Showing posts with label Melaku's Thought. Show all posts
Showing posts with label Melaku's Thought. Show all posts

Monday, April 21, 2025

እይታ | Perception

                                                        የትውልድ ቅብብሎሽ

               ለውጥ ስር ነቀል ሲሆን የትውልድ ቅብብሎሽ አይኖርም ። ለውጥ ስር ነቀል ነው  ብሎ ማመን ፣ ትላንት ሙሉ በሙሉ መጥፎ ነው ፣ ጥሩ ነገር የለውም ማለት ነው ። ህይወት ጥቁር ወይም ነጭ እንጅ ግራጫ መልክ የላትም እንደ ማለት ነው ። የህይወት እውነታ ግን ይህን አያሳይም ። ትላንት ፍጹም ጥሩ ወይም ፍጹም መጥፎ ሊሆን አይችልም ። ሙሉ በሙሉ ትክክል ወይም ስህተት ሊሆን አይችልም ። የትላንት ታሪክ የሰዎች ታሪክ ነው ። የትላንት ስራ የሰዎች ስራ ነው ። ሰዎች ደግሞ ትክክልም ስህተትም ይሰራሉ ። ጥሩም መጥፎም ያደርጋሉ ። በስር ነቀል ለውጥ ማመን ፣ ይህንን መሰረታዊ የሰው ልጅ ተፈጥሮ መካድ ወይም አለመቀበል ነው ። 

             የሰው ልጅ በብዛት መጥፎ ከሰራ ፣ በቀጣዩ ትውልድ በመጥፎ ታሪኩ ይወሳል ። ያ ማለት ግን ምንም ጥሩ ስራ የለውም ማለት አይደለም ። ከመጥፎ ስራው ብዛት አንጻር ፣ ጥሩ ስራው በቀላሉ የመታወስ እድል  ስለማይኖረው ነው ። በሌላ በኩል በብዛት ጥሩ ከሰራ ፣ ጥሩ ታሪኩ ለትውልዱ ይነገርለታል ። ይህ ማለት ግን መጥፎ ስራ የለውም ፣ መልአክ ነው ማለት አይደለም ። ከጥሩ ስራው አንጻር ፣ መጥፎ ታሪኩ ወደ ፊት ከመቀጠል ይልቅ በቀላሉ ስለሚቃጠል ነው ። ከመታወስ ይልቅ በቀላሉ ስለሚረሳ ነው ። የስራ የመታወስ አቅሙ ብዛቱ ነው ። ብዙ ጥሩ ከሰራን ፣ በብዙ ሰዎች እና በትውልድ ልብ ውስጥ በመልካምነት እንታወሳለን ። ትንሽ ከሰራን ግን ከመታወስ ይልቅ በቀላሉ እንረሳለን ። በተመሳሳይ ብዙ መጥፎ ከሰራን ፣ በክፋት ስማችን በትውልዱ ይነሳል ። ትንሽ ከሰራን ግን ፣ አይደለም ለትውልድ ሊሻገር ፣ ከቤት የማይሻገር ታሪክ ሆኖ ይቀራል ። 

            ጥሩ ከመጥፎ ሲበዛ መልካም ያስብላል ። መጥፎ ከጥሩ ሲበዛ ክፉ ያስብላል ። ልክነት ከስህተት ሲበዛ ጎበዝ ያሰኛል ። ስህተት ከልክነት ሲበዛ ሰነፍ ያሰኛል ። መልካም ፣ ጎበዝ እና ክፉ ሰዎች ታሪክ ይኖራቸዋል ። ሰነፎች ግን ምንም ታሪክ አይኖራቸውም ። ሰው ጎበዝ ሆኖ ክፉ ከሆነ ፣ ትውልድ ከክፋቱ ሳይሆን ከጉብዝናው ይማራል ። ጎበዝም መልካምም ከሆነ ፣ ከጉብዝናውም ከመልካምነቱም ይማራል ። ሰነፍ ከሆነ ግን ምንም ስለሌለው ፣ ትውልድ ከእርሱ ምንም አይማርም ። ሰነፍ ሰው እና ዳተኛ ትውልድ ምንም ታሪክ አይኖራቸውም ። አይደለም የታሪክ አሻራ ፣ የጣት አሻራ ይኑራቸው አይኑራቸው አይታወቅም ። ክፉ እውቀት ከመሀይምነት ይከፋል ( Bad knowledge is more danger than ignorance ) ቢባልም ፣ ምንም አለማወቅ ክፉ ባያደርግም ፣ የክፋት ተባባሪ ያደርጋል ። ምንም አለማወቅ የዋህ ሳይሆን ጅል ነው የሚያደርገው ። የዋህነት ከክፋት ነጻ መሆን ነው ። ጅልነት ግን ከእውቀት ነጻ መሆን ነው ። ከክፉም ከመልካም እውቀት ባዶ መሆን ነው ። ከክፉ እውቀት ይልቅ ፣ ከእውቀት ነጻ መሆን ቢሻልም ግን ጥሩ አይደለም ። ጥሩውም ልኩም ፣ መልካሙን መያዝ ክፉውን መጣል ነው ። ሁሉን መያዝ ፣ ሁሉን መጣል አይቻልም ። መርጦ መያዝ ፣ መርጦ መተው ግን ይቻላል ። ስለዚህ ምርጫችንን እናስተካክል ። ምክንያቱም ምርጫችን ነው ሰውም አውሬ የሚያደርገን ። መልአክም ሰይጣንም የሚያደርገን ። ስንፍና ግን በምንም ሚዛን አያዋጣም ። 

