዳብ ይሆናል ። አልማዝ የሚሆነው ተራ የመንደር ድንጋይ ይሆናል ። የሩቁን ነገር አጥርቶ መመልከት ፣ የቅርቡን ነገር በአግባቡ ለመጠቀም ይረዳል ። በአላማ ስንኖር እጃችን ላይ ያለውን ነገር ትክክለኛ ዋጋ እናውቃለን ። የማያዛልቅ ነገር ዓላማን የሚጋርድ ጥቁር መጋረጃ ነው ። 

    የማያዛልቅ ነገር ደማቅ ነው ፣ አይነ ግቡ ነው ። ከፍተኛ የስበት ሀይል ( gravitational force ) አለው ። የማያዛልቅ ነገርን መከላከል እንጅ መጋፈጥ ብዙ አያዋጣም ። '' ታሞ ከመማቀቅ አስቀድሞ መጠንቀቅ '' እንደሚባለው ፣ ለጊዜያዊ ነገር ቅድመ ጥንቃቄ ነው የሚያስፈልገው ። ለምሳሌ ጫትን ብንወስድ ለብዙ ወጣቶች ደምቆ ነው የሚታየው ፣ በጣም ያስጎመጃል ነገር ግን እድሜን ይፈጃል ። ጫት ለጊዜያዊ ደስታ እንጅ ለዘላቂ ደስታ ምንም አስተዋጸኦ የለውም ። መጀመሪያ ያደምቃል መጨረሻ ላይ ግን ያደቃል ። ጅማሬው ደስታ ነው ፣ ፍጻሜው ግን ሀዘን ነው ። ሱሰኛ ነገን ዛሬ አይኖርም ። ነገን ዛሬ ይገድላል ። በዛሬ ውስጥ የሞተ ነገ ደግሞ እድሜን በእጥፉ ነው የሚቀንሰው ። የማያዛልቅ ነገር እድሜ ማባከኛ እንጅ ፣ እድሜ ማራዘሚያ ወይም መጠቀሚያ ሊሆን አይችልም ። የማያዛልቅ ነገርን የሙጥኝ ማለት መጨረሻው ብክነት ነው ። 

     የማያዛልቅ ነገር ቅድሚያ የሚሰጠው ነገር አይደለም ። ነገር ግን ስሜት ለማያዛልቅ ነገር ቅድሚያ በመስጠት የተካነ ነው ። ሰው ደግሞ ከምንም በላይ ለስሜቱ ተገዥ ነው ። ስሜቱን መቆጣጠር የቻለ ሰው ፣ ለማያዛልቅ ነገር ፊት አይሰጥም ። ስሜታቸውን መግዛት የተሳናቸው ሰዎች ግን ፣ ፊታቸውን ብቻ አይደለም ልባቸውን ጭምር ነው ለማያዛልቅ ነገር አሳልፈው የሚሰጡት ። ሰው ልቡ ለጊዜያዊ ነገር ሲገዛ ፣ ማክበር ያለበትን ይንቃል ፣ መያዝ ያለበትን ይለቃል ። መገንባት ያለበትን ያፈርሳል ። ማንሳት ያለበትን ነገር ይጥላል ። መተው ያለበትን ነገር የሙጥኝ ይላል ። የሚጎዳውን እየተከተለ ፣ የሚጠቅመውን እየሸሸ ይኖራል ። ጥሩ ነገር የሚያመው ፣ መጥፎ ነገር የሚያስደስተው ብላሽ ይሆናል ። ለማያዛልቅ ነገር ፊት መስጠት መጨረሻው መበላሸት ነው ። 

     የማያዛልቅ ነገር ከጤና ይልቅ በሽታ ነው ። ክብር ሳይሆን ውርደት ነው ። ነጻነት ሳይሆን ባርነት ነው ። ሱስ ህመም ነው ፣ ሀሜት ውርደት ነው ፣ ሌብነት ባርነት ነው ። አለው አለው ባይነት መጨረሻው ባዶነት ነው ። ስርዓት ማጣት ፍጻሜው ሰውነትን ማጣት ነው ። መዝናናት ማብዛት መጨረሻው መጉላላት ነው ። ፊልም ሲበዛ ህይወትን ቅዠት ያደርጋል ። አሉባልታ ሲበዛ ህይወትን ጣዕም አልባ ያደርጋል ። በጠቅላላው ለማያዛልቅ ነገር መገዛት ፣ የህይወትን ጉዞ የከፍታ ሳይሆን የቁልቁለት ነው የሚያደርገው ። ለሁሉ ነገር ትክክለኛ ዋጋ እንዲኖረን የህይወት ዓላማ ይኑረን ። በመርህ እንኑር ። ያኔ መዳቡ ወርቅ ይሆናል ። ተራ ድንጋይ የመሰለን የከበረ አልማዝ ይሆናል ። 

       '' የሁሉም ነገር ዋጋ ያለው አላማ ውስጥ ነው ። አላማ ከሌለን አይደለም የሌላን ነገር ዋጋ ፣ የራሳችንን ዋጋ አናውቅም ። ''            


Saturday, August 9, 2025

እይታ | Perception

                                                             አጋጣሚን መፍጠር 

    አጋጣሚ ያልታሰበ ነገር ነው ። የታሰበ ነገር ሁሉ አጋጣሚ ሊሆን አይችልም ። አጋጣሚ ድንገቴ ነው ። በድንገት ማጣት መሞት መለያየት መክሰር መጎዳት አጋጣሚዎች ናቸው ። ማጣት ብቻ አይደለም ፣ ማግኘትም ድንገተኛ ከሆነ አጋጣሚ ነው ። አጋጣሚ ሀዘንም ደስታም ነው ። ዕጣም ጣጣም ነው ። መርገምም በረከት ነው ። ስኬትም ውድቀትም ነው ። ክብርም ውርደትም ነው ። አጋጣሚ ብዙ ነገር ነው ። አጋጣሚ የምን ውጤት ነው ቢባል ፣ በቀላሉ መልስ የማይገኝለት ጥያቄ ነው ። በቃ አጋጣሚ የእጣ ፈንታ ጉዳይ ነው ። በአጋጣሚ የማያምኑ ሰዎች ፣ አጋጣሚ የሚባል ነገር የለም ይላሉ ፣ ነገር ግን እነርሱ የለም ስላሉ አጋጣሚ አይኖርም ማለት አይደለም ። አጋጣሚ የፈጣሪ ድንቅ ጥበብ መገለጫ ነው ። አጋጣሚ የለም ማለት ሰው የተጻፈለት ታሪክ እንጅ ራሱ የሚጽፈው ታሪክ የለውም ማለት ነው ። የራሱ አሻራ ( legacy ) አይኖረውም ። የመምረጥ ነጻነትም ሊኖረው አይችልም ። የሰው ልጅ የነጻነቱ ማሳያ አንዱ አጋጣሚ ነው ። ፈጣሪ የሰው ልጅ የተጻፈለትን ብቻ እንዲኖር ሳይሆን ፣ አዲስ ታሪክ ጽፎ እንዲኖር ነጻ አድርጎ ነው የፈጠረው ። በዚህ የነጻነት ጉዞ ውስጥ ፣ አጋጣሚ ለሰው ልጅ ፈተና እና እድል ሆኖ ይከሰታል ። 

   አጋጣሚ ጥሩም መጥፎም ሊሆን ይችላል ። ጥሩ አጋጣሚ እድል ነው ። መጥፎ አጋጣሚ ፈተና ነው ። ብልሆች መጥፎ አጋጣሚን ወይም ፈተናን ወደ እድል መቀየር ይችሉበታል ። ጥሩ አጋጣሚን ወይም እድልን በአግባቡ መጠቀምም ያውቁበታል ። ሰነፎች ግን ፈተናን ወይም መጥፎ አጋጣሚን ወደ እድል መቀየር አይችሉም ። እድልን ወይም ጥሩ አጋጣሚን መጠቀምም አይችሉም ። ሰነፎች እድልን ወደ ፈተና ፣ በረከትን ወደ መርገም ፣ መፍትሄን ወደ ችግር ፣ ዕጣን ወደ ጣጣ መለወጥ ነው የሚችሉት ። ድንገት ያገኙትን ምርጥ ወዳጅ ጠላት ያደርጉታል ። እድል ሆኖ የመጣላቸውን ገንዘብ ሱስ ይገዙበታል ። መኪና የሚገዙበትን እድል ቁማር ላፍ ያደርግባቸዋል ። የሚከበሩበትን እድል አላግባብ በመጠቀም ይዋረዱበታል ። ፍቅሩን ጥላቻ ፣ ፈውሱን በሽታ ፣ መድሀኒቱን መርዝ ያደርጋሉ ። አጋጣሚ ከምንም በላይ መማሪያ ነው ። ጥሩ አጋጣሚ ማለፊያ ነው ። መጥፎ አጋጣሚ ደግሞ መማሪያ ነው ። እንዲህ የሚሆነው ግን ለሰነፎች ሳይሆን ለብልሆች ነው ። ለሰነፎች ጥሩ አጋጣሚ መዋረጃ ፣ መጥፎ አጋጣሚ ደግሞ መማሪያ ሳይሆን መማረሪያ ነው ። 

   ህይወት አጋጣሚ ባይኖር የሆነ አይነት ጣዕም ይጎድላታል ። አጋጣሚ የህይወት ቅመም ማጣፈጫ ነው ። በመጥፎም ይሁን በጥሩ ፣ መጠቀም ለቻለ አጋጣሚ ቅመም ነው ። መጠቀም ላልቻለ ግን ቅመም ሳይሆን ቂም ነው የሚሆነው ። ቂም ደግሞ የህይወት ማምረሪያ ሬት ነው ። ምክንያቱም ይህ ቂም የሚሆነው በፈጣሪ ላይ ነው ። ሰው ያለምንም እድል እና ፈተና ፣ እቅዱን ማሳካት መቻሉ ደስታውን ሙሉ አያደርግለትም ። እቅድ አጋጣሚን ይወልዳል ፣ አጋጣሚ ደግሞ ደስታን ሙሉ ያደርጋል ። በአጋጣሚ ያልተፈተነ ወይም በእድል ያልታገዘ እቅድ ፣ በሰው ውስጥ አዲስ ስሜትን የመፍጠር አቅም አይኖረውም ። ስለዚህ ህይወት ወይ በድል አሊያም በእድል ነው ሙሉ የምትሆነው ። ስላቀድን ብቻ ህይወት ሙሉ አትሆንም ፣ ሙሉነትም አይሰማንም ። ለዚህም ነው '' plan for expected as well as un expected. '' የሚባለው ። ለምንጠብቀው ብቻ ሳይሆን ለማንጠብቀውም ነገር መዘጋጀት ግድ ነው ። ያኔ አጋጣሚን ለመጠቀም በቂ ስነ ልቦናዊ አቅም ይኖረናል ። አልያ በአጋጣሚ ምክንያት አቅም ሳይሆን የሚፈጠረው ፣ ቅስም ነው የሚሰበረው ።

   ሰው አስቦ አጋጣሚን መፍጠር ባይችልም ፣ አስቦ ማቀዱ ግን አጋጣሚ እንዲፈጠር ምክንያት ይሆናል ። መልካም አጋጣሚ የማቀድ ውጤት ነው ። '' ሰው ያቅዳል ፈጣሪ ይፈጽማል ። '' አይደል የሚባለው ። አጋጣሚ ፈጣሪ የሰው ልጅ እቅዱን እንዲያሳካ የሚቸረው ድንቅ ስጦታ ነው ። አጋጣሚ ዝግጁ ለሆነ ሰው እንጅ ፣ ዝግጁ ላልሆነ አይሰጥም ። እቅድ ዝግጅት ነው ። ማቀድ የቻለ ሰው አጋጣሚን ለመቀበል ዝግጁ ነው ። ማቀድ ያልቻለ ደግሞ አጋጣሚን ለመቀበልም ለመጠቀምም አቅም አይኖረውም ። ሰው በአጋጣሚ ብቻ ዘላቂ ለውጥ ሊያመጣ አይችልም ። እቅድ እና አጋጣሚ ተባብረው ነው ፣ ለውጥን ዘላቂ የሚያደርጉት ። አጋጣሚን ለመፍጠር በእቅድ መኖር አስፈላጊ ነው ። በአጋጣሚ እየኖረ የከበረ የለም ። በእቅድ እየኖረ በአጋጣሚ የከበረ ግን ብዙ ነው ። እቅድ አጋጣሚን ሲቀድም ለውጥ አዎንታዊ ይሆናል ። አጋጣሚ እቅድን ሲቀድም ግን ለውጥ አሉታዊም አዎንታዊም የመሆን እድል ይኖረዋል ። ይህ የሚወሰነው እንደየሰው አስተሳሰብ እና አቀባበል ነው ። ጎበዝ ሰዎች አጋጣሚን ይፈጥራሉ ይጠቀማሉ ። ሰነፎች ግን የተፈጠረን አጋጣሚ ያባክናሉ ። አጋጣሚ እንዳይባክን በእቅድ እና በዝግጅት እንኑር ።

  ጊዜን ማባከን አጋጣሚን ማባከን ነው ። ጊዜን በግባቡ መጠቀም አጋጣሚን መፍጠርም መጠቀምም ነው ። ጊዜም አጋጣሚም የፈጣሪ ችሮታዎች ናቸው ። በሁለቱም ላይ የሰው ልጅ ስልጣን የለውም ። ሁለቱንም መጠቀም እንጅ ማዘዝ አይችልም ። ለመጠቀም መታዘዝ ፣ ለመታዘዝ ትሁት መሆን አስፈላጊ ነው ። አጋጣሚ ለትሁታን በረከት ነው ። ለእብሪተኞች ግን መቅሰፍት ነው ። '' ለሀጥዓን የመጣ ለጻድቃን ይተርፋል '' እንዲባል ፣ መቅሰፍቱ ለመልካሞች  ሊተርፍ ይችላል ። አጋጣሚ መልካም እንዲሆን ፣ ጊዜን ለመልካም ነገር እናውል ። ጊዜ አጋጣሚን ይጠብቃል ፣ አጋጣሚም ጊዜን ይጠብቃል ። በጊዜው የሚከሰት አጋጣሚ ሸክም አቅላይ ነው ። ያለጊዜው የሚከሰት አጋጣሚ ግን ሸክም አቅላይ ሳይሆን ራሱ ሸክም ነው ። ሸክም አጋጣሚ ነገር የመሸከም ውጤት ነው ። ጥላቻን በቀልን ቂምን የመሸከም ማሳያ ነው ። ስለዚህ በህይወታችን መልካም ነገር እንዲገጥመን ፣ ጥላቻን ቂምን ብቀልን አንሸከም ። ፍቅርን ይቅርታን የዋህነትን እንሽከም ። ያኔ እድል በሆነው መልካም አጋጣሚ ህይወት ሰላም እና ቀላል ትሆናለች ። 

          '' ማቀድ የሰው ድርሻ ነው ። አጋጣሚ የፈጣሪ ችሮታ ነው ። ''   

                                                                

Monday, August 4, 2025

እይታ | Perception

                                                            ፍቅር እና መስፈርት

   ፍቅር መርህ እንጅ መስፈርት የለውም ። መስፈርት ለፍቅር ምንም ነው ። ለፍቅር ሰው ምንም ይሁን ምን ፣ ይኑረው አይኑረው ሰው መሆኑ ብቻ በቂ ነው ። በፍቅር ዘንድ የሰው መርዘም ወይም ማጠር ፣ ዋጋውን ከፍ ወይም ዝቅ አያደርገውም ። መቅላት ወይም መጥቆር የሚጨምረው የሚቀንሰው ነገር የለም ። ጌታም ይሁን ባርያ ከመፈቀር የሚያግደው አይኖርም ። ለመፈቀር ሰው ዶክተር እንጅነር ፕሮፌሰር ባለጸጋ ወይም አዋቂ መሆን አይጠበቅበትም ፣ መልካም ሰው መሆኑ በቂ ነው ። ለፍቅር የሰው ማእረጉ ሳይሆን መልካምነቱ ነው የሚያስፈልገው ። በትጋት ጎበዝ የሆኑ ሰዎች ፣ ለመልካምነት ግን ሰነፍ የሆኑ ሰዎች ፣ በፍቅር ዘንድ ዋጋ የላቸውም ። ትጋት ያስከብራል ግን ለስራ ባለን ፍቅር እንጅ ለሰው ባለን ፍቅር  አይደለም ። ለስራ ያለን ፍቅር ብቻ ሰው አያደርገንም ፣ ለሰው ያለን ፍቅር ነው ሰው የሚያደርገን ። ስለዚህ ስራ ስንሰራ ለሰው እንደምንሰራ እያሰብን እንስራ ። ያኔ ፍቅር ሰውን ለመጥቀም እንጅ ለመጉዳት መስራት እንደሌለብን ያሳስበናል ። ይህ የፍቅር መስፈርት ሳይሆን መርህ ነው ። 

   ሰው ገንዘብ ስላለው ሊከበር ይችላል ። ያለፍቅር ግን በገንዘቡ ብቻ ሊወደድ አይችልም ። ሰው መወደድም መከበርም የሚችለው ፣ በገንዘቡ ላይ መልካምነትን ሲጨምር ነው ። ገንዘብ ሲቀነስ ፍቅር ፣ እኩል ይሆናል ክብር ሲቀነስ መወደድ ። መወደድ የሌለው ክብር ሰውን በሰው ልብ ውስጥ አያነግስም ። ክብር ከፍቅር ጋር ነው በሰው ልብ ላይ የሚያነግሰው ። ገንዘብ ክብርም ፍቅርም መሆን ይችላል ። ሰው በገንዘቡ መልካም ስራ ከሰራበት ፣ በገንዘቡ ፍቅርንም ክብርንም ያተርፋል ። በገንዘቡ ግን ክፋት ከሰራበት ፣ ተፈርቶ  ሊከበር ይችላል ፣ ነገር ግን ተወዶ ሊከበር በፍጹም አይችልም ። ተፈርቶ ከመከበር ተወዶ መከበር የተሻለ ነው ። የክብር የመጨረሻው ከፍታ ( climax ) ፍቅር ነው ። ገንዘብን የክብር ምንጭ ማድረግ የክብርን ከፍታ ሳይሆን የሚያሳየን ፣ የሞራል አዘቅት ነው የሚሆንብን ። ገንዘብ የፍቅር መሳርያ እንጅ ፍቅር የገንዘብ መሳርያ ሊሆን አይችልም ። ገንዘብን የፍቅር መሳርያ ካደረግን ፣ በገንዘባችን መልካም ስራ በመስራት ፣ ከክብር ሁሉ የላቀውን ክብር ማግኘት እንችላለን ። ፍቅርን ግን የገንዘብ መሳርያ ካደረግን ፣ የላቀውን ክብር ሳይሆን በፈጣሪ ዘንድ የተናቀውን ክብር ነው የምናገኘው ። ይህ ክብር እውነተኛ ሳይሆን አርተፊሻል ነው ። ዘላለማዊ ሳይሆን ጊዜያዊ ነው ። ከሰው ልብ ሳይሆን ከሰው አፍ ብቻ የሚገኝ ክብር ነው ። ስለዚህ ፍቅር በገንዘብ አይሰፈርም ፣ ነገር ግን ገንዘብን በአግባቡ መጠቀም ይችላል ። ይህ ሌላኛው የፍቅር መርህ ነው ።     

    ፍቅርና ውበት አብረው ይሄዳሉ ። ከዉጪ ይልቅ የውስጥ ውበት ለፍቅር ቅርብ ነው ። ፍቅር የሚታይ ሳይሆን የሚኖር ነው ። ውስጣዊ ውበትም በመኖር የሚገነባ ስብእና ነው ። ስለዚህ ውስጣዊ ውበት እና ፍቅር በጣም ይጣጣማሉ ። ውጪያዊ ውበት ግን ለጊዜያዊ ስሜት ቅርብ ነው ። ምክንያቱም ውጪያዊ ውበት የሚታይ እንጅ የሚኖር አይደለም ። '' ሲያዩት ያላመረ ሲበሉት ያቅራል '' ይባላል ። ይህ ለምግብ እንጅ ለሰው ልጅ አይሰራም ። ሲያዩት ያማረ ሰው ፣ አብረው ሲኖሩ ያቅር ይሆናል ። ሲያዩት ያላማረው ግን ለፍቅር ምቹ ሊሆን ይችላል ። የአፍንጫ ጎራዳ ወይም ሰልካካ መሆን ለፍቅር ግድ አይሰጠውም ። ካማረ አይን በላይ ያማረ አመለካከት ለፍቅር አስፈላጊ ነው ። ከዉብ ከንፈር በላይ ውብ ንግግር ፍቅርን ይማርከዋል ። ከለስላሳ ጸጉር በላይ ለስላሳ ባህሪ ፍቅርን ይገዘዋል ። ትህትና ውበት ነው ። ፍቅር ካለ ትህትና አለ ። ችምችም ካለ ጥርስ በላይ ትህትና ሰውን ውብ ያደርጋል ። ትሁት ሰው ውብ ነው ፣ ውጪያዊ ሳይሆን ውበቱ ውስጣዊ ነው ። ደግነት ውበት ነው ። ደግነት የሚኖረው ፍቅር ባለበት ነው ። ከተስተካከለ ቁመና በላይ ደግነት ሰውን ውብ የማድረግ አቅም አለው ። ርህራሄም ውበት ነው ። ያለ ፍቅር ርህራሄ አይታሰብም ። ከአለንጋ ጣት በላይ ርህራሄ ለሰው ልጅ ውበቱ ነው ። የሰው እውነተኛ ውበቶች ርህራሄ ደግነት ትህትና ቅንነት እና የመሳሰሉት ናቸው ። እነዚህ ደግሞ በሌላ አነጋገር የፍቅር መገለጫዎች ናቸው ። ፍቅር ከውብ አካል በላይ ውብ ስብእና ይገዛዋል ። ይህ ሌላኛው የፍቅር መርህ ነው ። 

