ሞትን መናቅ
ሞትን መናቅ በጣም ከባድ ነው ። ሞትን ለመናቅ
ቆራጥ መሆን ያስፈልጋል ። ሞት የሚናቀው ተስፋ በመቁረጥ ሳይሆን በቆራጥነት ነው ። ሞትን መናቅ የቆራጥነት የመጨረሻ ደረጃ ነው
። ለመራብ ቆራጥ ያልሆነ ፣ ለመሞት ድፍረት አይኖረውም ። ክብርን ለማጣት ያልደፈረ ፣ ሞትን ለመናቅ አቅም አይኖረውም ። ለመታመም
ፈቃደኛ ያልሆነ ፣ ለመሞት አይደለም ስለሞት ፈጽሞ አያስብም ። በነገራችን ላይ ስኬት ያለ ህመም ጤናማ አይደለም ። ግጭት የሌለበት
ወጥ ሰላም ግልጽነት ይጎድለዋል ። ፈተና የሌለበት ስራ ዘላቂ አይሆንም ። ድካም የሌለበት እንጀራ አይጣፍጥም ። መራብ የሌለበት
ጥጋብ ስሜት አይኖረውም ። ማጣት የሌለበት ማግኘት ትርጉም አልባ ነው የሚሆነው ።
ሞትን ለመናቅ በመጀመሪያ የሰው ልጅ ፣ እነዚህን ነገሮች
መለማመድ አለበት ። ለመታመም መፍቀድ አለበት ። ለመራብ መቁረጥ አለበት ። በፈተና መታሸት ይኖርበታል ። ለማጣት ዝግጁ መሆን
አለበት ። ለመናቅ መወሰን መቻል አለበት ። በመከራ ውስጥ ማለፍ ይኖርበታል ። በእነዚህ የህይወት መስመር ውስጥ ሲያልፍ ፣ ለእውነት
ጠንካራ ፍቅር ያድርበታል ። ለእምነት ወይም ለታማኝነት ያለው ዋጋ ከፍ ይላል ። ለፍቅር ይንበረከካል ። ለህይወት ዓላማ ያለው
እይታ በአግባቡ ይቀረጻል ። በሰብአዊነት ይታነጻል ። በሞራል ያድጋል ። ለፍትህ ይቆረቆራል ። ለሰብአዊ መብት ጠንካራ ተቀናቃኝ
ይሆናል ። ለራሱም ለሌላውም ሰው ህይወት ፣ ሀላፊነት የሚሰማው በሳል ሰው ይሆናል ። ለሰው ልጅ ሁሉ ነጻነት የሚታገል ብርሀን
ይሆናል ። ያኔ ሞትን ለመናቅ ድፍረት እና ወኔ ያገኛል ።
ፍቅር ፣ እውነት ፣ እምነት ፣ ነጻነት እነዚህ ነገሮች በሰው
ልጅ ህይወት ውስጥ ፣ ከፍ ያለ ዋጋ ነው ያላቸው ። ጥንትም ዛሬም ፣ ድሮም ዘንድሮም ፣ ወደፊትም ቢሆን ሁሌም ዉድ ናቸው ረክሰው
አያውቁም ። ፍቅርን የናቀ ይረክሳል ። እውነትን ያጣጠለ ወድቆ ይቀራል ። እምነትን ያረከሰ ይዋረዳል ። ነጻነትን የተጋፋ መጨረሻው
ባርነት ይሆናል ። ፍቅር ያስከብራል ። እውነት ነጻ ያወጣል ። እምነት ከሞት በላይ ያደርጋል ። ነጻነት ሰላም እና ደስታን ያጎናጽፋል
። ሞትን መናቅ ፍቅርን የማክበር ፣ እውነትን የማፍቀር ፣ እምነትን የመኖር ፣ ነጻነትን የማወቅ ውጤት ነው ።
ሰው እስከሞት ድረስ ዋጋ የሚከፍልላቸው ፣ እንቁ እሴቶች ናቸው
፣ ፍቅር ፣ እውነት ፣ እምነት እና ነጻነት ። ያለ እነርሱ ህይወትን ማሰብ እጅግ በጣም ከባድ ነው ። የሚገርመው ህይወትን በእነርሱ
መገንባትም ከባድ ነው ። ያለ እነርሱ መኖርም ፣ በእነርሱ መኖርም አስቸጋሪ ነው ። ግን ልዩነቱ እዚህ ጋር ነው ፣ ያለ እነርሱ
የሚፈጠረው ችግር መራራ ነው ። በእነርሱ የሚፈጠረው ችግር ግን ጣፋጭ ነው ። ሰው ፍቅርን በመናቁ የሚገጥመው ችግር መፍትሔ አልባ
ነው ። መፍትሔ ቢኖርም የሚያድን ሳይሆን የሚገድል ነው ። ስለ ፍቅር ችግር ቢገጥመው ግን የሚፈታ ነው ። መፍትሔው የሚጎዳ ሳይሆን
የሚጠቅም ነው ። ህይወትን የሚያበላሽ ሳይሆን የሚያስተካክል ነው ። ስለ ፍቅር መጎዳት ክብር ነው ። ፍቅርን መናቅ ግን ፍጻሜው
ውርደት ነው ።