   ከፍቅር ሁሉ የላቀው ፍቅር ፈጣሪን መውደድ ነው ። ሲቀጥል የሰውን ልጅ መውደድ ነው ። ከእነዚህ አካላት ውጪ የሰው ልጅ አብልጦ ሊወደው የሚችለው ነገር ሊኖር አይገባም ። እነርሱን በማስቀደም ሌላን ነገር መውደድ ይችላል ። ነገር ግን ከእነርሱ አስቀድሞ የሚወደው ነገር ሊኖር አይገባም ። ከሰው አብልጦ ገንዘብን መውደድ ገብጋባነት ነው ። ገብጋባነት ደግሞ እንስሳነት ነው ። ከሰው ይልቅ እንስሳን መውደድ ልበቢስነት ነው ። ልበቢስነት እንሰሳነት ነው ። እንሰሳነትም ልበቢስነት ነው ። ከሰው ይልቅ ሱስን መውደድ ልበ ደንዳናነት ነው ። ከልጆቹ ቁማር የበለጠበት አባት ልበ ደናዳና ነው ። ከሚስቱ ይልቅ አልኮል የሚናፍቀው ባል ልበ ደንዳና ነው ። ለባል ሳይሆን ለሀሜት ቅድሚያ የምትሰጥ ሚስት ልበ ደንዳና ናት ። ከሰው በላይ እውቀትን የሚወዱ ሰዎች ራስ ወዳዶች ናቸው ። ከእውቀት ክብርን ለማግኘት ብለው ፍቅረኛቸውን ችላ ያሉ ሰዎች ራስ ወዳዶች ናቸው ። እውነተኛ ፍቅር ለሁሉም ውይም ከሁሉ ነገር ይልቅ ሰውን ማስቀደም ነው ። እውቀትን ገንዘብን ቁስን ሱስን አብልጦ መውደድ ሰውን ያሳጣል ። ሰውን አብልጦ መውደድ ግን እውቀትንም ገንዘብንም አያሳጣም ። ሰውን ማጣት ሁሉን ማጣት ነው ። ሰውን ማግኘት ሁሉን ማግኘት ነው ። ፍቅር ማለት ሰውን እንደራስ በመውደድ ሁሉን ማግኘት ነው ። ፍቅር ካለ ሁሉም አለ ፣ ፍቅር ከሌለ ምንም የለም ። ይህ ከሁሉ የላቀው የፍቅር መርህ ነው ።  

    '' ፍቅር መነሻም መድረሻም ነው ። ምክንያቱም የመርሆች ሁሉ አለቃ ነው ። ''                 

Wednesday, July 30, 2025

እይታ | Perception

                                             ዋናው ኮንቴክስቱ ( አውዱ )

     ሁለት መታወቂያ የተሰኘው ፊልም ላይ ፣ ዳዊት አባተ ወይም በገጸ ባህሪ ስሙ ቢኒያም እንዲህ ሲል ይደመጣል ‘’ በህይወት እውነት ወይም ውሸት ፣ ጥሩ ወይም መጥፎ ፣ ሞራላዊ ወይም ኢ ሞራላዊ የሚባል ነገር የለም ፣ ዋናው አውዱ ( ኮንቴክስቱ ) ነው ። ’’ አውድ ሲባል በዋናነት ሁኔታ ማለት ነው ። ሰው ህይወቱን በአውድ ወይም በሁኔታ የሚመራ ከሆነ ፣ እውነትን በእውነትነቱ ሳይሆን የሚመዝነው ፣ እውነት በሚያመጣው ውጤት ላይ ተመስርቶ ነው ፣ እውነትን የሚለካው ። ይህ ደግሞ የሰውን ልጅ ውጤት ተኮር እንጅ ሂደት ተኮር አያደርገውም ። ነጮቹ ሰው ከውጤቱ በላይ ሂደቱ ላይ ትኩረት እንዲያደርግ ሲመክሩ ‘’ Trust the process! ‘’ ይላሉ ። 

   ከውጤቱ በላይ ለሂደቱ ትኩረት የሚሰጡ ሰዎች በመርህ የሚመሩ ናቸው ። ከሂደቱ በላይ ለውጤቱ ዋጋ የሚሰጡ ሰዎች ግን አብዛኛውን ጊዜ መርህ አልባ ናቸው ። ያው የትም ፍጪው ዱቄቱን አምጪው ይመቻቸዋል ። አብዝተው ውጤት የሚፈልጉ ሰዎች ፣ መርዝን መድሃኒት ነው እስከማለት ይደርሳሉ ። በእውነት መንገድ ውጤት ከሚያጡ ፣ በውሸት ተጉዘው ውጤት ላይ መድረስ ምርጫቸው ነው ። ለእነርሱ እውነት ከሁኔታ በልጦ አያውቅም ። ሁኔታ ነው ከእውነት የሚበልጥባቸው ። ስለ እውነት ማጣት መራብ መጠማት መዋረድ ፣ ለእነርሱ የጀግና ሳይሆን የቀሽም ሰው ተግባር ነው ። 

    በእርግጥ አውዳዊ ፍቺ የሚያስፈልገው እውነት አለ ። ነገር ግን ሁሉም እውነት አውዳዊ ፍቺ አያስፈልገውም ። ለምሳሌ የወል እውነት አውዳዊ ፍቺ አያስፈልገውም ። የወል እውነት ቦታ ጊዜ ሁኔታ የማይቀያይሩት እውነት ነው ። ጸሀይ በምስራቅ ወጥታ በምራብ ትጠልቃለች ። ይህ የሰፈር እውነት ሳይሆን የዓለም እውነት ነው ። ውሀ ውሀ እንጅ ነዳጅ አይሆንም ። ነዳጅም እንደዚሁ ውሀ ሊሆን አይችልም ። ይህ እውነት የሆኑ ቡድኖች ያጸደቁት ሳይሆን ፣ ሁሉም ሰው አምኖ የተቀበለው እውነት ነው ። ውጤት ተኮር የሆኑ ሰዎች ግን ፣ ከቻሉ ውሀ እና ነዳጅን ቀላቅለው ፣ ነዳጅ ነው ብለው ይሸጣሉ ። ምክንያቱም ከሂደቱ በላይ የሚተማመኑት በውጤቱ ነው ። ለዚህ ደግሞ ማሳመኛ ይሆናቸው ዘንድ ፣ ውሸትን ብቻ ይዘው አይቀርቡም ። ውሸትን በእውነት ሸፍነው ያቀርባሉ ።

   ውጤት ተኮር መሆን በራሱ ስህተት አይደለም ። ስህተት የሚሆነው ለውጤቱ ሲባል የማጭበርበር ስራ ሲሰራ ነው ። ውጤቱን ጥሩ ለማድረግ ሂደቱን መጥፎ ማድረግ ትክክል አይደለም ። ከሆነ ወይም ከተቻለ ውጤቱንም ጥሩ ሂደቱንም ትክክል ማድረግ ተገቢ ነው ። ካልሆነ ግን ውጤቱ ምንም ቢሆን ፣ ሂደቱን ትክክል ማድረግ ነው የሚያስፈልገው ። አንድ አንድ ሁኔታዎች ፣ የሰው ልጆች እስከሆንን ድረስ ፣ ሂደቱን በማበላሸት ውጤቱን ማሳመር እንደሚቻል ይጠቁሙናል ። ያኔ የገጠመን እውነት የወል ሳይሆን አንጻራዊ ስለሆነ ፣ ውሳኔያችንን እንደሁኔታው ማድረግ ግድ ይላል ።

    አንጻራዊ እውነት በአማራጭ የተሞላ ነው ። እንደ ሰው ፍጹም ስላልሆንን ፣በዚህ ጊዜ ውሳኔያችን ከሂደቱ በላይ በውጤቱ ላይ ቢመሰረት መልካም ነው ። ምርጫችንም የተሻለ ይሆናል ። በስህተት መንገድ ትክክል የሆነ ውጤት ማምጣት ባይቻልም ፣ በአንጻሩ ጥሩ ነገር ማድረግ ይቻላል ። እንደዚህ አይነት ሁኔታ ሲገጥመን ፣ ውሸት ወይም እውነት ፣ ትክክል ወይም ስህተት ሚዛን አይሆኑም ። ሚዛን የሚሆኑት ማዳን ወይም መግደል ፣ ማጥፋት ወይም ማልማት ፣ ማበላሸት ወይም ማስተካከል ናቸው ። በእርግጥ የሀገሬ ሰው '' ካልደፈረሰ አይጠራም ። '' ይላል ። የደፈረሰ ሁሉ ይጠራል ማለት ግን አይደለም ። አንዳንድ ነገሮች ላይጠሩ ይደፈረሳሉ ። ላይቃኑ ይጣመማሉ ፣ ላይስተካከሉ ይበላሻሉ ፣ ላይመለሱ ይለወጣሉ ። ስለዚህ በህይወት ስንኖር ፣ ከውሳኔ በፊት ሁኔታን በጥልቀት መፈተሽ እና መመዘን ያስፈልጋል ። ምክንያቱም ማዳን የምንችለውን ልንገድል እንችላለን ። መስተካከል የሚችለው እንደተበላሸ ሊቀር ይችላል ። መቆም ያለበት ወድቆ እንክትክቱ ሊወጣ ይችላል ። ሰዎች ነን ፍጹም ልንሆን አንችልም ። ስለዚህ ሁኔታን በአንጻራዊ እውነት ከምንመዝን ፣ አንጻራዊ እውነትን በሁኔታ ( context) ብንመዝን የተሻለ ነው ።

   እውነት ከእውነት ይለያያል ። ሁሉም እውነት እኩል መታየት የለበትም ። የሚጠቅም እውነት ከሚጎዳ እውነት ጋር እኩል መታየት አይኖርበትም ። የሚያጣላ እውነት ከሚያፋቅር እውነት ጋር ሊስተካከል አይገባውም ። ጥቁር ታሪክ የተሸከመ እውነት ፣ የጀግንነት ታሪክ ከተሸከመ ታሪክ ጋር እኩል ትኩረት ሊሰጠው አይገባም ። ምክንያቱም ጥቁር ታሪክ ጸጸትን በቀልን ቁጭትን ነው የሚወልደው ። የጀግንነት ታሪክ ግን ሞራልን አሸናፊነትን አንድነትን ነው የሚወልደው ። ስለዚህ ለሁሉም እውነት መታመን ታማኝ አያደርግም ። ትክክለኛ ታማኝነት ፍቅርን ፍትህን አንድነትን ለሚያሰፍን እውነት መታመን ነው ። ለሁሉም እውነት መታመን ጅልነት ነው ። ለምርጥ እውነት መታመን ግን ጀግንነት ነው ። በነገራችን ላይ ሰውን ለመጉዳት እውነተኛ የሚሆኑ ሰዎች አሉ ፣ እነዚህ ሰዎች ክፉዎች ናቸው ። ምክንያቱም የእነርሱ እውነት ፍቅር የለውም ። ፍቅር የሌለው እውነት ደግሞ የሞተ ነው ። ሰውን ለመጉዳት እውነተኛ ከመሆን ፣ ሰውን ለማዳን ውሸታም መሆን ይሻላል ። ነገርን ከሰው አንጻር እንጅ ፣ ሰውን ከነገር አንጻር መመልከት ልክ አይደለም ። የሚጎዳን እውነት ይዞ መኖር ፣ ሰውን ከነገር አንጻር መመልከት ነው ። 

   ዋናው አውዱ ( ኮንተክስቱ ) ማለት በምንም ጉዳይ ቢሆን ሰውን እናስቀድም ማለት ነው ። እውነትም አንጻራዊ እውነት ሰብአዊነትን ማስቀደም አለባቸው ። በእርግጥ የወል እውነት ፣ በምንም አይነት ሁኔታ ውስጥ ሰብአዊነትን ቢያስከብር እንጅ አያዋርድም ። አንጻራዊ እውነት ግን አስቸጋሪ ነው ። ፍትህን ለማዛባት ሰብአዊነትን ለመጣስ ሊውል ይችላል ። ስለዚህ አንጻራዊ እውነት ሲገጥመን መጠንቀቅ አለብን ። 

  '' ከሁኔታ የሚበልጠው እውነት የሰውን ልጅ ክብር የሚጨምር ነው ። በሁኔታ የሚገደብ እውነት ግን የሰውን ክብር ሊጨምርም ሊቀንስም ይችላል ። ''    

    

Tuesday, July 15, 2025

እይታ | Perception

                                                             ራስን መመርመር

  ራስን መመርመር ራስን መመልከት ነው ። አንድ የላቦራቶሪ ቴክኒሺያን በሰው ደም ውስጥ ፣ በሽታ አምጪ ህዋስ መኖሩን ለማረጋገጥ ፣ ማይክሮስኮፕን ይጠቀማል ። በተመሳሳይ የሰው ልጅ የስብእና በሽታ ሲገጥመው ፣ ራሱን ለመመርመር የስብእና ግድፈቱን የሚለይበት ማይክሮስኮፕ ያስፈልገዋል ። በሽታውን ለማወቅ ማይክሮስኮፑን በአግባቡ መጠቀም ግድ ይላል ። የሰው ልጅ የራሱን የስብእና በሽታ የሚያይበት ማይክሮስኮፕ አንዱ ጥሞና ነው ። ጥሞና የባህሪ በሽታን የመለየት ከፍተኛ አቅም አለው ። ጥሞና ሰውን ከፍተኛ መረጋጋት ውስጥ ይከታል ። ሰውን እንደ ፍሪጅ አቀዝቅዞ ፣ ባህሪን ከሚበክል ስሜት እና ሀሳብ ነጻ ያደርጋል ። ሰው በሽታውን አውቆ መድሀኒቱን እንዲፈልግ ፣ ጥሞና ብርሃን ይሆነዋል ። ጥሞና ዝምታ ነው ። ፈርቶ ዝም ማለት ሳይሆን አቅዶ ዝም ማለት ነው ።

  ፈርቶ ዝም ማለት ሁለት ገጽ አለው ። አንድም ለኪሳራ በሌላ በኩል ደግሞ ለትርፍ ሊዳርግ ይችላል ። የፍርሀት ዝምታ ከስሜታዊ ሰው ጥቃት ይጠብቀናል ። በስሜታዊ ሰው ፊት በፍርሀትም ይሁን በእውቀት ዝም ማለት ራስን ከአደጋ መከላከል ነው ። የፍርሀት ዝምታ ከዚህ አንጻር ሲታይ ጠቃሚ ነው ። ግን በሌላ ገጹ ሲታይ የፍርሀት ዝምታ ብዙ ነገር ያሳጣል ። ዝምታ ወርቅ ነው የሚባለውን ያህል ውድቅ የሚሆንበት ቦታም አለ ። መናገር ሲኖርብን ዝም ማለት ያሳጣል ። በእርግጥ ዝም ማለት ሲገባ መናገርም ያስቀጣል ። ሁለቱም እኩል ጉዳት አላቸው ። ከሁለቱም ጉዳት ነጻ የሚያወጣን ማስተዋል ነው ። ለዚህ ደግሞ መፍትሄው ጥሞና ነው ። 

 ጥሞና የነገርን ክብደት እና ቅለት ለመለየት ወሳኝ ነው ። ጥሞና የማስተዋል አቅምን ሲጨምር ፣ የፍርሀት ዝምታ ግን ማስተዋልን ይቀንሳል ። በጥሞና ውስጥ ነገርን በልኩ ማወቅ እና መረዳት ይቻላል ። ጤናማውን ከበሽተኛው ለመለየት ቀላል ይሆናል ። ይህ ደግሞ ራስን ለማስተካከል እድል ይሰጣል ። ጥሞና ራስን መመርመሪያ ምርጥ ማይክሮስኮፕ ነው ።

   ሌላኛው ራስን መመርመሪያ ማይክሮስኮፕ ተግባቦት ነው ። ከሰው ጋር መነጋገር ራስን ማያ መስተዋት ነው ። ሰው ፊቱ ላይ ያለውን ጉድፍ ለማጽዳት መስተዋት ይጠቀማል ። የባህሪ ግድፈቱን ለማጽዳት ደግሞ አጠገቡ ያለውን የቅርቤ የሚለውን ሰው ፣ እንደመስተዋት መጠቀም አለበት ። ሰው በምልአት ራሱን ማየት አይችልም ። ለእርሱ የተሰወረው አጠገቡ ላለ ሰው ግልጽ ሊሆን ይችላል ። በተለይ በሳል ሰው ካለ ፣ የማይታየውን ማየት የሚችል አቅም ስላለው ፣ ራስን ለመመርመር እና ለማስተካከል ጥሩ አቅም ይሆነናል ። ሰው ለብቻው ራሱን በመመርመር ውጤታማ አይሆንም ። የሚያግዘው እና የሚረዳው ሰው ያስፈልገዋል ።

   ሰው ራሱን ሲመረምር ሀቀኛ መሆን አለበት ። ስህተቱን ስህተት ፣ ልኩን ትክክል ነው ማለት አለበት ። ስህተቱን ልክ ልኩን ስህተት ካደረገ ግን ፣ ራሱን እየመረመረ ሳይሆን ራሱን እያባበለ ነው ። ራስን በማባበል ደግሞ አሉታዊ እንጅ አዎንታዊ ለውጥ ማምጣት አይቻልም ። እየባሱ መሄድ እንጅ መሻሻል አይኖርም ። ሰው ወደ ላይ የሚያድገው እውነትን መቀበል ሲችል ነው ። ወደ ታች የሚወርደው እውነትን መቀበል ሲያቅተው ነው ። ለስህተት ምክንያት እየሰጡ ራስን ከእውነት ማሸሽ ፣ መጨረሻው እድገት ሳይሆን ውርደት ነው ።

 ስለዚህ ራስን መርምሮ ለማሻሻል ፣ እውነትን መቀበል ቁልፍ ብቻ አይደለም ፣ የቁልፎች ሁሉ ቁልፍ ( Master key ) ነው ።

   ትክክለኛ ራሱን መርማሪ ፣ ተንኮል በመስራቱ ራሱን ደግ አደረክ ብሎ አያሞግስም ። ባይሆን በመጸጸት ራሱን ለማስተካከል ይጥራል ። ባደረገው መልካም ነገር ይደሰታል ራሱንም ይሸልማል ። በሰራው ስህተት ደግሞ ራሱን ይወቅሳል ። በልኩ ያዝናል በልኩ ደግሞ ይደሰታል ። ደስታው የበለጠ ተግቶ እንዲሰራ ሀይል ይሆነዋል ። ሀዘኑ ደግሞ ስህተቱን ይቀንስለታል ። በስህተት ማዘን በመልካም ስራ መደሰት ሰውነት ነው ። በተንኮል መደሰት በመልካም ስራ መከፋት አውሬነት ነው ። አንዳንድ ሰዎች ማታ ላይ ተኝተው ፣ የቀን ስራቸውን የሚያሰላስሉት ፣ በሰሩት ተንኮል ለመሳቅ እና ባደረጉት መልካም ነገር ለማዘን ነው ። ከዚያም በተጨማሪ የተሻለ ተንኮል ለማሰብ እና ለማቀድ ነው ።

     ተንኮል ለማቀድ ራሱን ከሚመረምር ሰው ፣ ራሱን የማይመረምር ብኩን ይሻላል ። ምክንያቱም ስህተትን ሆን ብሎ ሳይሆን ፣ ባለማወቅ ነው የሚሰራው ። አስቦ ራሱን መመርመር ባይችልም ፣ በሂደት በህይወት ልምድ ስህተቱን መቀነሱ አይቀርም ። ይህች ምድር ትልቅ ጥፋትን የምታስተናግደው ፣ ሳያውቁ ስህተት በሚሰሩት ሳይሆን አውቀው ሆን ብለው ስህተት በሚሰሩት ነው ። ክፉ ለማድረግ ራስን መመርመር ፣ ራስን መመርመር ሳይሆን ራስን መራር ማድረግ ነው ። ( Weak acid ) ደካማ አሲድን ጠንካራ አሲድ ( Strong acid ) ማድረግ ነው ። ይህ ደግሞ ከጎጂነት ወደ አጥፊነት መቀየር ነው ። ሰው ራሱን የሚመረምረው አጥፊ ከሆነ አልሚ ለመሆን ነው ። ተንኮለኞች ግን ራሳቸውን የሚመረምሩት የበለጠ አጥፊ ለመሆን ነው ።

   ራሳችንን መመርመር  ለክፋት ሳይሆን መልካም ለማድረግ መሆን አለበት ። ስህተትን ለመቀነስ እንጅ ስህተትን ወደ ተንኮል ለመቀየር መሆን የለበትም ። ራስን ለማረም እንጅ አረም ለማድረግ ራስን መፈተሽ አያስፈልግም ። ስራን ለማስተካከል እንጅ ለማበላሸት ራስን መመርመር አስፈላጊ አይደለም ። በዚህች ምድር ስንኖር ራስን መመርመር እጅግ በጣም አስፈላጊ ነው ። ነገር ግን ራሳችንን መመርመር ያለብን ምድርን ለማልማት እንጅ ለማጥፋት አይሁን ።

    ‘’ ራስን ለማስተካከል ራስን መመርመር ነው ቁልፉ ። ‘’                 

Saturday, July 5, 2025

እይታ | Perception

                                                       

                       መቅናት እና ማስቀናት

      ‘’ የቀናም ያስቀናም ሁሉም ቤት ያፈርሳል ። ‘’ አለ ዘፋኙ ። ምክንያቱም መቅናትም ማስቀናትም የትዳር ማነቆዎች ናቸው ። ትዳርን የማፍረስ አቅም አላቸው ። መቅናት እኔ ብቻ ልወደድ ባይነት ስለሆነ ፣ በፍቅር ውስጥ መጋራትን እንጅ ማጋራትን አይፈቅድም ። ቅናት ከመስጠት ይልቅ መቀበል ላይ ትኩረት ያደርጋል ። ዞሮ ዞሮ ቅናት የፍቅር ተቃራኒ ነው ። ምክንያቱም ፍቅር ከመቀበል ይልቅ ለመስጠት ከፍ ያለ ቦታ መስጠት ነው ። መስጠት ባነሰበት ሁሉ ፍቅር ያንሳል ። በመቀበል ብቻ ደግሞ ፍቅርን ማጎልበት አይቻልም ። መስጠትም መሰጠትም ባለበት ግን ፍቅር ያድጋል ይበዛል ። ያኔ መቅናትም ማስቀናትም አቅም ያጣሉ ። ለመስጠት ዝግጁ የሆነ ልብ ለቅናት ቦታ የለውም ።

   ቀናተኛ ሰው ለሰው ሲሰጥ ከእርሱ ላይ የተወሰደበት ይመስለዋል ። ካገኘው ይልቅ ያጣው ይታየዋል ። ከተሰጠው ይልቅ የተነፈገው ይጎላበታል ። ከፍቅር ይልቅ ለጥላቻ ምክንያት ይፈልጋል ። ቅናት ልብን ስለሚሰውር ፣ በቀናተኛ ሰው ዘንድ ከእርሱ ውጪ ሌላ ሰው ልክ ሆኖ አያውቅም ። ለእርሱ ልኩ ስህተት ፣ ስህተቱ ደግሞ ልክ ይሆናል ። ይህ ብቻ አይደለም ስህተትን ማጉላት ፣ ልክ የሆነውን ስራ ማኮሰስ ይችላል ። ለራስ መኖር እንጅ ለሌላው መኖር በቀናተኛ ሰው ዘንድ አይታሰብም ። ለሰዎች ሲኖር የማይደሰት ፣ ሰዎች ሲኖሩለት ብቻ የሚደሰት ራስ ወዳድ ፍጥረት ነው ። መኖር ሳይሆን ምን ጊዜም ማኖር ነው የሚፈልገው ። ከራሱ ውጪ ማየት የማይችል እውር ነው ። ቀናተኛ ሰው የራስ መንገድ እንጅ የጋራ መንገድ አይመቸውም ።

የራስ መንገድ አስፈላጊ ቢሆንም ፣ ለጋራ መንገድ ግን ክፍት መሆን አለበት ። የጋራ መንገድን ማስተናገድ የማይችል የራስ መንገድ ግትር ነው የሚያደርገው ። ይህ ደግሞ ከስምምነት ይልቅ ለግጭት ይዳርጋል ። በቀላሉ የሚፈታ ሳይሆን የማይፈታ ግጭት ነው የሚፈጥረው ።

   መቅናት መቃጠልም ማቃጠልም ነው ። መጀመሪያ በሰው ድርጊት መቃጠል ነው ። ሲቀጥል ነገር ማቀጣጠል ነው ። ሲለጥቅ በራስ ድርጊት ሌላውን ማቃጠል ነው ። በቅናት ቤቱን ያፈረሰ እንጅ የገነባ የለም ። ግንኙነቱን የተወ እንጅ በግንኙነቱ ፍሬ ያፈራ የለም ። ያፈረ እንጅ የኮራ ሊኖር አይችልም ። በጥርጣሬ እየተወጉ ሰላምን ማፍረስ እንጅ መገንባት በቅናት ፈጽሞ አይቻልም ። ‘’ ተጠራጥሮ ትዳር ኑሮ መች ያሞቃል ፣ የቀናም ያስቀናም ሁሉም ቤት ያፈርሳል ። ‘’ እንዲል ዘፋኙ ። ቅናት እና ጥርጣሬ የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታ ናቸው ። ቅናት ባለበት ጥርጣሬ ሊኖር ግድ ነው ። ጥርጣሬ ባለበት ቅናት ሊጠፋ አይችልም ። ሁለቱ ተባብረው ነው ሰውን አንድደው አመድ የሚያደርጉት ። ቅናት እና ጥርጣሬ!

   መቅናት ብቻ አይደለም ማስቀናትም በሽታ ነው ። ለማቃናት ሳይሆን ለማስቀናት የሚለፉ ሰዎች አሉ ። ማስቀናት የሚወዱ ሰዎች ፣ በማስደሰት ሳይሆን በማናደድ የሚያምኑ ናቸው ። በሰው ንዴት የሚደሰቱ ሲበዛ ራስ ወዳድ ናቸው ። ዉድ መሆናቸውን ለማሳየት ፣ ርካሽ መንገድ የሚጠቀሙ ብኩኖች ናቸው ። በማስቀናት ፍቅርን ለማጎልበት የሚጥሩ ጅሎች ናቸው ። ፍቅር በቅናት ይላላል እንጅ አይጠነክርም ። ቅናት በፍቅር ውስጥ የእርጎ ዝንብ ነው ። ልብን የሚበክል ባክቴሪያ ነው ።

ቅናትን በማስቀናት ጎትቶ ማምጣት ፣ ንጹህ ልብን መበከል ነው ። የተበከለ ልብ ደግሞ ከፍቅር ይልቅ ለጥላቻ ምቹ ነው ። የቅናትም የማስቀናትም መጨረሻ ጥላቻ ነው ። ሁለቱም የልብ በካይ ጋስ ( Carbon di oxide ) ናቸው ። ስለዚህ ለማቃናት እንጅ ለማስቀናት አንኑር ።

   በአርአያ ( Role model ) መቅናት ክፋት የለውም ። ይህ ቅናት በጎ ነው ። በሰው ልብ ውስጥ ክፋትን ሳይሆን ፣ ለስራ መነሳሳትን ( Motivation ) ነው የሚፈጥረው ። መጥፎው ቅናት ግን ለስራ ሳይሆን ለነገር ነው ሚያነሳሳው ። እኔ እንደሱ በሆንኩ ማለት እና እኔ ተከብሬ እርሱ በተዋረደ ማለት ይለያያል ። በጎ ቅናት ራስን ለማክበር መመኘት ነው ። መጥፎ ቅናት ደግሞ ሌላውን ለማዋረድ መጣር ነው ። በጎ ቅናት ከሰው እኩል ለመሆን መጣር ነው ። መጥፎ ቅናት ግን ከሰው ሁሉ በልጦ ለመገኘት መታገል ነው ። በሰው ጉብዝና በበጎ የቀና ሰው ፣ እንደሰውየው ጎበዝ ይሆናል ። በክፋት የቀና ሰው ግን ጎበዝ ሳይሆን ግብዝ ነው የሚሆነው ። በነገራችን ላይ በቅናት የሰውን ነገር የራስ ማድረግ አይቻልም ። ነገር ግን በበጎ ቅናት ካደረብን ፣ ቅናቱ በፈጠረው መነሳሳት ፣ ትጉ በመሆን የሰውን ሳይሆን ፣ የራስን ህልም ልክ እንደሌላው እውን ማድረግ ይቻላል ። በክፋት ግን የሰውን ነገር የራስ ለማድረግ ከጣርን ያለንን እናጣለን ።

 እንደ አልበርት አንስታይን የፊዚክስ ሊቅ ብሆን ብሎ መቅናት ችግር የለውም ። እንደ አልበርት አንስታይን ለምን እኔም እኩል ችሎታ አልተሰጠኝም ብሎ መቅናት ግን ትርፉ በሽታ ነው ። ምክንያቱም ህይወት አንተ ራስህን በትጋት ስታገኝ እንጅ የምታከብርህ ፣ በቅናት ስትንጨረጨር ዞር ብላ አታይህም ።

የስኬት ምስጥሩ ሰውን ማየት ሳይሆን ፣ በሰው ውስጥ ራስን ማየት ነው ። እዚች ምድር ላይ ሰውን በማየት ብቻ የከበረ የለም ። በጎ ቅናት በሰው ውስጥ ራስን ማየት ነው ። መጥፎ ቅናት ግን ከሰው ጋር ራስን ማነጻጸር ነው ። ከሰው መማር እንጅ በሰው መማረር አያዋጣም ። መማር ወይ ከሰው እኩል አልያም ከፍ ያደርገናል ። መማረር ግን በምንም ሂሳብ ከሰው እኩል አይደርገንም ። በጎ ቅናት መማር ነው ። መጥፎ ቅናት መማረር ነው ። ስለዚህ በበጎ እንቅና ፣ በክፋት ከመቅናት ግን እንጠንቀቅ ።

   ‘’ መቅናትም ማስቀናትም በሽታ ነው ፣ በበጎ መቅናት ግን መልካም እይታ ነው ። ‘’

Saturday, June 28, 2025

እይታ | Perception

                                                              ስንፍና

  ስንፍና እየቻሉ አለመስራት ነው ። የማይችሉትን አለመስራት ግን ስንፍና አይደለም ። ምክንያቱም የሰው ልጅ ሁሉን መስራት አይችልም ። ሁሉን ቻይ ፈጣሪ ብቻ ነው ። ደካማ ጎን የሌለው ፣ ጠንካራ ጎኑ ብቻ የሚነገርለት አካል ፈጣሪ ብቻ ነው ። የሰው ልጅ ግን ደካማ እና ጠንካራ ጎን አለው ። አንዱ ጠንካራ በሆነበት ሌላው ደካማ ሊሆን ይችላል ። ሌላው ጠንካራ በሆነበት አንደኛው ደግሞ ደካማ ነው ። በቃ ይህ የህይወት እውነታ ነው ። በአንድ ነገር ደካማ መሆን ግን ስንፍና አይደለም ። ስንፍና መስራት አለመቻል ብቻ ሳይሆን ፣ ምንም መስራት አለመቻል ነው ። መስራት እየቻሉ መለገም ፣ ማንበብ እየቻሉ ማሳበብ ፣ መድረስ እየቻሉ መቅረት ፣ መራመድ እየቻሉ መቆም ፣ መቆም እየቻሉ መቀመጥ ፣ መቀመጥ እየቻሉ መቆመጥ ነው ስንፍና ።

 ድክመት የተፈጥሮ ውጤት ነው ። ስንፍና ግን የምርጫ ውጤት ነው ። ሰው መርጦ ደካማ መሆን አይችልም ። መርጦ ግን ሰነፍ መሆን ይችላል ። ድክመትን ማሻሻል ይቻላል ፣ ማስወገድ ግን በፍጹም አይቻልም ። ስንፍናን ማስወገድ ግን ይቻላል ። ድክመትን ለማሻሻል ፈጣሪን መማጸን ግድ ነው ። ስንፍናን ለማስወገድ ግን ራስን ማሳመን በቂ ነው ። ድክመትን መቀበል እንጅ መቃወም አይቻልም ። ስንፍናን መቀበልም መቃወምም ይቻላል ። ጠንካራ ሰው ስንፍናን መቃወም የሚችል ነው ። በዚያው ልክ ድክመቱን አምኖ መቀበል የሚችል ነው ። ዳተኛ ሰው ግን ስንፍናን መቃወም አይችልም ። ድክመቱንም አምኖ መቀበል አይችልም ። ለሚያደርገው የስንፍና ድርጊት ሰበብ መፍጠር ነው የሚችለው ።

ለችግሩ መፍትሄ የማያጣ ሳይሆን ፣ ለስንፍናው ምክንያት የማያጣ ፍጥረት ነው ። ሰነፍ ማለት ደክሞ ሳይሆን አውቆ የተኛ ነው ። ’’ አውቆ የተኛን ቢቀሰቅሱት አይነቃም ። ‘’ ይል የለ ያገሬ ሰው ፣ ሰነፍ እንደዛ ነው ። እየቻለ የማያደርግ እያወቀ ዝም የሚል ነው ።

  ንግግር አለመቻል ስንፍና አይደለም ድክመት ነው ። መናገር እየቻሉ ዝም ማለት ነው ስንፍና ። በተፈጥሮ ንግግር ላይ ደካማ የሆነ ሰው ፣ በጥረት የንግግር ችሎታውን ማሻሻል ቢችልም ፣ በፍጹም አንደበተ ርቱዕ ሊሆን አይችልም ። አንደበተ ርቱዕ ካልሆንኩ ብሎ ከሚታገል ፣ ድክመቱን አምኖ ቢቀበል ይሻለዋል ። ‘’  Change the changeable, accept the unchangeable. ‘’ እንዳለው የህይወት ክህሎት አሰልጣኙ ፣ የሚለወጠውን መለወጥ ፣ የማይለወጠውን መቀበል የተሻለ ነው ። የሚችሉት ላይ አድምቶ መስራት ፣ የማይችሉትን ለሚችሉት አሳልፎ መስጠት ብልሀት ነው ። ሁሉን ካልቻልኩ ማለት ፣ ምንም አለመቻልን ነው የሚፈጥረው ። ምንም አለመሞከር ደግሞ ስንፍናን ነው የሚፈጥረው ። መሞከር ሁሉን ወደ መቻል ሳይሆን ወደ መቻል ነው የሚወስደን ። አለመሞከር ግን ወደ ምንም አልመቻል ነው የሚወስደን ። ስንሞክር የምንችለውን እናውቃለን ፣ የማንችለውን እንለያለን ። ያኔ ድክመትን ከስንፍና እናጠራለን ።

በሁሉም ነገር ላይ ጎበዝ መሆን አይቻልም ። በምንም ነገር ላይ ጎበዝ አለመሆን ግን እርሱ ስንፍና ነው ። ሰው ያለችሎታ አይፈጠርም ። ችሎታውን ማወቅ ግደታው ነው ። ምንም ችሎታ የሌለው ሰነፍ ነው ። ሁሉም ሰው የሚችለውን አለመቻልም ስንፍና ነው ።የሰው ልጅ ሁሉ መማር ማንበብ መጻፍ እንዲችል ተደርጎ ነው የተፈጠረው ። እኔ ትምህርት ንባብ ፅሁፍ አይሆነኝም ማለት ትልቅ ስንፍና ነው ። እኔ ስእል አይሆነኝም ማለት ይቻላል ። ምክንያቱም ስእል ልዩ ተሰጥኦ ይፈልጋል ። ለአንድነት የሚሰጥ ሳይሆን ለልዩነት የሚቸር ነው ። በደፈናው እኔ ትምህርት አይሆነኝም ማለት ግን ስንፍና ነው ።

   ችሎታ በሁለት ይከፈላል ። ለልዩነት የሚሰጥ እና ለአንድነት የሚሰጥ ችሎታ ነው ። ሁሉም ሰው የሚችለው ነገር የአንድነት ችሎታ ነው ። የተወሰኑ ሰዎች ሊያደርጉት የሚችሉት ነገር ግን ለልዩነት የተሰጠ ነው ። መናገር መቻል ለሁሉ የተሰጠ ነው ። አሳምሮ መናገር ግን በልዩነት የሚሰጥ ነው ። ቀላል ሂሳብን መስራት ሁሉም ሰው ይችለዋል ። ከባድ እና ውስብስብ ሂሳብን መስራት ግን ልዩ የተፈጥሮ ዝንባሌን ይጠይቃል ። መኪናን መንዳት ለሁሉም ሰው ይቻላል ። መኪናን መስራት ግን ሁሉም ሰው አይችለውም ። ስለዚህ የአንድነት ችሎታን ማጣት ስንፍና ነው ። የልዩነት ችሎታን ማጣት ግን ድክመት ነው ወይም ያለቦታ የመገኘት ውጤት ነው ። 

   ‘’ ለሚያምን ሁሉ ይቻለዋል ። ‘’ ይላል ታላቁ መጽሀፍ ። ለጣረ ሁሉ ይቻለዋል ግን አላለም ። ምክንያቱም ከጥረት እምነት ይበልጣል ። ሰው ሁሉን ማድረግ ባይችልም ፣ ሁሉን ማድረግ በሚችለው ፈጣሪ ፣ በእምነቱ ምንም ማድረግ ይችላል ። ይህ የሚሆነው ስለጣረ ስለለፋ ሳይሆን ስላመነ ነው ። እዚህ ጋር ከሰው ችሎታው በላይ እምነቱ በጣም ወሳኝ ነው ። ለዚህም ነው የእምነት ሰዎች ፣ የጥረት ሰዎች ብዙ የሚደክሙበትን ፣ በቀላሉ የሚያከናውኑት ።

 የሰው ልጅ ደካማ ጎኑ የሚሸፈነው በእምነት ነው ። ስንፍናው ግን በምንም አይሸፈንም ። ባይሆን በቅጣት ይወራረዳል ።

   አንዳንድ ነገሮችን ማድረግ አለመቻል ፣ ስንፍና ስላልሆነ ብዙ መጨነቅ ተገቢ አይደለም ። ሰው መጨነቅ ያለበት ማድረግ እየቻለ ባለማድረጉ ነው ። ምንም አለመጨነቅ ልክ አይደለም ለስንፍና ይዳርጋል ። በሁሉም ነገር መጨነቅም ልክ አይደለም ፣ ለአእምሮ ህመም ይዳርጋል ። ሰው የሚችለውን ለማድረግ በመጠኑ መጨነቅ አለበት ። የማይችለውን ለማድረግ ግን ማመን እንጅ መጨነቅ የለበትም ። የሚችለውን ለመስራት በመጨነቁ ስንፍናውን ያስወግዳል ። የማይችለውን ለማድረግ ማመኑ ፣ ድክመቱን አምኖ ለመቀበል ይረዳዋል ።

  ‘’ ስንፍና ልዩነትን መፍጠር አለመቻል ነው ። ድክመት ልዩነትን አምኖ መቀበል ነው ። ‘’                            

Monday, June 16, 2025

እይታ | Perception

                                                     

                              ራስን ማጣት

     

       ራስን ማጣት መልከ ብዙ ነው ። ሰው ራሱን የሚያጣበት ምክንያት ብዙ ነው ። ራስን ከሚያሳጡ ነገሮች መሀል አንዱ ስሜታዊነት ነው ። ስሜታዊነት ሰውን ሌላ ሰው የማድረግ አቅም አለው ። ሰው ሲቆጣ ሲያዝን ሲፈራ እና ሲደሰት ፣ ከነበረው ማንነቱ የተለየ ማንነትን ይላበሳል ። ለዚህ ነው ስሜታዊ የሆኑ ሰዎች ፣ ባህሪያቸው በቀላሉ የማይለይ ፣ ስብእናቸው ተለዋዋጭ እየሆነ የሚያስቸግረው ። ስሜታዊ ሰዎች ሲደሰቱ ሌላ ፣ ሲያዝኑ ሌላ ሰው ናቸው ። በቀላሉ ራሳቸውን ያጣሉ ። ሲጀመር ዋስትና ያለው ባህሪ ወይም ስብእና ስለማይኖራቸው ፣ እንደ እስስት በቀላሉ የመለዋወጥ ባህሪ ይኖራቸዋል ። ለእነርሱ ከባዱ ራስን ማጣት ሳይሆን ራስን ማግኘት ነው ። በስሜት ለመገንባት ብርቱ ናቸው ። የዚያኑ ያህል በንዴት ለማፍረስ ጎበዝ ናቸው ። ሆ ብሎ መስራት ወዲያው ደግሞ ሆ ብሎ ማበላሸት መለያ ባህሪያቸው ነው ። ባጭሩ በስሜታዊነት ራስን ማጣት እንጅ ራስን ማግኘት ፣ ወደ ራስ መመለስ አይኖርም ።