እውነትም እንደፍቅር ነው ፣ መጀመሪያ ላይ ዋጋ ያስከፍላል ፣ መጨረሻ
ላይ ግን ጥሩ አድርጎ ይከፍላል ። ስለ እውነት የሚገጥም ችግር ወደ ከፍታ ነው የሚወስደው ።
እውነትን በመተው የሚፈጠር ችግር ግን ጉዞው የቁልቁለት ነው ። እውነትን በመተው
የሚገኝ ክብር ጊዜያዊ ነው ። እውነትን የሙጥኝ በማለት የሚገኝ ክብር ግን ዘላለማዊ ነው ። ሰው ከእውነት ጋር ቢኖርም ባይኖርም
ችግር ይገጥመዋል ። ያለ እውነት በምቾት ከሚኖር ፣ ስለ እውነት ቢቸገር ይሻለዋል ። የእውነት ችግር ስጦታ እንጅ መርገም አይደለም
። እውነትን በመተው የሚፈጠር ችግር ግን በረከት ሳይሆን መርገም ነው ። ስለዚህ ስለ እውነት ዋጋ እንክፈል ፣ ዋጋ ለሌለው ነገር
እውነትን ከምንተው ።
እምነትም እንደ ፍቅር እና እውነት ተመሳሳይ ነው ። መጀመሪያ ይፈትናል
በመጨረሻም ይሸልማል ። ፈተናው መሰላል እንጅ መሰናክል አይደለም ። ወደ ላይ ቢወስድ እንጅ ወደ ታች አይጥልም ። እምነትን በመካድ
የሚመጣ ፈተና ግን መሰላል ሳይሆን መሰናክል ነው ። ከከፍታ አንስቶ ትቢያ ላይ ይጥላል ። እምነት የሚፈጥረው ደስታ ዘላቂ ነው
። በክህደት የሚገኝ ደስታ ግን እንደ ጳጉሜ ወር በጣም አጭር ነው ። ደስታው ወጥ ሳይሆን ጋጠወጥ ነው ። አለ ስትሉት ይጠፋል
፣ የለም ስትሉት ብቅ ይላል ። ምክንያቱም ምንጩ ትክክል ስላልሆነ ፣ ደስታውም ስርዓት ያጣል ። ስርዓት ያለው ፣ መከራ የማይበግረው
ደስታ ያለው እምነት ዉስጥ ነው ።
ነጻነት ፍቅርን የማክበር ፣ እውነትን አጥብቆ የመያዝ ፣ እምነትን በልኩ
የመኖር ውጤት ነው ። ነጻ መሆን የሚቻለው ከፍቅር ፣ ከእውነት እና ከእምነት ጋር ነው ። ሰው ለውድ እቃ በጣም ብዙ ገንዘብ ሊከፍል
ይችላል ፣ ህይወቱን ወይም ነፍሱን ግን በፍጹም አሳልፎ አይሰጥም ። ለምሳሌ ለወርቅ ህይወቱን አይለግስም ። ለአልማዝ ነፍሱን አሳልፎ
አይሰጥም ።
ለነጻነት ግን እስከሞት ድረስ ዋጋ ይከፍላል ። ነፍሱን አሳልፎ ይሰጣል ።
ህይወቱን ያለስስት ይለግሳል ። ነጻነት ማለት ለጋራ ህግ እየተገዙ ፣ ህይወትን በራስ መምራት መቻል ነው ። ለራስ ህይወት ሙሉ
ሀላፊነትን መቀበል ነው ። ነጻነት የተፈጥሮን ህግ መጻረር አይደለም ፣ ይልቅ በተቃራኒው የተፈጥሮን ህግ በተጠንቀቅ መፈጸም ነው
። የሰው ልጅ ትክክለኛ ተፈጥሮው ነጻነቱ ነው ። ነጻነት የሰው ልጅ ተፈጥሮ ከሆነ ፣ ተፈጥሮንም ሆነ የተፈጥሮን ህግ መቃወም ነጻነት
አይደለም ። ለዚህ ነው የሰው ልጅ ነጻነቱ ሲነካ ደሙ የሚፈላው ። ምክንያቱም ነጻነት ለሰው ልጅ በተፈጥሮ የተሰጠው ውድ ስጦታው
ነው ።
የሰው ልጅ የነጻነት ዋጋ ሲገባው ፣ ሞትን በመናቅ በሞት ፊት
ደፋር ይሆናል ። የነጻነት ዋጋ በገንዘብ ሳይሆን የሚከፈለው ፣ በፍቅር ፣ በእውነት እናም በእምነት የሚከፈል ነው ። ፍቅር ፣
እውነት እና እምነት ሰውን በሞት ፊት ጀግና የሚያደርጉ ሀይሎች ናቸው ። ሞትን መናቅ የሚችሉ ሰዎች ፣ በፍቅር ፣ በእውነት እና
በእምነት ለነጻነት የሚኖሩ ሰዎች ናቸው ።
‘’ ፍቅር እውነት እምነት እና ነጻነት ፣ ሞትን የሚያስንቁ ሀይሎች ናቸው ። ‘’
No comments:
Post a Comment