ሌላኛው ራስን የሚያሳጣ ነገር ዝለት ነው ። ዝለት ሲባል የመንፈስም የአካልም ነው ። በእርግጥ የአካል ዝለት ፣ ያን ያህል የባህሪ ወይም የስብእና መዛባትን አይፈጥርም ። የመንፈስ ዝለት ግን ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ፣ የባህሪ መረበሽን ፣ የስሜት መቃወስን ፣ የስብእና መዛባትን ያስከትላል ። ዝለት ቀላሉን ነገር ከባድ ያደርጋል ። ተግባቢ የነበረውን ነጭናጫ ያደርገዋል ። ትእግስተኛ የነበረውን ቁጡ ያደርገዋል ። ትሁት የነበረውን ትእቢተኛ ያደርገዋል ። ብርቱ የነበረውን ደካማ ያደርገዋል ።

 በዝለት ውስጥ ስራ በጥረት እንጅ በጥራት አይሰራም ።በዝለት ውስጥ ለመጣር የተወሰነ አቅም ይኖራል ፣ ለማጣራት ግን በቂ አይሆንም ። ምክንያቱም ዝለት አቅላችንን ያስተናል ፣ ራሳችንንም ያሳጣናል ። ዝለት የስራ መብዛት ውጤት ነው ። ከአቅም በታች መስራት ዘልዛላ ያደርጋል ። ከአቅም በላይ መስራት ደግሞ ለዝለት ይዳርጋል ። ስለዚህ ሰው ራሱን ላለማጣት አቅሙን ማወቅ አለበት ። በአቅሙ ልክ መስራት አለበት ።  

   ራሳቸውን የሚያጡ ሰዎች ብዙ ጊዜ ራሳቸውን የማያውቁ ሰዎች ናቸው ። ራስን ማወቅ የራስን አቅም ስሜት ድክመት ጥንካሬ እና ሀሳብ ወይም አላማ ማወቅ ነው ። እነዚህን የራሱ የሆኑትን ነገር ያላወቀ ሰው ፣ በስራ ቦታ ፣ በማህበራዊ ግንኙነት ውስጥ በቀላሉ ራሱን ያጣል ። ምክንያቱም ችግር ሲገጥመው የሚታገስለት አላማ የለውም ። ድክመቱን አውቆ ነገርን  በማሸሽ ወይም በመሸሽ ፣ ከራሱ አያርቅም ። ራሱን ለማሸነፍም ጠንካራ ጎኑ ምን እንደሆነ መለየት አይችልም ። በመጨረሻም ራሱን በማጣት ብዙ ነገሩን ያጣል ። በእርግጥ ራስን ከማጣት በላይ ከባድ ችግር የለም ። ሰው ያለውን ሁሉ ቢያጣ ችግር የለውም ። ከባድ ችግር የሚፈጠረው ግን ራሱን ያጣ እለት ነው ።       

   ራስን ማጣት የነበረንን መጥፎ ነገር ማጣት ሳይሆን ፣ ያለንን ጥሩ ነገር ማጣት ነው ። ሰው ያለውን መጥፎ ነገር ቢያጣማ መልካም ነው ። ያኔ ራሱን አጣ ሳይሆን ፣ ራሱን አገኘ ነው የሚባለው ። የነበረውን ቁጣ ትቶ ፣ ያልነበረውን ትእግስት ቢላበስ እሰየው ነው ። ትእቢቱን ረስቶ ትህትናን ከያዘ ፣ ይህ መልካም ነው ። ስስትን ትቶ ደግ መሆን ከጀመረ ፣ ያኔ ወደ ጥንተ ተፈጥሮው ፣ ወደ ሰውነቱ ተመለሰ ማለት ነው ። ራስን ማጣት መልካም ነገርን ማጣት ነው ። ትእግስትን ትህትናን እምነትን እውነትን ደግነትን ማጣት ነው ። ሰው እንደ ድሮ  አይደለህም ተለውጠሃል ፣ ወደራስህ ተመለስ የሚባለው ፣ የነበረውን መልካም ነገር ሲያጣ ነው ።

   አንዳንድ ሰው ገንዘብ ሲያገኝ ትህትናውን ያጣል ። በነገራችን ላይ ማግኘት የሚያስከትለው ማጣት በሽታ ነው ። ሰው ራሱን ከሚያጣ ገንዘብን ቢያጣ ይሻለዋል ። ምክንያቱም ገንዘብ ሲያገኝ ራሱን የሚያጣ ከሆነ ፣ ገንዘብ መልሚያው ሳይሆን መጥፊያው ይሆናል ። ማግኘት ማንነትን ሊያጠነክር እንጅ ሊያፈርስ አይገባም ። ሰው በገንዘቡ የተሻለ ነገር ለመስራት ፣ ራሱን ላለማጣት በተጠንቀቅ መጠበቅ ይኖርበታል ። ገንዘብ ራስን ከሚያሳጡ ነገሮች ዋነኛው ነው ።

   ስልጣን ሲያገኙ ጨካኝ የሚሆኑ አሉ ። መራራት እስኪያቅታቸው ድረስ ራሳቸውን የሚያጡ አሉ ። ከስልጣን በፊት ሰው የነበሩ ፣ ስልጣን ሲሰጣቸው ወደ አውሬነት ይቀየራሉ ። ለሰው የሚራሩ ምርጥ የነበሩ ፣ በሰው የሚጨክኑ ምጥ ይሆናሉ ። በስልጣን ምክንያት ራሳቸውን ያጡ ፣ ብዙ የድርጅት የማህበረሰብ የሀይማኖት እና የሀገር መሪዎች አሉ ። የነበራቸውን መልካም ነገር አጥተው ፣ ያልነበራቸውን ክፉ ነገር የታጠቁ ብዙ ናቸው ። በስብእናቸው ይመሩናል ተብለው ተመርጠው ፣ በስልጣን ምክንያት ስብእናቸውን በማጣት ፣በትክክል የመሩን ሳይሆን በትግል የመረሩን ብዙ ናቸው ። በስልጣናችሁ ክቡር ፣ በመሪነታችሁ ምስጉን ለመሆን ፣ ስልጣን ስታገኙ ራሳችሁን ላለማጣት መጠንቀቅ አለባችሁ ። ያልነበራችሁን እውቀትና ልምድ የምታገኙበት እንጅ ፣ የነበራችሁን መልካም ስብእና የምታጡበት መሆን የለበትም ።

   እውቀት ሲያገኙ ራሳቸውን በደምብ ማወቅ ሲገባቸው ፣ በተቃራኒው ራሳቸውን የሚያጡ ብዙ ናቸው ። መሃይምነት ከምሁርነት ይሻላል የሚያስብሉ ፣ እውቀት ሲያገኙ ራሳቸውን ያጡ ምሁራን ብዙ ናቸው ። እውቀት ሰይጣን ያደረጋቸው ብዙ አዋቂዎች አሉ ። ለሰው በእውቀታቸው መድሃኒት ሳይሆን ፣ መርዝ እስከ መስራት የደረሱ ብዙ ናቸው ። መፍትሄ ሳይሆን ችግር የፈበረኩ ብዙ ናቸው ። አዋቂነት አውሬነት የሆነባቸው ተማራማሪዎች ቁጥራቸው ቀላል አይደለም ። በእውቀታቸው ዓለምን የጦርነት ማእከል ያደረጉ ፣ የፖለቲካውን አለም የሴራ ማምረቻ እንዲሆን የቀረጹ ፣ ትምህርት ቤቶችን የዝሙት ማስፋፊያ ያደረጉ ብዙ ናቸው ። እውቀት ሰውን ወደ ሰውነት እንጅ ወደ ሰይጣንነት ሊወስደው አይገባም ። ወደ ራሱ ሊመልሰው እንጅ ራሱን ሊያሳጣው አይገባም ። ለዚህ ደግሞ እውቀትን መምረጥ ተገቢ ነው ። ፈጣሪ የፈቀደውን መልካሙን ሁሉ ማወቅ ፣ ክፉውን መተው አስፈላጊ ነው ።

      ‘’ ለማግኘት ራስን ማጣት ልክ አይደለም ። ከክፉ ነገር ራስን መጠበቅ ፣ ማጣት ሳይሆን ራስን ማግኘት ነው ። ‘’    

Friday, June 6, 2025

እይታ | Perception

                                        ራስን ይቅር አለማለት

 

  ራስን ይቅር አለማለት የከባድ ጸጸት ውጤት ነው ። በነገራችን ላይ ለሰው ይቅርታ ከማድረግ በላይ ፣ ለራስ ይቅርታ ማድረግ ከባድ ነው ። ምክንያቱም እዚህ ጋር ጥፋት የራስ ነው ። በደል ማድረስ ህመምን ከባድ ያደርገዋል ። የሰው ልጅ ህሊናውን አሽከር ካላደረገ በስተቀር ፣ ጥፋት በመስራቱ የሚደርስበት ህመም ቀላል እይደለም ። አብዝተው ለሰው የሚጨነቁ ሰዎች ፣ ጥፋት ከሰሩ ለራሳቸው ይቅርታ ለማድረግ በጣም ይቸገራሉ ። በተለይ ሰው በእነርሱ ምክንያት ብዙ ከተጎዳ ፣ የሚደርስባቸውን የህሊና ስቃይ መሸከም ይከብዳቸዋል ። ለሰው የሚጨነቁ ሰዎች ፣ ለሰው የሚሳሱ ሲበዛ ስስ ፍጥረቶች ናቸው ። ሰው ተቸግሮ እያዩ ማለፍ አይችሉም ። ምናልባት ገንዘብ እያዩ ጥለው ሊያልፉ ይችላሉ ። ምክንያቱም እነርሱ ለሰው እንጅ ለገንዘብ አይሳሱም ። ገንዘብን እያዩ ማለፍ ካልፈለጉም ፣ ለራሳቸው ብለው ሳይሆን መርዳት የሚፈልጉት ሰው ስላለ ይሆናል ።

   ለሰው የሚጨነቁ ሰዎች ፣ ሰው እንዳይጎዳባቸው በጣም ጥንቃቄ ያደርጋሉ ። ጥንቃቄያቸው ከፍቅር ይመነጫል ። በእርግጥ አንዳንድ ሰዎች አሉ ፣ ሰው እንዳይታመም የሚጨነቁት ፣ ለሰውየው ሳስተው ሳይሆን ፣ ስራቸው እንዳይታጎል ወይም የሚያገኙትን እንዳያጡ ነው ። እነዚህ ግን ትላንት ላወቁትም ፣ እድሜ ልክ ለሚያውቁትም ያላቸው ስሜት ተመሳሳይ ነው ።  ለስራቸው ወይም ለጥቅማቸው ሳይሆን ፣በቃ እንዲሁ ለሰው በጣም ይሳሳሉ ። ለእነርሱ ማንም ይጎዳ ፣ ሰው እስከሆነ ድረስ ይጨነቃሉ ። የተቸገረ ሰው ሲያዩ ሀዘናቸው ጥልቅ ነው ።

  በእነርሱ ምክንያት ሰው ችግር ላይ ወድቆ ቢያዩ ፣ ሀዘናቸው እጅግ ከባድ ነው የሚሆነው ። በጸጸት ምክንያት ለራሳቸው ይቅርታ ለማድረግ አቅም ያጣሉ ። ይቅርታ መጠየቅ አይከብዳቸውም ነገር ግን ራሳቸውን ይቅር ለማለት ፣ ከባድ ፈተና ይሆንባቸዋል ። ልባቸው ስስ ስለሆነ ይቅርታ ማድረግ ለእነርሱ በጣም ቀላል ነው ። ሰው ሆኖ ጥፋት የማይሰራ ፣ ስህተት የማይፈጽም የለም ። የእነርሱን ህሊና አንቆ የሚይዘው ግን ፣ ጥፋቱ የሚፈጥረው ጉዳት ነው ። ለዚህ ደግሞ የሰዎችን ጉዳት ለመቀነስ ፣ በቻሉት መጠን ስህተት ላለመስራት ጥረት ያደርጋሉ ። ከሰሩም ይቅርታቸው በቃል ብቻ የሚወሰን ሳይሆን ፣ በተለያየ ነገር ሰውን ለመካስ ይሞክራሉ ። አልያ በቃል ይቅርታ በመጠየቅ ብቻ ህሊናቸው እረፍት አያገኝም ። በጸጸት ምክንያት ራሳቸውን ሊጎዱ ይችላሉ ።

   ለራስ ይቅርታ ማድረግ ሰውነትን መቀበል ድክመትን ማመን ነው ። ይቅርታ ለማድረግ መቸገር ግን ፍጹም ለመሆን መታገል ነው ። ሰው ደግሞ በስራው ፍጹም ሊሆን አይችልም ። ሆን ብሎ ስህተትን መስራት ተንኮል ነው ። ሰውን ለመጉዳት አስበው አቅደው ጥፋት ወይም ስህተት የሚሰሩ አሉ ። ይህ ሰውነት ሳይሆን አውሬነት ነው ። ሰው ሆኖ አለመሳሳት አይቻልም ። ሆን ብሎ ስህተት መስራት ግን ሰው መሆን አይደለም ። ስምንተኛ ክፍል የስፖርት መምህራችን ‘’ Mistake is humanity, again mistake is stupidity ( ስህተት መስራት ሰብዓዊነት ነው ስህተትን መድገም ግን ደደብነት ነው ። ) ‘’ ይል ነበር ። ነገር ግን ማወቅ ያለብን ፣ አውቀንም ሆነ ሳናውቅ ስህተት መስራታችን ፣ ራስን ይቅር ከማለት ሊከለክል አይገባም ።

ሰው ስህተትን የማይደግመው ለራሱ ይቅርታ ማድረግ ሲችል ነው ። አልያ ስህተትን በሌላ ስህተት እየቀየረ ይኖራል ። ጥፋትን በሌላ ጥፋት እየተካ ይቀጥላል ። ለራሱ ይቅርታ ማድረግ ካቃተው ፣ ላለመሳሳት ከመጠን በላይ ይጨነቃል ። ላለመሳሳት ሲጨነቅ የበለጠ ስህተት ይሰራል ። በጸጸት ብዛት ስህተትን ማስቆም አይቻልም ። ጥፋትን መግታት አይታሰብም ። ስህተትን ማመን ፣ ለጥፋት ሀላፊነት መውሰድ ፣ ድክመትን መቀበል ነው ፣ ስህተትንም ጥፋትንም ባለበት የሚያስቆመው ።

   ይቅርታ እረፍት ነው ። መንፈስን የሚያድስ ሀይል ነው ። ያልታደሰ መንፈስ ደካማ ነው ። ስለዚህ ስህተትን ለመደጋገም ቅርብ ነው ። መንፈስ ሲታደስ ብርቱ ይሆናል ። ሰው ውስጡ ሲታደስ ስህተትን ላለመድገም አቅም ያገኛል ። ሰው የሚታደሰው በይቅርታ ስለሆነ ፣ ለራስም ለሌላውም ይቅርታ ማድረግ ወሳኝ ነው ። ሰዎች ልክ እንደተፈጥሮ ሀብት ( Natural resource ) በሁለት ይከፈላሉ ። ታዳሽ እና ታዳሽ ያልሆኑ በመባል ። የይቅርታ ሰዎች ታዳሽ ናቸው ። የበቀል ሰዎች ደግሞ ታዳሽ ያልሆኑ ፍጥረቶች ናቸው ። ታዳሽ የተፈጥሮ ሀብቶች ዘላለማዊ እንደሆኑ ሁሉ ፣ የይቅርታ ሰዎችም ዘላለማዊ ናቸው ። ታዳሽ ያልሆኑ የተፈጥሮ ሀብቶች ጊዜያዊ ( limited ) ናቸው ። በተመሳሳይ ታዳሽ ያልሆኑ የበቀል ሰዎች ጊዜያዊ ናቸው ። የይቅርታ ሰዎች ህይወትን የሚቀጥሉ ሀይሎች ናቸው ። የበቀል ሰዎች ደግሞ ወይ ህይወትን የሚጨርሱ አልያም ለራሳቸው የሚያልቁ ሀይሎች ናቸው ። ህይወትን የሚቀጥሉ በሰው ልብ ውስጥ ለዘላለም ይኖራሉ ። ህይወትን የሚያቃጥሉ ከሰው ልብ በቀላሉ ይሰረዛሉ ። ስለዚህ ህይወትን ለመቀጠል የይቅርታ ሰው እንሁን ።

   ከልብ ለመሆን ለራስ ይቅርታ ማድረግ ተገቢ ነው ። ለመበርታት ለመታደስ ይህ ግድ ነው ። በጸጸት ብዛት መኖር ራስን ማቃጠል ነው ። ዘላለማዊ ሳይሆን ጊዜያዊ መሆን ነው ። ይህ ደግሞ ራስን በራስ መግደል ነው ። ስህተት ሰውኛ መሆኑን አምነን ፣ ለራስ ይቅርታ በማድረግ አዲስ ሰው እንሁን ። ለምድር ታዳሽ ሀይል ፣ ለሰዎችም ለራሳችንም ህይወትን ቀጣይ እንሆን ዘንድ ፣ ለራስም ለሌላም ይቅርታ ማድረግን እንለማመድ ። የቱንም ያህል ስህተት ብንሰራም ፣ ለራስ ይቅርታ የማድረግ ሞራል ልናጣ አይገባም ።

    ‘’ ስህተትን ላለመድገም ለራስ ይቅርታ ማድረግ ቁልፍ ነው ። ‘’            

Saturday, May 31, 2025

እይታ | Perception

                                              ፍትህ

  ፍትህ የስራ ውጤት ነው ። ሰው የስራውን ካላገኘ ፍትህ የለም ማለት ነው ። ፍትህ ካለ ጥሩ የሰራ ይሸለማል ። መጥፎ የሰራ ደግሞ ይቀጣል ። በተቃራኒው ፍትህ ከሌለ ፣ መጥፎ የሰራ አይቀጣም ። ጥሩ የሰራ አይሸለምም ። አለመሸለም ብቻ አይደለም ፣ ጥሩ በመስራቱ ሊቀጣ ይችላል ። ፍትህ ከሌለ የዘሩትን ማጨድ አይቻልም ። መታጨድ እንጅ ማጨድ አይኖርም ። መልካም የሰሩ የዘሩትን ማጨድ ባይችሉም ፣ ክፉዎች ግን ያልዘሩትን ያጭዳሉ ። ያላበሰሉትን ይበላሉ ። ያልሰጡትን ይወስዳሉ ። ያልተንከባከቡትን ፍሬ ይመገባሉ ። ፍትህ በሌለበት ትጋት ከንቱ ነው ። ምክንያቱም ሰርቶ መከበር አይቻልም ። ሰርቆ መከበር ነው የሚቻለው ። ጥሮ ማሳካት እጅግ ከባድ ነው ። አጭበርብሮ ማሳካት ግን ቀላል ነው ። ያለፍትህ ስራ ዋጋው ዝቅ ይላል ። ሴራ ግን ዋጋው ከፍ ይላል ።

ለስራ የሚተጉ ፍትህ ያሰፍናሉ ። ለሴራ የሚተጉ ደግሞ ፍትህ ያዛባሉ ። ለመስራት የሚተጉ ፍትህን ያረጋግጣሉ ። ለመስረቅ የሚተጉ ፍትህን ይረግጣሉ ። መስረቅም መስራትም ትጋት ይፈልጋሉ ። ልዩነቱ መስረቅ በአጭር ጊዜ ውስጥ ብዙ ገንዘብ ያስገኛል ። የደስታ ሰገነት ላይ ያስቀምጣል ። ግን ደግሞ የሀዘን አዘቅት ውስጥ መክተቱ ኣይቀርም ። ስራ በአንድ ጊዜ ብዙ ገንዘብ አያስገኝም ። ደስታውንም በመጠኑ ፣ ገንዘቡንም በልኩ እያሳደገ ነው የሚሄደው ። ሰው በመስረቁ የሰውን ደስታ ይቀማል ። ለዚያ ነው ደስታው ከልክ በላይ የሚሆነው ። የሚገርመው ሀዘኑም ከልክ በላይ መራር ነው ። ምክንያቱም የሚሸከመው ሀዘን የራሱን ብቻ ሳይሆን ፣ የሰውንም ጭምር ነው ።

ሰው በመስራቱ ግን ሀዘኑም ደስታውም በልኩ ነው ። ምክንያቱም የሚቀማው ደስታ የለም ። የሚሸከመውም ተጨማሪ ህዘን የለም ። እርሱ ፍትሐዊ ነው ።

ለመስራት እንጅ ለመስረቅ ፣ ለማስደሰት እንጅ ለማሳዘን ፣ ፍትህን ለማረጋገጥ እንጅ ለማዛባት አትትጉ ። ትጋት ደስ የሚለው ከቅንነት ጋር ነው ። ቅንቅንነት አይመቸውም ። ስኬት የትጋት ውጤት ነው ። ሰው ለፍትህ ከተጋ ፣ ስኬት የሀቀኞች ትሆናለች ። ፍትህን ለማዛባት ከተጋ ግን ፣ ስኬት የአጭበርባሪዎች ትሆናለች ። ፍትህ አለ ማለት የተጉ ስኬትን ይጎናጸፋሉ ፣ የአጭበረበሩ ይቀጣሉ ፣ የማይለፉ ሰነፎች ደግሞ ከሁለቱ ይማራሉ ። ፍትህ ከሌለ ስኬትም ቅጣትም የለም ። ስኬት ከሌለ አርአያ አይኖርም ። ቅጣት ከሌለ መማርያ አይኖርም ። ንቁ ሰው ከአርአያው ይማራል ። ያልነቃው በቅጣት ይማራል ። ፍትህ አለ ማለት በሁለቱም መንገድ መማር አለ ማለት ነው ። ከሌለ ግን መማረር እንጅ መማር አይቻልም ።

ፍትህ ለእውነት መቆም ነው ። በፍትህ ዘንድ ወገንተኝነት አይሰራም ። ጥፋተኛ ዘመድ ስለሆነ ከፍርድ አያመልጥም ። ሌባ ልጅ ስለሆነ ከቅጣት አይድንም ። ወንጀለኛ ወዳጅ ስለሆነ ከእስር አይተርፍም ። ፍትህ ስጋ ብሎ አያዳላም ። ለወዳጅ ብሎ ፍርደ ገምድል አይሆንም ። ለልጅ ብሎ እውነትን አይገፋም ። ለፍትህ መኖር ማለት ለእውነት እየቆሙ ፣ መከራን እየታገሱ መኖር ነው ። እውነት የለም ማለት ፍትህ የለም ማለት ነው ። ለፍትህ የእውነት መኖር ግድ ነው ። እውነት እና ፍትህ የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታ ናቸው ።

ለዚህ ነው ለመርማሪ እውነቱን ማወቅ ከባድ ፈተና የሚሆንበት ። የፍትህ መሰረቱ እውነት ስለሆነ ፣ ፍትህን የሚረግጡ እውነት እንዳትታወቅ ፣ ባለ በሌለ አቅማቸው ይታገላሉ ። ፍትህን ለማስፈን የሚተጉ ፣ እውነቱን ለማግኘት ከባድ ትግል ውስጥ ይገባሉ ። ‘’ እውነት እና ንጋት እያደር ይጠራል ። ‘’ እንዲባል ፣ እውነቱ ግን መታወቁ አይቀርም ። ፍትህን የነበሩት ቢያጡት ፣ የሚመጡት ማግኘታቸው አይቀርም ።

‘’ ለፍትህ እውነት እርቃኑን መሆን አልበት ። ‘’ አለች ፣ የስራና ክህሎት ሚኒስትር ወ/ሮ ሞፈሪያት ካሚል ። እውነትነት አለው ። ብዙውን ጊዜ እውነት ፣ ወይ ፍቅርን አሊያም ጥላቻን መልበሱ አይቀርም ። ጥላቻን ከሚለብስ ፍቅርን ቢለብስ የተሻለ ነው ። እውነት ጥላቻን ከለበሰ ጉዳቱ የከፋ ይሆናል ። በጥላቻ የሚነገር እውነት ፣ ሰው ውስጥ ሀይለኛ ቁጣን ይቀሰቅሳል ። ፍትህን ለማስፈን ከመጣር ይልቅ ለበቀል ያነሳሳል ። ፍትህ አላማው ማስተማር እና መካስ ነው ። በቀል ክፋትን በክፋት መመለስ ነው ። የፍትህ መጨረሻው ሰላም እና እርቅ ነው ። የበቀል መጨረሻው ግን መጨራረስ ነው ። እውነትን ጥላቻ ማልበስ ፣ ነገርን ወደ በቀል መውሰድ ነው ። ስለዚህ ከቻልን እውነትን ፍቅርን እናልብስ ። ካልሆነ እርቃኑን ይሁን ።

ለሰው ልጅ የሚሻለው ግን ፣ ያለምንም ጥርጥር እውነትን ፍቅርን ማልበስ ነው ። ያኔ ፍትህ ይረጋገጣል ፣ እንደ ሀብት ከትውልድ ትውልድ ፣ ሲሸጋገር የሚመጣን በቀል ማስቆም ይቻላል ። Genetic code ( የዘረ መል ውርስ ) እስኪመስል ፣ በቀልን በደም የሚዋረስ ህብረተሰብ አለ ። በቀል ለትውልድ የሚያወርሱት ሀብት ሳይሆን እርግማን ነው ።

 ምንም ጥቅም የሌለው ርካሽ ተግባር ነው ። የፈሰሰን ውሀ ለማፈስ መታገል ነው ። ይሄ ደግሞ የራስን ውድ አላማ መዘንጋት ነው ። ህልምን ቀብሮ ራእይን አፈር ድሜ ማብላት ነው ። በትላንት ታሪክ ዛሬን ለመኖር መታገል ነው ። ትላንት ለዛሬ ግብዓት እንጅ ግብ አይደለም ። በቀለኞች ግን ለዛሬ ወይም ለነገ የሚሆን ግብ የላቸውም ። የእነርሱ ግባቸውም ህልማቸውም ትላንት ነው ። የወላጅ ክፉ ሀሳብ ማስፈጸም ነው ራእያቸው ። ይሄ ሁሉ የሚሆነው እውነት ጥላቻን ሲለብስ ነው ። እውነት ፍቅርን ሲለብስ ግን በተቃራኒ ነው የሚሆነው ። ወደ ይቅርታ ይመራል ። ሰው የወላጁን ሳይሆን የራሱን ህልም እንዲኖር ይረደዋል ። የራሱ ግብ እንዲኖረው አስተሳሰቡን ይቀይረዋል ። ዛሬና ነገን በአግባቡ እንዲጠቀም ያግዘዋል ። በቀለኛ ሳይሆን ፍትሀዊ እንዲሆን ያስገድደዋል ። ከምንም በላይ ጎጅውን ጥላቻ ሳይሆን ፣ ጠቃሚውን ፍቅር እንዲያስቀድም ያደርገዋል ። ፍትህ የሚረጋገጠው በፍቅር እንጅ በጥላቻ አይደለም ። በቀል ፍትህ አይሆንም ። ፍትህ ይቅርታ ማድረግ ማስተማር መቅጣት እና መካስ ነው ።  

 

 ‘’ እውነትን ፍቅር አልብሱት ፣ ያኔ ፍትህ ይረጋገጣል ። ‘’     

Thursday, May 29, 2025

እይታ | Perception

                                       ከራስ መጣላት

 ከራስ መጣላት የራስን እውነት አለመቀበል ነው ። የገዛ ስሜታችንን መካድ ነው ። በጠቅላላው ራስን አለመቀበል ነው ። የሰውን ልጅ ከራሱ እንዲጣላ ምክንያት የሚሆኑ ነገሮች ብዙ ናቸው ። በሰዎች ዘንድ ክብርን ለማግኘት ሲሉ ከራሳቸው የሚጣሉ አሉ ። እነዚህ ሌሎችን ለማሳመን ወሬ በመፍጠር የሚተካከላቸው የለም ። በወሬ ጤፍ ይቆላሉ ጉም ይዘግናሉ ። ያለን ነገር ሳይሆን ፣ የሌለን ነገር መፍጠር ይችላሉ ። ተውሰው መልበስ ይችላሉ ። ሰርተው መልበስ ግን አይችሉም ። ብራንድ ጫማ ማድረግ ይችላሉ ፣ መግዛት ግን አይችሉም ። የሰው ሁሉ የእነርሱ ነው ። እነርሱ ግን የሚረባ አንድም ነገር የላቸውም ። የሚለብሱት የሚጫሙት የሚዘንጡት ሁሉ በሰው ነው ። በቃ እነርሱ ምንም የሌላቸው ባዶ ናቸው ። ሰው ባዶነቱን አምኖ መቀበል ካቃተው ፣ ምንም ነገር ሊኖረው አይችልም ። ቦዶነቱን አምኖ መቀበል የቻለ ግን ፣ በአዲስ ነገር ባዶነቱን መሙላት ይችላል ። ምክንያቱም ራሱን መቀበል የቻለ ትሁት ነውና ።

ራሱን የተቀበለ ሰው ለመማር ለመስራት ለማወቅ ዝግጁ ነው ። ይህ ደግሞ ባዶ ከመሆን ይጠብቀዋል ። ራስን መቀበል መልካም ነገርን ከሌሎች ለመቀበል ልብን ክፍት ያደርጋል ። መቀበል ከሌለ መለወጥ አይኖርም ። አቀባበላችን ግን ለውጣችንን ይወስነዋል ። የምንቀበለው ጥሩ ነገር ከሆነ ፣ ለውጣችን አዎንታዊ ይሆናል ። የምንቀበለው ግን መጥፎ ከሆነ ፣ ለውጣችን አሉታዊ ይሆናል ። ከራሱ የተጣላ ሰው ሀሳብ መቀበል አይችልም ። ቢቀበልም ጥሩውን ሳይሆን መጥፎውን ነው ። ስጦታ መቀበል እና መዋስ ወይም መበደር ግን ይችልበታል ።

በሰው ዘንድ ለመከበር ብሎ ከራሱ የተጣላ ፣ ትልቁ ችሎታው መዋስ ወይም መበደር ነው ። ምክንያቱም ከራሱ የተጣላ ሰው ይሉኝታ ቢስ ነው ። መስራት ያሳፍረዋል ግን መዋስ ያኮራዋል ። ተናንሶ ከመስራት ይልቅ ፣ በሰው አንሶ ላለመታየት የሚያደርገው ጥረት እጅግ ይገርማል ። ስለዚህ ሰው ለመለወጥ ራሱን መቀበል ባዶነቱን ማመን አለበት ። መዋሸት ማቆም አለበት ። ውሸት የራስን ፍሬ የሚቀብር ክፉ አረም ነው ። አረም ውሸቱን ካልነቀለ ፣ ሰው አለሙን መመልከት አይችልም ። በእጁ ያለውን ወርቅ ማስተዋል አይችልም ። በእጁ የያዘው ተራ ፣ በሌላ ሰው እጅ ያለው ተራራ መስሎ ይታየዋል ። ለመከበር ብላችሁ ከራሳችሁ አትጣሉ ። እውነተኛ ክብርን ለማግኘት ከፈለጋችሁ ፣ ከራሳችሁ ታረቁ ማንነታችሁን ተቀበሉ ።

ሌላው የሰውን ልጅ ከራሱ የሚያጣላው ከወዳጅ መቀያየም ነው ። በተለይ የሚያፈቅሩት ሰው ሲያስቀይም በጣም ከባድ ነው ። የተበደለው/ችው ግለሰብ የገዛ የራሱን ስሜት ይከዳል ። ከልብ የሚወዱትን ወይም የሚያፈቅሩትን ሰው ፣ ልባቸው እየፈለገ እነርሱ ግን በአፋቸው አልወደውም ወይም አልወዳትም ይላሉ ። ከፍቅር ይልቅ ጥላቻ እንዳላቸው ለማሳወቅ ፣ አሁንስ አይኑን አያሳየኝ በማለት ይምላሉ ። አያሳየኝ ብለው አፋቸውን ሞልተው ይምላሉ ፣ ነገር ግን በደለ የተባለው ፍቅረኛ ወይም ግለሰብ ሲመጣ ልባቸውን በፍቅር ይሞላሉ ። ያንን ሰው እየናፈቁ መቼም አይናፍቀኝም ይላሉ ። እውነቱ ግን ‘’ ማሽላ በውስጥ እያረረች ከላይ ትስቃለች ‘’ እንደሚባለው ፣ አፋቸው ልባቸውን ይከዳል እንጅ ስር የሰደደ ናፍቆት በውስጣቸው አለ ። እነዚህ ሰዎች ሰው ፊት እየሳቁ ፣ ቤት ገብተው እርር ብለው የሚያለቅሱ ፣ አሳዛኝ ፍጡራን ናቸው ። በፍቅር ምክንያት ከራስ መጣላት በሽታ ነው ።

 ስሜትን አፍኖ መያዝ ፣ ጠንካራ መስሎ ለመታየት ከራስ ጋር መታገል ፣ ላለመሸነፍ በውጥረት ውሎ በጭንቀት ማደር ። ይሄ ሁሉ እየወደዱ መጥላት የሚያመጣው መዘዝ ነው ። ከራስ መጣላት የሚፈጥረው ዱብዳ ነው ። ስለዚህ እየወደዱ ከመጥላት በይቅርታ ሰላም መፍጠር ። በእብሪት አልሸነፍ ባይ ሆኖ ከራስ ከመጣላት ፣ በትህትና እርቅ ማውረድ የተሻለ ነው ። ያኔ ከራስም ከሰውም ሰላም መሆን ይቻላል ።

ከራሳቸው ከሚጣሉ ሰዎች መሀል ፣ ችግር ከራሳቸው የሚያጣላቸው ሰዎች እጅግ ያሳዝናሉ ። እነዚህ ሰዎች ወደው ሳይሆን ተገደው ነው ከራሳቸው የሚጣሉት ። ለመኖር ሲሉ ያላመኑበትን ነገር ያደርጋሉ ። መስጠት እየፈለጉ ይከለክላሉ ። ማዳን እየፈለጉ ይገድላሉ ። መውደድ እየፈለጉ ይጠላሉ ። መቅረብ እየፈለጉ ይርቃሉ ። ማግኘት እየፈለጉ ያጣሉ ። መናገር እየፈለጉ ዝም ይላሉ ። ማልቀስ እየፈለጉ ይስቃሉ ። እነዚህ ሰዎች በአብዛኛው ፣ በክፉዎች መሀል የሚኖሩ ሩሩ ናቸው ። ጨካኝ ሌባ እንዳለ ሁሉ ሩሩ ሌባ አለ ። ክፉ ባለስልጣን እንዳለ ሁሉ ሩሩ ባለስልጣንም አለ ። አስቸጋሪ ሰራተኛ እንዳለ ሁሉ መልካም ሰራተኛ አለ ። ችግሩ ያ አይደለም ። ክፉው ከመልካሙ ሲበዛ ነው ችግር የሚፈጠረው ። መልካሞች ከክፉዎች ከበዙ ፣ ችግር ይቀረፋል እንጅ አይፈጠርም ። ከራስ መታረቅ እንጅ ከራስ መጣላት አይኖርም ። ክፎዎች ሲበዙ ግን ከራስ መጣላት ይኖራል ።

 ክፉ ከመልካም ይልቅ ጉልበት ሲኖረው ፣ መልካም ሰዎች አቅም በማጣት ከራሳቸው ይጣላሉ ። ግፍ ሲፈጸም መናገር እየቻሉ ዝም ይላሉ ። ሰው ሲገደል ማዳን እየቻሉ እያለቀሱ ይቀብራሉ ።

ደሀ ሲበደል መድረስ እየቻሉ ይሸሻሉ ። በክፉዎች ፊት አብረው ስቀው ፣ ቤት ገብተው ግን እርር ብለው ያለቅሳሉ ። እድሜ ልክ የህሊና እረፍት አጥተው ይኖራሉ ። ሆን ብሎ ከራስ መጣላት እና ተገዶ ከራስ መጣላት ይለያያል ። ሆን ብለው ከራሳቸው የተጣሉ ፣ አምነው ስለሆነ ጫናው ለእነርሱ ቀላል ነው ። ተገደው ከሆነ ግን ስለማያምኑበት ጫናው እጅግ ከባድ ነው ። በክፉዎች መሀል ቅን ሆኖ መገኘት ከባድ ነው ። በመልካሞች መሀል ቅንቅን ሆኖ መገኘትም ከባድ ነው ። ህይወት ከመልካሞች ጋር ደስ ትላለች ። ምክንያቱም ከራስ መጣላት የለም ።  ከክፉዎች ጋር ግን ትመራለች ። ምክንያቱም ከራስ መጣላት ሁሌም አለ ። የሰውን ልጅ ከራሱ የሚያጣላው ፣ አንደኛው እና ዋነኛው ክፋት ነው ።

 

‘’ ከራስ መጣላት ራስን መካድ ነው ። ራስን መካድ ደግሞ አርቴፊሻል ህይወት መምራት ነው ። ‘’                        

Tuesday, May 27, 2025

እይታ | Perception

                                   እምነት ወይስ እውነት

   ያለ እምነትም ያለ እውነትም መኖር ከባድ ነው ። እውነት ለነጻነት ፣ እምነት ለአብሮነት እጅግ አስፈላጊ ናቸው ። እምነት በእውነት ላይ ሲመሰረት ፣ ሰው በህይወቱ ሙሉነት ይሰመዋል ። እምነት በጥቅም ላይ ከተመሰረተ ግን ሰው በህይወቱ የሙሉነት ስሜት ይጎድለዋል ። በውሸት ማመን እርሱ የቁም ሬሳ መሆን ነው ። በውሸት ማስመሰል እንጅ መሆን አይቻልም ። ማስመሰል እውነተኛ ደስታን ሊሰጥ አይችልም ። መሆን ነው እውነተኛ ደስታን የሚፈጥረው ። እውነተኛ ደስታ ከእውነት እንጅ ከውሸት በፍጹም ሊገኝ አይችልም ። ብዙዎች ደስታን በውሸት ለማጣጣም ይሞክራሉ ። ነገር ግን እውነታው ደስታ ምን እንደሆነ በቅጡ አይረዱትም ። ምክንያቱም ውሸት የሚፈጥረው ደስታ ርካሽ እና ጊዜያዊ ነው ። እውነት የሚፈጥረው ደስታ ግን ውድ እና ዘላለማዊ ነው ።

  ውሸት እና እምነት ህይወትን እርካታ ቢስ ያደርጋሉ ። እውነት እና እምነት ግን የህሊና እርካታን ይለግሳሉ ። ሰው በውሸት ሲኖር ፣ ደስታን በራሱ መፍጠር አይችልም ። ደስታን ከሌሎች ለማግኘት ይለፋል ይደክማል ፣ ይወጣል ይወርዳል ። ደስታን ከሌሎች ማግኘት ከባድ ነው ። ከራስ ማግኘት ግን ቀላል ነው ። ደስታን ከራሱ የሚያገኝ ፣ በራሱ ደስታን መፍጠር የሚችል ነው ። እንደዚህ አይነት ሰው ደግሞ ሰውን ለማስደሰት ብሎ አይሰራም ፣ ነገር ግን ሰውን የሚያስደስት ስራ መስራት ይችላል ። ደስታን መፍጠርም መጋራትም ማጋራትም ይችላል ። ምክንያቱም ስለእውነት በእውነት ነው የሚኖረው ።

  እምነት በማስመሰል ወይም በውሸት ላይ ሲመሰረት ፣ እውነትን አይፈታተንም ።

ሰው ለብዙ ዓመት አዝሎ የኖረው እምነት ፣ ውሸት እንደሆነ ያወቀ እለት ፣ ያንን እምነት ለመተው ብዙ አይከብደውም ። ምክንያቱም ውሸት እውነትን አይበልጥም ። በውሸት የተፈጠረ እምነት ፣ በእውነት ፊት አቅም የለውም ።

     ለፍቅር እውነትን መደበቅ ግን እውነትን የሚፈታተን እምነትን ይፈጥራል ። ፍቅር የሚፈጥረው እምነት በጣም ጠንካራ ነው ። ሰው ካጣው እውነት በላይ ያገኘው ፍቅር ሲበልጥበት ፣ እውነትን አምኖ ለመቀበል ይቸገራል ። ይህንን እውነት ከሚያውቅ ፣ ባያውቅ ምርጫው ይሆናል ። ሰዎች አንዳንዴ በጣም ለሚወዳቸው ሰዎች ስለፍቅር ሲሉ ፣ እውነተኛ ማንነታቸውን ደብቀው አብረው ይኖራሉ ። እነርሱን ላለማጣት ፈርተው እውነቱን ሳይናገሩ ይዘው ይቆያሉ ። በእርግጥ  ለጥቅም ሲሉ እውነትን የሚደብቁ ክፉዎች አሉ ። እነዚህ ግን እንደ እነርሱ አይደሉም ፣ ጥቅምን ላለማጣት ሳይሆን ሰውን ላለማጣት ሲሉ ነው ፣ እውነትን የሚደብቁት ። ብዙ ጊዜ እንደዚህ አይነት ነገር ፣ በወላጅ እና በልጅ መሀል ሲከሰት ይስተዋላል ። የስጋ ዝምድና የሌላቸው ወይም ( Biological ) ያልሆኑ ወላጆች ፣ የአብራካቸው ክፋይ ( Biological )  ያልሆነ ልጅ ያሳድጋሉ ። አብዛኛውን ጊዜ ወላጆች እውነቱን ከመናገር ይልቅ ፣ እውነቱን መደበቅ ይመርጣሉ ። ግን በሚገርም የወላጅነት ፍቅር ያሳድጋሉ ። ይህ ፍቅር በልጅ ውስጥ ጠንካራ እምነትን ይፈጥራል ። ይህ እምነት በውሸት ብቻ እንደተፈጠረው እምነት ደካማ አይደለም ። ፍቅር የፈጥረው ሀይለኛ እምነት ነው ። ለእውነት በቀላሉ የማይረታ ብርቱ እምነት ነው ።

     ለሰው ልጅ ፍቅር የፈጠረው እምነት ፣ ከተደበቀበት እውነት ይበልጥበታል ።  

ምክንያቱም በውሸት ቢኖርም ያገኘው ፍቅር የእውነት ነው ። ያጣው እውነት ካገኘው ፍቅር አይበልጥበትም ። ለዚህም ነው ‘’ ፍቅርን ያልሰነቀ እውነት የሞተ ነው ። ‘’ የሚባለው ። ሰው አንዳንዴ እውነትን ከማጣቱ በላይ ፣ እውነትን ማወቁ ይጎዳዋል ። የሚጎዳን እውነት ማወቅ ህይወትን ያናጋል ። የሚጠቅም እውነትን ማወቅ ግን ህይወትን ያስተካክላል ። ስለዚህ ሁሉን እውነት ማወቅ አይጠቅምም ። የነበረንን ጥሩ ነገር የሚያሳጣ እውነት ባይታወቅ ይሻላል ። ያልነበረንን ጥሩ ነገር የሚያመጣ እውነት ግን ሊታወቅ ግድ ነው ። ፍቅርን የሚያሳጣ እውነት ባለበት ተደብቆ ቢቀር ይሻላል ። ፍቅርን የሚጨምር እምነት ግን ፣ ካለበት ተፈትሾ ቢገኝ መልካም ነው ። አብሮነትን ፣ መተሳሰብን ፣ ሰላምን የሚያደፈርስ እውነት መታወቁ አይጥቅምም ። አብሮነትን ፣ መተሳሰብን ፣ ሰላምን የሚፈጥር እና የሚያጠነክር እውነት ተቆፍሮም ቢሆን መገኘት አለበት ። ልክ እንደ ክርስቶስ መስቀል ሱባኤ ሊያዝለት ይገባል ። በግራ በኩል እንደተሰቀለው ወንበዴ መስቀል ፣ ተገኘም አልተገኘም ፍቅርን ሰላምን መተሳሰብን የሚያሳጣ እውነት አያስፈልግም ።

 እውነት ነጻነት ነው ። ግን ሁሉም እውነት ነጻነትን አይለግስም ። ነጻነትን የሚያሳጣ እውነት አለ ። ጤናን የሚያቃውስ እውነት አለ ። ይህንን እውነት መተው የተሻለ ነው ። የሚያበራ እውነት እንጅ የሚያጨልም እውነት መታወቁ አስፈላጊ አይደለም ። ቢታወቅ የሚጎዳ እውነት አስተሳሰብን ይቀይራል ፣ በአዎንታ ሳይሆን በአሉታ ። እምነትን ይበርዛል ። ቢታወቅ መጥቀምም መጉዳትም የማይችል እውነት አለ ። ይህ እውነት ቢታወቅ የሚጨምረው ነገር የለም ። ባይታወቅም የሚቀንሰው ነገር የለም ። ኖረም አልኖረም ዋጋ ቢስ ነው ። ለዚህ እውነት ትኩረት መስጠት ጅልነት ነው ።

  ቢታወቅ የሚጠቅም እውነት ግን ህይወትን ቀያሪ ነው ፣ በአሉታ ሳይሆን በአዎንታ ። ለምሳሌ ፈጣሪን ፣ ሀይማኖትን ፣ ሳይንስን ፣ ቴክኖሎጂን ፣ የሚጠቅሙ ማህበራዊ እሴቶችን ፣ ደጋግ ሰዎችን ማወቅ ፣ ህይወትን በመልካም መንገድ ይለውጣል ። ከዚህም በተጨማሪ የኔ የምትሉትን ሰው ማወቅ እፎይታን ይሰጣል ። ቤተሰብን ፣ ዘመድን ፣ ወዳጅን ማወቅ ያስደስታል ። እውነት ሀዘንም ደስታም ነው ። ከሚያሳዝን እውነት የሚያስደስት እውነት ይሻላል ። የሚያስደስት እውነት ውስጡ ፍቅር አለ ። ስለዚህ ከሚያሳዝን እውነት ፣ ያለ እውነት በፍቅር የተፈጠረ እምነት ይበልጣል ። የሚያስደስት እውነት ግን ፍቅርን የያዘ ስለሆነ ፣ እርሱ የሚፈጥረው እምነት ፣ ከሁሉም አይነት እምነት ይበልጣል ። ምክንያቱም እምነት ሁሉ በእርሱ መንገድ ነው መቀረጽ ያለበት ።  ጠቃሚ እውነትን ከፍቅር ጋር በመያዝ ። 

   ‘’ እምነት ከሚጎዳ እውነት ይበልጣል ። ከሚጠቅም እውነት ግን ያንሳል ። ‘’                              

Saturday, May 24, 2025

እይታ | Perception

                                            ክብር

    ‘’ ለአንዳንዱ ክብሩ የእሱነቱ መገለጫ ነው ። ለአንዳንዱ ደግሞ ክብሩ ሰውነቱ ነው ። ‘’ አለች ሰላም ተስፋዬ በማርትሬዛ ፊልም ላይ ። ይህን የተናገረችው በልብስ ምክንያት ከባድ ወቀሳ ደርሶባት ነው ። በነገራችን ላይ ልብስ የሰው ልጅ የማንነቱ መገለጫ እንጅ ማንነቱ ግን አይደለም ። ሰውነቱን ከፍም ዝቅም አያደርግም ። ቆሻሻ የለበሰ የአእምሮ ህመምተኛ ሰው ከመባል የሚከለክለው የለም ። ምናልባት ሰው ከሚለው መጠሪያ በፊት ፣ እብድ የሚል ተቀጽላ ከመጨመሩ በስተቀር ። ተቀጽላ ደግሞ ዋናውን የሰውን ማንነት ወይም ሰውነትን የመፋቅ አቅም የለውም ። ቅጽል ወይ ያኮስሳል አልያም ያገናል ። ሰውን ቀይሮ እንስሳ ወይም ግኡዝ ፍጥረት ሊያደርግ አይችልም ። ሰው ንጹህም ለበሰ ቆሻሻ ያው ሰው ነው ።

   ሰውን ከቆሻሻ ልብስ በላይ ክብሩን የሚያሳጣው ቆሻሻ አስተሳሰቡ ነው ። ሰው በንጹህ ልብስ ቆሻሻ ማንነቱን ለመደበቅ ከሚሞክር ፣ በንጹህ አስተሳሰብ ቆሻሻ ማንነቱን ቢያጸዳ መልካም ነው ። ገላን አጥቦ ማጽዳት ቀላል ነው ። አስተሳሰብን አጥቦ ማጽዳት ግን በጣም ከባድ ነው ። ከመነቸከ አስተሳሰብ የመነቸከ ልብስ ይሻላል ። የመነቸከን ልብስ አጥበነው ካቃተን አውጥተነው እንጥላለን ። የመነቸከን አስተሳሰብ ግን አጥበን ለማጽዳትም ፣ አውጥተን ለመጣልም በጣም አስቸጋሪ ነው ። ስለዚህ ሰው በልብሱ ከሚከበር በአስተሳሰቡ ቢከበር የተሻለ ነው ። ልብስ የሚያስከብረው በሩቁ ነው ። በርቀት በልብሱ ያከበሩትን ሲቀርቡት በአስተሳሰቡ ይንቁታል ። በልብስ የበለጸገ በስብእና የረከሰ ማንነት ክብሩ ጊዜያዊ ነው ። ዘላቂ ክብር ያለው በመልካም አስተሳሰብ የሚገነባ ውብ ስብእና ውስጥ ነው ። ልብስ ሳይሆን በዋናነት ልብ ነው ወሳኙ ።

   በቆሻሻ ልብ ላይ ጸዳል ልብስ መልበስ ፣ በአሮጌ አቁማዳ አዲሱን ወይን ማኖር ነው ። ሁለቱ ደግሞ አይስማሙም ። ወይ ወይኑ ይበላሻል አልያም አቁማዳው ይቀረደዳል ። ስለዚህ የሚሻለው አዲሱን ወይን በአዲስ አቁማዳ ማኖር ነው ። ሰውነትን ባከበረ ማንነት ላይ ንጹህ ልብስ ማኖር ነው ፣ ለሰው ልጅ ዘላቂ ክብር የሚሆነው ። እውነተኛ ክብር ከውጭ ሳይሆን ከውስጥ ነው የሚመነጨው ። በሚታይ ነገር ለመከበር መሞከር ሞኝነት ነው ። ከሚታይ ነገር ይልቅ የማይታይ ነገር ከፍ ያለ ዋጋ አለው ። ለዚህም ነው ከሚታየው ልብስ በላይ ፣ የማይታየው ልብ የሚያስከብረው ። ሰው ለመታየት ሳይሆን ሆኖ ለማሳየት ነው መኖር ያለበት ። ለመታየት መልበስ በቂ ነው ። ለማሳየት ግን ከመልበስ ባሻገር ፣ መስራት ወይም መኖር ግድ ይላል ። የሰው ልጅ እውነተኛ ማንነት ያለው ደግሞ ፣ በመልበስ ውስጥ ሳይሆን በመኖር ውስጥ ወይም በመስራት ውስጥ ነው ። በልብስ አምሮ የሚታይ ፣ ምናልባት እላዩ የሚያምር ውስጡ የሚያማርር ፍጥረት ሊሆን ይችላል ። እላዩ ስላማረ ከሰውነት ከፍ አይልም ። አማራሪ በመሆኑ ግን ከሰውነቱ ዝቅ ባይልም ፣ በማንነቱ ላይ ሌላ ተቀጽላ ይለጠፋል ፣ አስመሳይ የሚል መገለጫ ።

   ጥሩ መልበስ ልክ አይደለም ወይም አያስፈልግም ማለት አይደለም ። ጥሩ መልበስ ራስን መንከባከብ ክብርንም መጠበቅ ነው ። ነገር ግን ሰው ራሱን መጠበቅ ያለበት ፣ በሰው ለመታየት ብቻ  መሆን የለበትም ። ለራሱ ለጤናውም ጭምር መሆን አለበት ።

 በሰው ለመታየት ሲል ጤናውን ምቾቱን ማጣት የለበትም ። ኢኮኖሚው እስኪቃወስ ፣ ኑሮው ኢስኪናጋ አምሮ ለመታየት ብዙ መድከም አይኖርበትም ። ማማር ከጤና አይበልጥም ። መዘነጥ ከአእምሮ ሰላም አይልቅም ። ዋናውን በማጣት የሚገኝ ትርፍ ዋጋ ቢስ ነው ። ዋናውን በመያዝ የሚገኝ ትርፍ ግን ጠቃሚ ነው ። መኖር ከሌለ መቀናጣት አይቻልም ። ቅንጦት ኖረም አልኖረም መኖር ይቻላል ። ለመቀናጣት መኖር ግድ ነው ። ለመኖር ግን መቀናጣት ግዴታ አይደለም ። ሰው ኖረ የሚባለው ስለተቀናጣ ሳይሆን ፣ ጤናውን እና የአእምሮ ሰላሙን መጥበቅ በመቻሉ ነው ። ለአስፈላጊው ነገር ሲባል ፣ ቅንጡውን ነገር መተው እንጅ ፣ ለቅንጡ ነገር ሲባል አስፈላጊውን ነገር ማጣት ተገቢ አይደለም ። በእርግጥ ልብስ አስፈላጊ ነገር ነው ። ነገር ግን የልብስ መሰረታዊ ጥቅሙ ፣ ገላን መሸፈን እንጅ ገላን ማሳየት አይደለም ። ገላን ለማሳየት ሲሉ ብዙዎች ጤናቸውን እስከማጣት ደርሰዋልና ። የሚመቸንን መልበስ አስፈላጊ ነው ። የማይመቸንን መልበስ ግን በሽታ ነው ። የምንችለውን መልበስ ተገቢ ነው ። የማንችለውን መልበስ ግን ቅንጦት ነው ። የሚያምርብን ልብስ ለጤና ጥሩ ነው ። የማያምርብንን ግን መልበስ ለጤና ጠንቅ ነው ። ልብስ ገላን ሲሸፍን ክብርም ውበትም ነው ። ግን ለመከበር አጉል መልበስ ክብር ያሳጣል ።

 ሰውን እኩል የሚያደርግ ልብስ ደንብም ነው ክብርም ነው ። የተማሪዎች ዩኒፎርም ፣ የሰራተኞች የስራ ልብስ ፣ የወታደሮች እና የፖሊሶች የደንብ ልብስ የሚያስከብር እናም ክብር የሚገባው ሊዩ ልብስ ነው ። እነዚህን ልብሶች መልበስ መታደል ነው ።

ነገር ግን በልብስ እከብራለው ባይ ለነዚህ ልብሶች ክብር የለውም ። ምክንያቱም ከሰው እለያለው ባይ ነው ። እሱን ከሰው የሚለየው እንጅ አንድ የሚያደርገው ነገር አይመቸውም ። በእርግጥ ሰው ከሰው ይለያያል ። በሌላ በኩል ከብዙሃኑ አንድ የሚያደርገው ፣ የሚጋራው ነገር ብዙ ነው ። ሁሉም ሰው ሊኖረው በሚችለው ነገር ልዩ ልሁን ማለት አያስከብርም ። ከሌላው በሚለየን ነገር ላይ መስራት ግን ያስከብራል ። ሰውን ከሰው የሚለየው ደግሞ ስራው እንጅ ልብሱ አይደለም ። ፈረንጀቹ ‘’ ( First impression is last impression ) ’’ ይላሉ ። የፈርስት ኢምፕረሽን አንዱ መለኪያ አለባበስ ነው ። እዚህ ጋር አለባበስ ለስራ ያለንን ክብር ነው የሚያሳየው ። ስራን ለማክበር መልበስ ያስከብራል ። ከሰው ሁሉ ለመለየት ወይም ለሰው ብሎ መልበስ ግን አያስከብርም ።

        ‘’ ክብር ልብስ ውስጥ ሳይሆን ልብ ውስጥ ነው የሚገኘው ። ‘’                               

Wednesday, May 21, 2025

እይታ | Perception

                                                   አውቆ መሸነፍ 

     አውቆ መሸነፍ ያማል ። ሰው በማስተዋል ስህተት ሲሰራ ክፉኛ ይጎዳል ። ባለማስተዋል የሚሰራ ጥፋት ብዙ ጫና የለውም ። አውቆ መሸነፍ የትህትና ውጤት ነው ። ለትእቢተኞች አውቆ መሸነፍ የሞት ያህል ከባድ ነው ። ሰው አውቆ የሚሸነፈው በዓላማ ነው ። ያ አላማ ደግሞ መልካም እንጅ ክፉ መሆን የለበትም ። ለክፋት ሆን ብለው የሚሸነፉ ፣ ዓላማቸው ማታለል ነው ። ለመልካም ነገር አውቀው የሚሸነፉ ፣ ዓላማቸው ማስተካከል ወይም ማረም ነው ። ለማታለል አውቆ መሸነፍ ተንኮለኝነት ነው ። ለማስተካከል አውቆ መሸነፍ ግን ጥበበኛነት ነው ። አውቆ መሸነፍ ዓላማው መልካም ከሆነ ፣ ነገርን በጥበብ የማብረድ መንገድ ነው ። ዓላማው መጥፎ ከሆነ ግን ፣ ክፉኛ ሰውን የመጉዳት ስልት ሆኖ ያገለግላል ። ለተንኮለኞች ሆን ብሎ መሸነፍ ፣ መንደርደሪያ ወይም መደራደሪያ ነው ። ሌላውን ለማሳመን የሚውል አሻጥር ነው ። ለጥበበኞች ግን ክፉውን መሻገሪያ እና ማሻገሪያ ነው ።

    በአውቆ መሸነፍ ውስጥ ያለ ዝቅታ ፣ በማሸነፍ ከሚገኝ ከፍታ ይበልጣል ። አውቆ ተሸናፊ በመጀመሪያ ተሸናፊ ፣ በመጨረሻ ግን ድል አድራጊ ነው ። መነሻው ማጣት ነው ፣ መዳረሻው ግን ሁሉን ማግኘት ነው ። ሰው አውቆ የሚሸነፈው አቅም ስላጣ አይደለም ፣ ሰላም ላለማጣት ነው ። ፍቅርን ለማስፈን ፣ እውነትን ለማሳወቅ እናም አብሮነትን ለማጽናት ነው ። መሸነፍ ባይኖር አብሮነት አይኖርም ። አሸንፋለው ባይ በበዛበት ቦታ ፣ ህብረት የሚባል ሀሳብ ፣ ሀሳብ እንጅ በፍጹም ተግባር ሊሆን አይችልም ። በተለይ አውቀው የሚሸነፉ ትሁታን በሌሉበት ።

ለሰላም ሆን ብለው የሚሸነፉ መሪዎች ያስፈልጋሉ ። ለፍቅር አውቀው የሚሸነፉ ምሁራን ሊኖሩ ግድ ይላል ። ለእውነት እጅ የሚሰጡ ባለጸጎች ሊበዙ ይገባል ። ለታማኝነት የሚንበረከኩ ባለሞያዎች ሊጠነክሩ ግድ ይላል ። ሀገር ሰላም ፍቅር መተሳሰብ እንዲሰፍንባት ።

     ሰው አልሸነፍ ባይ መሆን ያለበት ለችግር እንጅ ለሰላም መሆን የለበትም ። ለጠላት እንጅ ለወዳጅ መሆን የለበትም ። ለጥላቻ እንጅ ለፍቅር መሆን የለበትም ። ለውሸት እንጅ ለእውነት መሆን የለበትም ። ለሰላም ለፍቅር ለእውነት ለወዳጅነት የሚሸነፉ ፣ ምንም ይሁን ምን መጨረሻ ላይ ድል የእነርሱ ነች ። እነርሱ እየታመሙ የሚፈውሱ ፣ እያለቀሱ እንባ የሚያብሱ ፣ እየወደቁ የሚያነሱ ፣ እየተዋረዱ የሚያስከብሩ ፣ እያጡ የሚያስገኙ ሩህሩህ እና ጀግና ናቸው ። አውቀው የሚሸነፉ ትሁታን ሩህሩህም ጭምር ናቸው ። ሩህሩህ ስለሆኑ ሰውን የመረዳት አቅማቸው ከፍ ያለ ነው ። ሰውን በጥልቀት መረዳት መቻላቸው ነው ፣ ለመሸነፍ ዝግጁ ያደረጋቸው ። መሸነፍ ውስጥ ፍቅር ሰላም እውነት እና ህብረት አለ ። አልሸነፍ ባይነት ግን እነዚህን ውድ የህይወት እሴቶች ያሳጣል ።

ለችግር አልሸነፍ ባይነት መንፈሰ ጠንካራነት ነው ። ለእውነት አልሸነፍ ባይነት ግን ግትርነት ነው ። ለመከራ አልሸነፍ ባይነት አይበገሬነት ነው ። ለምክር አልሸነፍ ባይነት ግን ንቀት ነው ። ለፈተና እጅ አልሰጥም ባይነት የሞራል ልእልና ነው ። ለፍቅር አልገዛም ባይነት ግን የሞራል ውድቀት ነው ። ለሁሉም ነገር አልሸነፍ ባይነት ኢ ሞራላዊ ያደርጋል ። ለፍቅር አውቆ መሸነፍ ግን የስብእና ከፍታ የሞራል ልእልና ነው ። በድርቅና ከማሸነፍ በፍቅር መሸነፍ የተሻለ ነው ። በግትርነት ከማሸነፍ በእውነት መሸነፍ ልቆ መገኘት ነው ።

አውቆ መሸነፍ ዓለምን ከጦርነት አውድማነት ፣ የሰው ልጅን ከአሰቃቂ ሞት እና ችግር ይታደጋል ። ዛሬ አለማችን ላይ ያለውን የሩሲያ እና የዩክሬን ጦርነት ብንመለከት ፣ ሌላ የምንም ውጤት አይደለም ፣ የአልሸነፍ ባይነት መዘዝ ነው ። ለባርነት አልሸነፍ ባይነት መልካም ቢሆንም ፣ ለሰላም እጅ አልሰጥም ባይነት ግን ራስወዳድነት ነው ። ራስ ወዳዶች አልሸነፍ ባዮች ናቸው ። ለክብራቸው ጥግ ድረስ ዋጋ ይከፍላሉ ። ለሌላው ክብር ግን ደንታም የላቸውም ። ክብራቸው ከተነካ ዓለም ዶግ አመድ እስክትሆን ይዋጋሉ ። ራስ ወዳዶች ክብራቸውን የሚያጡለት ነገር ከሰውነት ውጪ ነው ። ለሰብአዊነት ቦታ የላቸውም ። ለህሊና አይገዙም ። ህሊና ሲጮህባቸው በአልኮል ያደነዝዙታል ። ያለ የሌለ ሀይላቸውን ተጠቅመው ማሸነፍ እንጅ ፣ መሸነፍ የሚለው ቃል በመዝገበ ቃላት ውስጥ እንዲገኝ አይፈልጉም ። ስለዚህ በእነርሱ ምክንያት የሚራብ የሚጠማ የሚጎሳቆል የሚፈናቀል የሚንከራተት ሰብአዊ ፍጥረት ግድ አይሰጣቸውም ።

    ለእውነት ለፍቅር ለሰላም መሸነፍ እረፍት ነው ። አለመሸነፍ ግን እረፍት ማጣት ነው ። በማሰቃየት የሚገኝ እረፍት የለም ። በማታለል ውስጥ እፎይታ ሊኖር አይችልም ። አልሸነፍ ባይነት ማታለልን ማሰቃየትን ፣ ለማሸነፍ ስልት አድርጎ ይወስዳል ። አውቆ መሸነፍ ግን በስቃይ ውስጥ በማለፍ ፣ ለራስም ለሌላውም ሰው እረፍት መሆን ነው ።

ከማሸነፍ አውቆ መሸነፍ ከባድ ነው ። ማሸነፍ ሰው ላይ መስራት ነው ። መሸነፍ ግን ራስ ላይ መስራት ነው ። ሰው ሰውን ማረጋጋት ብዙ አይከብደውም ። ራሱን በራሱ ማረጋጋት ግን በጣም ይከብደዋል ። የሰውን ንዴት ለመቆጣጠር ጎበዝ ነው ፣ ነገር ግን የራሱን ንዴት ለመቆጣጠር ግን ሰነፍ ነው ። አውቆ መሸነፍ ራስን ማራጋጋት ይጠይቃል ። ንዴትን የመቆጣጠር ጥበብን ይፈልጋል ። አውቆ ተሸናፊ ራሱን ማረጋጋት ፣ ንደቱን መቆጣጠር የሚችል የስሜት ብስለት ባለቤት ነው ። ማሸነፍ ስኬት ነው ። መሸነፍ ደግሞ ሰብአዊነት ነው ። ሰውን ማሸነፍ ብቻ ሰውና ክቡር አያደርግም ። ለህሊናው ያልተሸነፈ መቼም ቢሆን አሸናፊ አይደለም ። ምክንያቱም ትክክለኛ ማሸነፍ ያለው ለህሊና መሸነፍ ውስጥ ነው ። ሰውነትም የሚኖረው ለህሊና መሸነፍ ውስጥ ነው ። አውቆ መሸነፍም ለህሊና የመገዛት ውጤት ነው ።

   ‘’ አውቆ መሸነፍ ለሰላም መማረክ ፣ ለፍቅር እጅ መስጠት ፣ ለእውነት ክብር መስጠት ፣ ለህሊና መገዛት ነው ። ‘’     

Sunday, May 18, 2025

እይታ | Perception

                                     አጉል ድፍረት

     አንድ ወጣት ነው ፣ ፖሊስ ጣቢያ ፊት ለፊት ፣ ከጣቢያው አጥር ጥግ ሽንቱን ይሸናል ። በጣም ነው የሚገርመው ፣ ህግን በሚያስከብር አካል ፊት ስርዓት አልበኛ መሆን ፣ ይህ አጉል ድፍረት ነው ። አጉል ድፍረት ንቀትም ነው ። ህግን መጣስ ድፍረት የሚመስላቸው ሰዎች አሉ ። ነገር ግን ህግን መጣስ ሳይሆን ፣ ህግን ማክበር እናም ማስከበር መቻል ነው ትክክለኛው ድፍረት ። ሰዎች እንደ ስብእናቸው እና አስተሳሰባቸው ድፍረታቸው ይለያያል ። ሰው ለመግደል የሚደፍሩ እንዳሉ ሁሉ ፣ ሰው ለማዳን ደፋር የሆኑ አሉ ። አዲስ ነገር ለመስራት የሚደፍሩ አሉ ። አዲስ ነገር ለመስረቅ ደፋር የሆኑም ብዙ አሉ ።

   ከሰው ጋር ለመጣላት በጣም ደፋር የሆኑ አሉ ። ሰው ፈርቶ ዳር ይዞ የሚመለካተቸውን ሁለት ወጠምሻዎችን ፣ ለማስታረቅ የማይፈሩ ደፋር ግን ጥበበኞች አሉ ። ለመልካም ነገር መድፈር ፣ ድፍረትን ትክክል ያደርገዋል ። ለመጥፎ ነገር መድፈር ፣ እርሱ አጉል ድፍረት ነው ። አጉል ድፍረት ጥፋት ነው ። ትክክለኛ ድፍረት ግን ልማት ነው ። ለመዋሸት መድፈር ስህተት ነው ። እውነትን ለመናገር መድፈር ግን ልክ ነው ። በእርግጥ ሁሉንም እውነት ማፍረጥረት ትክክል አይደለም ። እርሱ አጉል ድፍረት ባይሆንም ፣ የጅል ድፍረት ነው የሚሆነው ። መነገር ያለበትን እውነት መናገር ፣ መነገር የሌለበትን እውነት መያዝ መቻል ነው ትክክለኛ ድፍረት ። ይልቅ እውነቱን ከመናገር ፣ ዝምታ ትክክለኛ እና ትልቅ ድፍረትን ይጠይቃል ።

እዚህ አለም ላይ ምስጢር በማውጣት ከተገደሉት በላይ ፣ ምስጥር በመያዝ ህይወታቸውን ያጡ ይበዛሉ ቢባል ማጋነን አይሆንም ። ፊልምም ፣ ልቦለድም ፣ የገሀዱ አለም እውነታም ይህን  ነው የሚያንጸባርቁት ።

     ውሸት መናገር አጉል ድፍረት ነው ። ምክንያቱም ሰው ውሸት ሲናገር ፣ ሰውን ብቻ አይደለም የሚዋሸው ፣ የገዛ ህሊናውን እና ፈጣሪውን ጭምር ነው ። በተለይ ሰውን ለመጉዳት አስቦ መዋሸት አጉል ድፍረት ብቻ ሳይሆን ጭካኔም ነው ። ሰው ሰውን ለማዳን ቢዋሽ ፣ በሂደቱ ሳይሆን በውጤቱ ምክንያት ይመሰገናል ። ሰውን ለመጉዳት ሲዋሽ ግን ፣ ሂደቱም ውጤቱም አስከፊ ስለሆነ ፣ በፈጣሪም ሆነ በሰው ዘንድ ክፉኛ ያስወቅሰዋል ። ለመዋሸት ደፋር የሆኑ ሰዎች አሉ እዚህ ምድር ላይ ፣ እነርሱም አስመሳዮች ናቸው ። አስመሳዮች ለመዋሸት ምንም አያንገራግሩም ። አስመሳይነት ለትወና ጥሩ ብቃት ( Good quality) ነው ። ለህይወት ግን መጥፎ ባህሪ ( Bad quality )  ነው ። ለትወና ግብዓቱ ፣ ለኑሮ ግን ግብዓተ መሬቱ ነው አስመሳይነት ።

      ለመዋሸት ድፍረት ማግኘት ትንሽነት ነው ። ለእውነት ግን ደፋር መሆን ጀግንነት ነው ። አጉል ድፍረት ከራስ ጋር ያጣላል ። ሰው የሌለውን አለኝ ፣ ያልሆነውን ነኝ የሚለው በአጉል ድፍረት ነው ። ገንዘብ ሳይኖረው አለኝ የሚል ፣ እውቀት ሳይኖረው አዋቂ ነኝ ብሎ የሚኮራ ፣ ውስጡ በትእቢት ተሞልቶ በአንደበቱ ትሁት ነኝ የሚል ፣ ከራሱ የተጣላ እና አጉል ደፋር የሆነ ሰው ነው ። ውሸት ከራስ ያጣላል ፣ አጉል ድፍረት ከሰውም ከራስም ያጋጫል ። ትክክለኛ ድፍረት ራስን መምሰል ነው ። የሆኑትን ማመን ያልሆኑትን መተው ነው ።

  ራስን መምሰል ከጸጸት ያድናል ። ከአጉል ድፍረትም ይገላግላል ። ራስን መምሰል ከሰው ሊያጋጭ ይችላል ። ከራስ ጋር ግን በፍጹም አያጋጭም ። ራሳቸውን የሆኑ ሰዎች ሁሌም ከራሳቸው ጋር ሰላም ናቸው ። ከሰዎች ጋር ግን በማያምኑት እና በማይቀበሉት ሀሳብ እና ድርጊት ምክንያት ሰላም ላይሆኑ ይችላሉ ። የሰላም መነሻው ከራስ መታረቅ ነው ። ከራሱ የታረቀ ደግሞ ከሰው መታረቅ ብዙ አይከብደውም ። ራሳቸውን የሆኑ ሰዎች ከራሳቸውም ከሰው ለመጣላት ሳይሆን ለመታረቅ ደፋር ናቸው ። ከራሳቸው የተጣሉ ሰዎች ግን ፣ ለመታረቅ ፈሪ ለመጣላት ደፋር ናቸው ። ምክንያቱም ከራሳቸው የተጣሉ ሰዎች ፣ ልባቸው ለይቅርታ ዝግ ነው ። ራሳቸውን የሆኑ ሰዎች ግን ልባቸው ለይቅርታ ክፍት ነው ። ይቅር ለማለትም ፣ ይቅርታ ለመጠየቅም ዝግጁ ናቸው ። አስመሳዮቹ ግን ይቅርታ ሲጠየቁ ደስ ይላቸዋል ። ይቅርታ መጠየቅ ግን ያማቸዋል ።

     ስለዚህ አጉል ድፍረት ራስን ማጣት ነው ። ድፍረትን ያለቦታው መጠቀም ነው ። ድፍረትን ያለቦታው መጠቀም ዋጋ ያስከፍላል ። ዋጋ ያስከፍላል ማለት መጨረሻው አያምርም ማለት ነው ። ድፍረትን በቦታው መጠቀምም ዋጋ ያስከፍላል ፣ ነገር ግን መጨረሻው ያምራል ። ፍጻሜው ሀዘን ሳይሆን ደስታ ነው ማለት ነው ። ድፍረት የእምነት ውጤት ነው ። አጉል እምነት አጉል ድፍረትን ይወልዳል ። ትክክለኛ እምነት ደግሞ ለክ የሆነ ድፍረትን ይፈጥራል ። ስለዚህ ድፍረትን ለማስተካከል እምነትን ማስተካከል ተገቢ ነው ። ለምሳሌ ሰውን በመናቅ የምናምን ከሆነ ፣ ድፍረታችን አጉል ይሆናል ። ሰውን በማክበር የምናምን ከሆነ ግን ፣ ድፍረታችን ትክክል ይሆናል ።

በውሸት የምናምን ከሆነ ፣ ለምንችለው ነገር ድፍረት እናጣና ፣ ለማንችለው ነገር አጉል ድፍረት ይኖረናል ። ድፍረታችን ልክ እንዲኖረው ፣ በልክ ማሰብ እና ማመን ተገቢ ነው ።

   ድፍረት ጀግና ያደርጋል ። አጉል ድፍረት ግን ጀዝባ ያደርጋል ። ያለድፍረት ስኬት የለም ። በአጉል ድፍረትም ስኬት የለም ። ያለድፍረት አዲስ ነገር መፍጠር አይቻልም ። በአጉል ድፍረትም መፍጠር አይቻልም ። ድፍረት ይጠቅማል ፣ አጉል ድፍረት ይጎዳል ። ድፍረትን በልኩና በቦታው እንጠቀም ። ከአጉል ድፍረት ግን እንጠንቀቅ ።

ሴትን ፣ ህጻናትን ፣ ሽማግሌዎችን መድፈር ፣ የአጉል ድፍረት ውጤት ነው ። አጉል ድፍረት ለወንጀል እንጅ ለስራ ትጉ አያደርግም ።

   ‘’ አጉል ድፍረት ፣ አጉል እምነት ነው ። አጉል እምነት ደግሞ የተዛባ አስተሳሰብ ነው ። ‘’                        

Wednesday, May 14, 2025

እይታ | Perception

                                                                         

                              ግጭት

     ‘’ ግጭት የህብረተሰብ አንቀሳቃሽ ሀይል ነው ‘’ ትላለች ህይወት ተፈራ ። በእርግጥ ይሄ ሀሳብ እውነትነት አለው ። ግጭት አንቀሳቃሽ ወይም አራማጅ ሀይል ነው ። ጦርነት አይደለም ግጭት ነው አንቀሳቃሽ ሀይል ። ጦርነትማ አንቀሳቃሽ ሀይል ሳይሆን አስለቃሽ ሀይል ነው ። ግጭት አስለቃሽ የሚሆነው መዳረሻው ጦርነት ሲሆን ነው ። መጨረሻው ጦርነት ካልሆነ ግን ፣ አዲስ ሀሳብ ወልዶ ፣እውቀት ጨምሮ ጥበብ አክሎ ነው የሚያልፈው ። ግጭት በሰው ልጅ ተፈጥሮ ውስጥ ያለ የሚኖር የሚቀጥል ነገር ነው ። ግጭት እንደ ውሀ ምግብ እና ልብስ ላያስፈልግ ይችላል ። ነገር ግን እኛ ባንፈልገውም ፣ ሰዎች እስከሆንን ድረስ በህይወት ስንኖር ሁል ጊዜ የሚገጥመን የህይወት ሀቅ ነው ።

    ሰው ከራሱ ፣ ከተፈጥሮ ፣ ከሰው እናም ከፈጣሪ ይጋጫል ። ሰው ከራሱ ሲጋጭ ፣ ግጭቱን መቆጣጠር ከቻለ አዲስ ሀሳብ ይወልዳል ። መቆጣጠር ካልቻለ ግን አዲስ ጭንቀት ይወልዳል ። መቆጣጠር ከቻለ ፣ ግጭቱን በጥበብ ይፈታል ። መቆጣጠር ካቃተው ግን በጥበብ ሳይሆን በጠብ ስራ ይፈታል ። ሰው ከተፈጥሮ እና ከፈጣሪ የሚጋጨው ፣ ከራሱ መታረቅ ሲያቅተው ነው ። ከሰው ጋር የሚጋጨው ግን ፣ በአብዛኛው በአንድ ሀሳብ ፣ ስራ ወይም ጉዳይ ላይ መስማማት ወይም መስማት ሲያቅተው ነው ። ከመስማማት መስማት ይቀድማል ። መስማት ከሌለ መስማማት አይኖርም ። በብዛት ሰው ከሰው የሚጋጨው ባለመስማማት ሳይሆን ባለመስማት ነው ማለት ይቻላል ። በመስማት ከባዱ ቀላል ይሆናል ።  

ባለ መስማት ግን ቀላሉ ከባድ ይሆናል ። ቀላሉ ነገር ከባድ ሲሆን ፣ ግጭት በቀላሉ ይፈጠራል ። ከባድ የመሰለው ነገር ቀለል ሲል ግን ፣ ግጭት በቀላሉ ይፈታል ።

      ግጭት ለድራማ እና ለፊልም ውበት ነው ። ለገሀዱ ዓለም ግን መፈታት ከቻለ ውበት ነው ። መፈታት ካልቻለ ግን ውበት ሳይሆን ወበቅ ነው ። ለልቦለድ የሚያሞቅ እሳት ነው ። ለገሀዱ አለም መፈታት ከቻለ ፣ በጨለማ ውስት ያለ ውብ የእሳት ብርሀን ነው ። ካልተፈታ ግን የእሳት ብርሀን ሳይሆን ትኩሳት ነው ። ግጭትን አንቀሳቃሽ ሀይል ማድረግ የሚቻለው በጥበብ ነው ። ግጭት በአብዛኛው የሚፈጠረው ፣ በነበረ ነገር ሳይሆን ፣ እንደ አዲስ በሚፈጠር ነገር ነው ። በታየ ነገር ሳይሆን ፣ ባልታየ ነገር ነው ። በተሞከረ ሳይሆን ባልተሞከረ ፣ በተለመደ ሳይሆን ባልተለመደ ነገር ነው ።

       ሰው አዲስ ነገርን በቀላሉ ለመቀበል ይቸገራል ። አዲስ ነገር ጠቃሚም ይሁን ጎጂ ፣ በቀላሉ በሰው ዘንድ ተቀባይነትን አያገኝም ። በእርግጥ ጎጂ ነገር ፣ ከጠቃሚ ነገር ይልቅ በፍጥነት የመለመድ እድል አለው ። በዚም ተባለ በዚያ አዲስ ነገር ግጭት መፍጠሩ አይቀርም ። ግጭትን በአግባቡ ማስተናገድ የቻለ ፣ ጎጂውን በመተው ጠቃሚውን አዲስ ነገር መቀበል እናም መጠቀም ይችላል ። በአግባቡ ማስተናገድ ያልቻለ ግን ፣ ጎጂውንም ጠቃሚውንም አዲስ ነገር ሳይቀበል እናም ሳይጠቀም ይቀራል ። ግጭትን መጠቀም የሚቻለው በአግባቡ ማስተናገድ ሲቻል ነው ። አልያ ግጭት ጥቅመ ቢስ አድርጎ ያስቀረናል ።

 አዲስ ነገር አዲስ ሀሳብ ፣ አዲስ ቦታ ፣ አዲስ ልብስ ፣ አዲስ ቁስ ፣አዲስ ቁርስም ሊሆን ይችላል ።

 የሰው ልጅ በዚህ የቴክኖሎጂ እና የመረጃ ዘመን ፣ ብዙ አዲስ ነገር ይገጥመዋል ። በቅርብ ቀን አዲስ ፊልም ፣ አዲስ ፕሮግራም ፣ አዲስ እንግዳ ፣ ምን አዲስ ነገር የሚሉ የሚዲያ ልፈፋዎች ፣ ሆን ተብለው የሰው ጆሮ ለማደንቆር የሚፈጠሩ ይመስላሉ ። ነገር ግን ከሁሉም አዲስ ነገር ፣ ከባዱ አዲስ ነገር ቢኖር ፣ አዲስ ሀሳብ ነው ። ሀሳብ ከግጭት ቀጥሎ ነው ተግባር የሚሆነው ። ያለ ግጭት የሚተገበር ሀሳብ ያለ አይመስለኝም ፣ ተራ ሀሳብ ካልሆነ በስተቀር ። ተራ ሀሳብ ግጭት አያስፈልገውም ። ተራ ሀሳብ ግጭት የሚፈጥረው ፣ በነገር አካባጆች መካከል ነው ። በነገር አቅላዮች ዘንድ ፣ ተራ ሀሳብ ቦታ የለውም ። የነገር አቅላይነት ( simplicity ) አንዱ ጥቅም ፣ በተራ ሀሳብ ጊዜን አለማጥፋት ነው ።

      የሰውን ልጅ ጊዜ ከሚበሉ ነገሮች መካከል አንዱ ነገርን ማካበድ ነው ። ትንሹን ነገር ትልቅ ማድረግ ፣ ቀላሉን ነገር ማወሳሰብ ። ነገርን ማካበድ በሀሳብ እና በተግባር መካከል ያለ ግድግዳ ነው ። ሀሳብ እንዳይተገበር አመድ የሚያደርግ አሲድ ነው ። በሀሳብ እና በተግባር መሀል ከባድ ግጭት የሚፈጥረው ፣ ነገርን ማካበድ ነው ። ከራሳቸውም ከሰውም በመጋጨት በብዛት የሚታወቁት ፣ ነገርን የሚያከብዱ ሰዎች ናቸው ። ግጭት ለእነዚህ ሰዎች ፣ ወደፊት አራማጅ ሳይሆን ፣ ነገርን አላማጅ ነው ። የሚማሩበት ሳይሆን የሚኮሩበት ነው ። ግጭት ለእነርሱ የበላይነትን ማሳያ እንጅ ፣ የተሻለ ነገር ማሳያ መስታወት አይደለም ። ሌሎችን አስለቃሽ ጭስ እነርሱን አስነጋሽ ዘውድ ነው ለእነርሱ ግጭት ። ስለዚህ ለግጭት ምክንያት ናቸው ተብለው ከሚጠቀሱ ነገሮች መካከል አንዱ ፣ ነገርን ማካበድ ነው ማለት ይቻላል ። ነገርን በማካበድ ከግጭት ጋር ወደፊት መሄድ አይቻልም ።

          ነገርን ማቅለል የሚችሉ ሰዎች ናቸው ፣ ግጭትን እንደመስታወት የሚጠቀሙት ። ለእነርሱ ግጭት አንቀሳቃሽ ሀይል ነው ማለት ይቻላል ። በግጭት ውስጥ ራሳቸውን ያያሉ ይማራሉ ። ለእነርሱ ሀሳብ እና ተግባር አይን እና አፍንጫ ናቸው ። በሀሳብ እና በተግባር መሀል ግጭት ቢፈጠር በቀላሉ ስለሚፈቱት ፣ ሀሳብን መኖር አይከብዳቸውም ። ነገርን ማቅለል ካለ ሀሳብ ተግባር ነው ። በተቃራኒው ነገር የሚካበድ ከሆነ ፣ ሀሳብ ተግባር ሳይሆን ሀሳር ነው የሚሆነው ። በነገር ማቅለል ውስጥ ግጭት ጠቃሚ ነው ። በነገር አካባጅነት ውስጥ ግን ግጭት ጎጂ ነው ።

      ‘’ ነገርን ማቅለል ካለ ግጭት አንቀሳቃሽ ሀይል ነው ። ‘’

Friday, May 9, 2025

እይታ | Perception

                                  ሞትን መናቅ

         ሞትን መናቅ በጣም ከባድ ነው ። ሞትን ለመናቅ ቆራጥ መሆን ያስፈልጋል ። ሞት የሚናቀው ተስፋ በመቁረጥ ሳይሆን በቆራጥነት ነው ። ሞትን መናቅ የቆራጥነት የመጨረሻ ደረጃ ነው ። ለመራብ ቆራጥ ያልሆነ ፣ ለመሞት ድፍረት አይኖረውም ። ክብርን ለማጣት ያልደፈረ ፣ ሞትን ለመናቅ አቅም አይኖረውም ። ለመታመም ፈቃደኛ ያልሆነ ፣ ለመሞት አይደለም ስለሞት ፈጽሞ አያስብም ። በነገራችን ላይ ስኬት ያለ ህመም ጤናማ አይደለም ። ግጭት የሌለበት ወጥ ሰላም ግልጽነት ይጎድለዋል ። ፈተና የሌለበት ስራ ዘላቂ አይሆንም ። ድካም የሌለበት እንጀራ አይጣፍጥም ። መራብ የሌለበት ጥጋብ ስሜት አይኖረውም ። ማጣት የሌለበት ማግኘት ትርጉም አልባ ነው የሚሆነው ።

              ሞትን ለመናቅ በመጀመሪያ የሰው ልጅ ፣ እነዚህን ነገሮች መለማመድ አለበት ። ለመታመም መፍቀድ አለበት ። ለመራብ መቁረጥ አለበት ። በፈተና መታሸት ይኖርበታል ። ለማጣት ዝግጁ መሆን አለበት ። ለመናቅ መወሰን መቻል አለበት ። በመከራ ውስጥ ማለፍ ይኖርበታል ። በእነዚህ የህይወት መስመር ውስጥ ሲያልፍ ፣ ለእውነት ጠንካራ ፍቅር ያድርበታል ። ለእምነት ወይም ለታማኝነት ያለው ዋጋ ከፍ ይላል ። ለፍቅር ይንበረከካል ። ለህይወት ዓላማ ያለው እይታ በአግባቡ ይቀረጻል ። በሰብአዊነት ይታነጻል ። በሞራል ያድጋል ። ለፍትህ ይቆረቆራል ። ለሰብአዊ መብት ጠንካራ ተቀናቃኝ ይሆናል ። ለራሱም ለሌላውም ሰው ህይወት ፣ ሀላፊነት የሚሰማው በሳል ሰው ይሆናል ። ለሰው ልጅ ሁሉ ነጻነት የሚታገል ብርሀን ይሆናል ። ያኔ ሞትን ለመናቅ ድፍረት እና ወኔ ያገኛል ።

          ፍቅር ፣ እውነት ፣ እምነት ፣ ነጻነት እነዚህ ነገሮች በሰው ልጅ ህይወት ውስጥ ፣ ከፍ ያለ ዋጋ ነው ያላቸው ። ጥንትም ዛሬም ፣ ድሮም ዘንድሮም ፣ ወደፊትም ቢሆን ሁሌም ዉድ ናቸው ረክሰው አያውቁም ። ፍቅርን የናቀ ይረክሳል ። እውነትን ያጣጠለ ወድቆ ይቀራል ። እምነትን ያረከሰ ይዋረዳል ። ነጻነትን የተጋፋ መጨረሻው ባርነት ይሆናል ። ፍቅር ያስከብራል ። እውነት ነጻ ያወጣል ። እምነት ከሞት በላይ ያደርጋል ። ነጻነት ሰላም እና ደስታን ያጎናጽፋል ። ሞትን መናቅ ፍቅርን የማክበር ፣ እውነትን የማፍቀር ፣ እምነትን የመኖር ፣ ነጻነትን የማወቅ ውጤት ነው ።

          ሰው እስከሞት ድረስ ዋጋ የሚከፍልላቸው ፣ እንቁ እሴቶች ናቸው ፣ ፍቅር ፣ እውነት ፣ እምነት እና ነጻነት ። ያለ እነርሱ ህይወትን ማሰብ እጅግ በጣም ከባድ ነው ። የሚገርመው ህይወትን በእነርሱ መገንባትም ከባድ ነው ። ያለ እነርሱ መኖርም ፣ በእነርሱ መኖርም አስቸጋሪ ነው ። ግን ልዩነቱ እዚህ ጋር ነው ፣ ያለ እነርሱ የሚፈጠረው ችግር መራራ ነው ። በእነርሱ የሚፈጠረው ችግር ግን ጣፋጭ ነው ። ሰው ፍቅርን በመናቁ የሚገጥመው ችግር መፍትሔ አልባ ነው ። መፍትሔ ቢኖርም የሚያድን ሳይሆን የሚገድል ነው ። ስለ ፍቅር ችግር ቢገጥመው ግን የሚፈታ ነው ። መፍትሔው የሚጎዳ ሳይሆን የሚጠቅም ነው ። ህይወትን የሚያበላሽ ሳይሆን የሚያስተካክል ነው ። ስለ ፍቅር መጎዳት ክብር ነው ። ፍቅርን መናቅ ግን ፍጻሜው ውርደት ነው ።

        እውነትም እንደፍቅር ነው ፣ መጀመሪያ ላይ ዋጋ ያስከፍላል ፣ መጨረሻ ላይ ግን ጥሩ አድርጎ ይከፍላል ። ስለ እውነት የሚገጥም ችግር ወደ ከፍታ ነው የሚወስደው ።

 እውነትን በመተው የሚፈጠር ችግር ግን ጉዞው የቁልቁለት ነው ። እውነትን በመተው የሚገኝ ክብር ጊዜያዊ ነው ። እውነትን የሙጥኝ በማለት የሚገኝ ክብር ግን ዘላለማዊ ነው ። ሰው ከእውነት ጋር ቢኖርም ባይኖርም ችግር ይገጥመዋል ። ያለ እውነት በምቾት ከሚኖር ፣ ስለ እውነት ቢቸገር ይሻለዋል ። የእውነት ችግር ስጦታ እንጅ መርገም አይደለም ። እውነትን በመተው የሚፈጠር ችግር ግን በረከት ሳይሆን መርገም ነው ። ስለዚህ ስለ እውነት ዋጋ እንክፈል ፣ ዋጋ ለሌለው ነገር እውነትን ከምንተው ።

       እምነትም እንደ ፍቅር እና እውነት ተመሳሳይ ነው ። መጀመሪያ ይፈትናል በመጨረሻም ይሸልማል ። ፈተናው መሰላል እንጅ መሰናክል አይደለም ። ወደ ላይ ቢወስድ እንጅ ወደ ታች አይጥልም ። እምነትን በመካድ የሚመጣ ፈተና ግን መሰላል ሳይሆን መሰናክል ነው ። ከከፍታ አንስቶ ትቢያ ላይ ይጥላል ። እምነት የሚፈጥረው ደስታ ዘላቂ ነው ። በክህደት የሚገኝ ደስታ ግን እንደ ጳጉሜ ወር በጣም አጭር ነው ። ደስታው ወጥ ሳይሆን ጋጠወጥ ነው ። አለ ስትሉት ይጠፋል ፣ የለም ስትሉት ብቅ ይላል ። ምክንያቱም ምንጩ ትክክል ስላልሆነ ፣ ደስታውም ስርዓት ያጣል ። ስርዓት ያለው ፣ መከራ የማይበግረው ደስታ ያለው እምነት ዉስጥ ነው ።

     ነጻነት ፍቅርን የማክበር ፣ እውነትን አጥብቆ የመያዝ ፣ እምነትን በልኩ የመኖር ውጤት ነው ። ነጻ መሆን የሚቻለው ከፍቅር ፣ ከእውነት እና ከእምነት ጋር ነው ። ሰው ለውድ እቃ በጣም ብዙ ገንዘብ ሊከፍል ይችላል ፣ ህይወቱን ወይም ነፍሱን ግን በፍጹም አሳልፎ አይሰጥም ። ለምሳሌ ለወርቅ ህይወቱን አይለግስም ። ለአልማዝ ነፍሱን አሳልፎ አይሰጥም ።

 ለነጻነት ግን እስከሞት ድረስ ዋጋ ይከፍላል ። ነፍሱን አሳልፎ ይሰጣል ። ህይወቱን ያለስስት ይለግሳል ። ነጻነት ማለት ለጋራ ህግ እየተገዙ ፣ ህይወትን በራስ መምራት መቻል ነው ። ለራስ ህይወት ሙሉ ሀላፊነትን መቀበል ነው ። ነጻነት የተፈጥሮን ህግ መጻረር አይደለም ፣ ይልቅ በተቃራኒው የተፈጥሮን ህግ በተጠንቀቅ መፈጸም ነው ። የሰው ልጅ ትክክለኛ ተፈጥሮው ነጻነቱ ነው ። ነጻነት የሰው ልጅ ተፈጥሮ ከሆነ ፣ ተፈጥሮንም ሆነ የተፈጥሮን ህግ መቃወም ነጻነት አይደለም ። ለዚህ ነው የሰው ልጅ ነጻነቱ ሲነካ ደሙ የሚፈላው ። ምክንያቱም ነጻነት ለሰው ልጅ በተፈጥሮ የተሰጠው ውድ ስጦታው ነው ።

         የሰው ልጅ የነጻነት ዋጋ ሲገባው ፣ ሞትን በመናቅ በሞት ፊት ደፋር ይሆናል ። የነጻነት ዋጋ በገንዘብ ሳይሆን የሚከፈለው ፣ በፍቅር ፣ በእውነት እናም በእምነት የሚከፈል ነው ። ፍቅር ፣ እውነት እና እምነት ሰውን በሞት ፊት ጀግና የሚያደርጉ ሀይሎች ናቸው ። ሞትን መናቅ የሚችሉ ሰዎች ፣ በፍቅር ፣ በእውነት እና በእምነት ለነጻነት የሚኖሩ ሰዎች ናቸው ።

       ‘’ ፍቅር እውነት እምነት እና ነጻነት ፣ ሞትን የሚያስንቁ ሀይሎች ናቸው ። ‘’                                                                        

Tuesday, May 6, 2025

እይታ | Perception

                                                              ኢላማ

    ኢላማ  ሰው ዓላማውን ፣ ፍላጎቱን ፣ ውጥኑን ለማሳካት የሚወስደው እርምጃ ነው ። ሰውን ወደ መዳረሻው የሚወስደው ፣ የትኩረት አቅጣጫ ነው ። ኢላማ ከሌለ ስኬት የለም ። ስኬት የለም ማለት ግን ኢላማ የለም ማለት አይደለም ። ስኬት ቢኖርም ባይኖርም ፣ ኢላማ ይኖራል ። ስኬት ግን ያለ ኢላማ ፈጽሞ አይታሰብም ። ሰው ኢላማው ትክክል ከሆነ ፣ ከስኬት ጫፍ ይደርሳል ። ኢላማው ትክክል ካልሆነ ግን ፣ ከውድቀት አፋፍ ይደርሳል ። በእርግጥ ትክክለኛ ኢላማ ኖሮትም ፣ ከስኬት ጫፍ የማይደርስ ሰው አለ ። ምክንያቱ ወይ የአቅም ማነስ ነው ፣ አልያም የባህሪ ጉድለት ነው ። ጥሩ ባህሪ እናም በቂ አቅም ኖሮት ፣ ኢላማው ግን የተሳሳተ ከሆነ ፣ ሰው ለስኬት አይበቃም ። ጥሩ ባህሪ ባይኖረውም ፣ በቂ አቅም ካለው ፣ ኢላማው ትክክል ከሆነ ከስኬት የመድረስ እድሉ አለው ። ጥሩ ባህሪ ኖሮት ፣ በቂ አቅም ከሌለው ፣ ኢላማው ትክክል ቢሆንም ፣ ስኬት እና እርሱ ሆድ እና ጀርባ ናቸው ። ጥሩ ባህሪ ከበቂ አቅም ጋር ሲደመር ትክክለኛ ኢላማ ፣ ያለምንም ጥርጥር ከስኬት ማማ ያደርሳሉ ።

         ኢላማ በመጀመሪያ አቅምን ያማከለ መሆን አለበት ። ‘’ አቅምን አውቆ መኖር ጥሩ ነው ታላቅ ችሎታ ነው ። ’’ አይደል ያለው አንጋፋው ዘፋኝ መሀሙድ አህመድ ። የሰው ልጅ ትልቁ ችሎታው አቅሙን ማወቁ ነው ። አቅሙን የማያውቅ ሰው ተሰባሪ ነው ። ስብራቱ ደግሞ የልብም የአካልም ነው ። ያለአቅሙ ያልምና አልሆን ሲለው ፣ በራስ መተማመኑን ያጣል ። እምነቱን ሲያጣ ልቡ ይሰበራል ። ልቡ ሲሰበር ክፉኛ በሀዘን ይጎዳል ። ሀዘኑ በመጨረሻ ለጤና መታወክ እና ለአካል ጉዳት ይዳርገዋል ። ህጻን ልጅን ጥሬ ስጋ ማብላት መጨረሻው ህመም ነው ። የአስር አመትን ልጅ ፣ ሀምሳ ኪሎ ዱቄት ማሸከም ፍጻሜው የአካል ጉዳት ነው ።

የአስራ አምስት አመትን ልጅ ፣ የፍልስፍና መጽሐፍ ማስነበብ ፣ መጨረሻው ሜዳሊያ ሳይሆን ሜዳ ላይ መውደቅ ነው ። ስለዚህ ኢላማ እና አቅም መመጣጠን አለባቸው ። በእርግጥ ኢላማ ከፍ ብሎ አቅም ከሚያንስ ፣ አቅም ከፍ ብሎ ኢላማ ቢያንስ የተሻለ ነው ። ኢላማ ዝቅ ማለቱ ግን እድገትን ሊገታ ይችላል ። እኩል ሲሆኑ ወይም ትንሽ ከፍ ቢል ፣ ጤናማ እድገት ይኖራል ።

       ኢላማ አተርፍ ባይ አጉዳይ መሆን የለበትም ። አንዳንድ ሰዎች የራሳቸውን ጎደሎ ለመሙላት ፣ የሌላው መጉደል አለበት ብለው ያምናሉ ። የራሳቸውን እንጀራ ለመጋገር ፣ የሌላውን ዳቦ መርገጥ አለብን ይላሉ ። ጠቅመው መጠቀም ሳይሆን ፣ ጎድተው መጠቀም ይፈልጋሉ ። ጥቅምን መጋራትም ሆነ ማጋራት ደስ አይላቸውም ። ብቻውን የበላ ብቻውን ይሞታል ቢባሉ ፣ አብሮስ የበላ መች አብሮ ሞተ ብለው ይመልሳሉ ። ብቻውን የበላ ሳይራብ ይሞታል ። አብሮ የበላ በራብ ይደፋል ብለው ያምናሉ ። መኖር በጋራ መሞት በግል ነው ፣ ይህ የተፈጥሮ ህግ ነው ። እነርሱ ጋር ግን መኖርም መሞትም በግል ነው ። የሚኖሩት ለራሳቸው ነው ። ሌላው እስከጠቀማቸው ያኖሩታል ። ካልጠቀማቸው ደግሞ ያሽቀነጥሩታል ። አተርፍ ባይ አጉዳይ የሆነ ኢላማ ፣ ከስህተትም በላይ ትልቅ ስህተት ነው ። ትክክለኛ ትርፍ የጎደለን በመሙላት የሚገኝ ነው ። የሞላን በማጉደል ማትረፍ ግን ፣ ትርፍ ገንዘብ ሊያስገኝ ቢችልም ለህሊና ኪሳራ ይዳርጋል ። የጎደለን መሙላት ለሚፈልጉ ሰዎች ፣ ችግር ሲሳይ ነው ። አተርፍ ባይ አጉዳይ ለሆኑ ሰዎች ግን ችግር ስቃይ ነው ። በነገራችን ላይ ሳይንሳዊ ጥናት አላማው ጉድለት መሙላት ( Gap fill ) ነው ። ስለዚህ ችግርን እንደ ሲሳይ እንጅ እንደ ስቃይ አይመለከትም ። ለማደግ ችግርን ይፈታል እንጅ ችግርን አይፈጥርም ። እነ አትርፍ ባይ አጉዳዮች ግን ለማትረፍ ችግርን ከመፍታት ይልቅ ችግርን ይፈጥራሉ ።

       አተርፍ አጉዳይ መሆን ፈጣሪ አያደርግም ። በአብዛኛው ፈጣሪዎች ሰው እናትርፍ ብለው እንጅ ገንዘብ እናትርፍ ብለው ስራ አይጀምሩም ። በሽታ ሲከሰት ሳይንቲስቱ መድሀኒት የሚፈጥረው ሰው ለማዳን ነው ። ሁለቱ ወንድማማቾች (  Right Brothers ) አውሮፕላንን የፈበረኩት የሰውን ድካም ለማቅለል ነው ። የኮምፒዩተር ሶፍትዌሮች ፣ የሞባይል መተግበሪያዎች የሚበለጸጉት የሰውን ልጅ ኑሮ ለማቅለል ነው ። በትክክል ከተረዳን እናም ከተጠቀምን ፣ እነዚህ ነገሮች ጫናን ከመፍጠር ይልቅ ይቀንሳሉ ። ፈጣሪዎች ኢላማቸው የተስተካከለ ስለሆነ ፣ አላማቸው ዉብ ነው ። ሰውን እያስለቀሱ ሳይሆን ፣ የሰውን እንባ በማበስ ነው የሚያተርፉት ። ሰውን በማቃለል ሳይሆን ችግርን በማቅለል ነው የሚደሰቱት ። ለዓለም የጎደላትን ይሞላሉ እንጅ ለዓለም ጉድለት አይሆኑም ።

        ትክክለኛ ዓላማ ለተስተካከለ ዒላማ ዋስትና አይሆንም ። ዓላማ ኢላማን አይወስንም ። ኢላማ ግን ዓላማን ይወስናል ። ኢላማችን ልክ ሲሆን ነው ፣ ዓላማችን እውን የሚሆነው ። ኢላማችን ስህተት ከሆነ ግን ዓላማችን ቅዥት ነው የሚሆነው ። መብት ለማግኘት መብት መንፈግ ትክክል አይደለም ። ስልጣን ለመንጠቅ ነፍስ መንጠቅ ተገቢ አይደለም ። እምነትን ለመፍጠር ከሀዲ መሆን ልክ አይደለም ። ለመታረቅ ማጣላት ተንኮል ነው ። ለመቆም መጣል ግፍ ነው ። ሳይነፍጉ ማግኘት ፣ ሳይነጥቁ መውሰድ ፣ ሳይክዱ መታመን ፣ ሳያጣሉ መታረቅ ፣ ሳይጥሉ መቆም ይቻላል ። ትክክለኛ ኢላማ ያለውም እነዚህ ውስጥ ነው ። በአለም ዙሪያ የሚዘወተር አንድ የተሳሳተ ኢላማ አለ ፣ መንግስትን ለመቀየር የህዝብን ሀብት ማውደም ። መንግስትን ለመቀየር ፣ የህዝብን ሀብት ማውደም ሳይሆን መፍትሔው ፣ ህዝብን ማሳመን ኢላማ ማድረግ ነው የሚያዋጣው ። ማውደም ሳይሆን ማሳመን ነው ትክክለኛ ኢላማው ። አባትን ለማሳመን ልጅን ኢላማ ማድረግ የተሳሳተ እርምጃ ነው ።

 ርእሰ መምህሩን ስለጠሉ ትምህርት ቤቱን ማፍረስ አምሮን ማፍረስ ነው ። መብትን ለማስከበር መንገድ መዝጋት እድልን መዝጋት ነው ።

ገበያ ለመፍጠር የሌላውን ገበያ መዝጋት ቀሽምነት ነው ። የተሳሳተ ኢላማ የመሽቀዳደም ውጤት ነው ። በመሽቀዳደም ውስጥ ፣ መቅደም ያለበት ይከተላል ፣ መከተል ያለበት ይቀድምና ነገር ይበላሻል ። ቀኙ ግራ ፣ ግራው ቀኝ ይሆናል ። መሽቀዳደም ራስ ወዳድ ያደርጋል ። ስለዚህ ለትክክለኛ ዓላማ ፣ የተሳሳተ ኢላማ እንዲኖረን ያስገድደናል ። መሽቀዳደም መከባበርን ያሳጣል ። እኔ እሻላለው እንጅ ፣ ሌላው ይሻላል ማለት በመሽቀዳደም ውስጥ ከባድ ነው ። መከበር እንጅ ማክበር ፈጽሞ አይታሰብም ። ስለዚህ አላማችን እውን እንዲሆን ፣ የተስተካከለ ኢላማ እንዲኖረን ፣ መሽቀዳደምን ማስወገድ መቻል አለብን ።

       ‘’ ኢላማ ሲስተካከል ዓላማ እውን ይሆናል ። ‘’      

እይታ | Perception

                                                    ስሜታዊነት እና እምነት     እምነት በስሜት አይገነባም ። እምነት ሲሞቀን የምንገነባው ፣ ሲበርደን ደግሞ የምናፈርሰው ወረት አይደለም ። ...