         መልአክ እና የሰው መልአክ ይለያያሉ ። መልአክ ፍጹም ነው ። የሰው መልአክ ግን ፍጹም አይደለም ። በተመሳሳይ አውሬ እና የሰው አውሬ ይለያያሉ ። አውሬ ርህራሄ የለውም ፣ ፍጹም ጨካኝ ነው ። የሰው አውሬ ግን ፍጹም ጨካኝ አይደለም ። በትንሹም ቢሆን ልቡ መራራቱ አይቀርም ። ሰው ከሰው መልአክ ብዙ መማር አለበት ። ከሰው አውሬ ግን ትንሽ ነው መማር ያለበት ። ትንሽም ተማረ ብዙም ተማረ ፣ ዋናው ነገር መማር መቻሉ ነው ። ለውጥ ደግሞ የመማር ውጤት ነው ። ለመማር ነገርን ከስሩ መንቀል ሳይሆን የሚያዋጣው ፣ ነገርን ከስሩ መመልከት ነው የሚያስፈልገው ። ትላንትን ከስሩ መንቀል ሳይሆን ፣ ችግርን ከስሩ መንቀል ነው መፍትሔው ። '' አረምን መንቀል ስር ሳይሰድ ነው ። '' እንዲሉ አበው ፣ ለለውጥ አረምን እንጅ አለምን መንቀል አያዋጣም ። ስር ነቀል ለውጥ ግን አረምን ሳይሆን አለምን መንቀል ነው ። ስለዚህ ጠቃሚ ሳይሆን ጎጂ ነው ። ስር ነቀል ለውጥ የዋህነት የጎደለው ልባምነት ፣ ይቅር ባይነት የሌለው ትጋት ነው ። ከሰው መልአክም ከሰው አውሬም መማር አለመቻል ነው ። ይህ ደግሞ እንደ ሀገር ሊኖር የሚችለውን የወደፊት ጉዞ ይገታል ። 

         ስር ነቀል ለውጥ ትውልድ ያፈርሳል እንጅ አይገነባም ። ታሪክ ያቃጥላል እንጅ አያስቀጥልም ። ለመማር ዝግጁ ለሆነ ሰው ታሪክ ሀብት ነው ። ዝግጁ ላልሆነ ግን ታሪክ ሸክም ነው ። ሉሲ ፣ አክሱም ፣ ፋሲለደስ ፣ ጀጎል እና ላሊበላ ላወቀበት ሀብት ናቸው ። ላላስተዋለ ግን ዘበት ናቸው ። ትክክለኛ ለውጥ ሁሉን ጥሎ ማለፍ ሳይሆን ፣ መጥፎውን ጥሎ ጥሩውን ይዞ መሻገር ነው ። ጥሎም አንጠልጥሎም ማለፍ ነው ። ያኔ እንደ አዲስ የሚገነባ ታሪክ ሳይሆን ፣ በሂደት የሚገነባ ታሪክ ይኖረናል ። መሳሪያ የሚቀባበል ትውልድ ሳይሆን ፣ ታሪክ እና ስራ የሚቀባበል ትውልድ ይታነጻል ። ሆ ብሎ የሚያቃጥል ሳይሆን ፣ ሀ ብሎ የሚያስቀጥል ትውልድ ይነሳል ። በስሜት የሚያፈርስ ሳይሆን በስሌት የሚገነባ ትውልድ ይፈጠራል ። ስር ነቀል ለውጥ ፣ ለውጥን ከመፍጠር በላይ ነውጥን የመፍጠር እድሉ ሰፊ ነው ። ምክንያቱም በዚህ የለውጥ ሂደት ፣ መነካት የሌለበት የህዝብ ልብ የሚነካ ነገር ሊወድም ይችላል ። መጥፋት የሌለበት ሀገራዊ  ማንነት በቀላሉ ሊጠፋ ይችላል ። ሀገር ያለ ካስማ እና ያለ ምሶሶ መና ልትቀር ትችላለች ። 

         ስር ነቀል ለውጥ ከጥቅሙ ጉዳቱ ፣ ከልማቱ ጥፋቱ ፣ ከአዎንታዊነቱ አሉታዊነቱ ይገዝፋል ። ስለዚህ ለውጥ ጥገናዊ እንጅ ስር ነቀል መሆን የለበትም ። የተበላሸውን እያስተከከሉ ፣ የተዛነፈውን እያቃኑ ፣ የደፈረሰውን እያጠሩ ፣ በነበረው ጥሩ ነገር ላይ አዲስ ነገር እየጨመሩ መሄድ ነው ጥገናዊ ለውጥ ። የዚህ ለውጥ መርህ ፣ ታሪክ እየረሱ እና እየጣሉ መሄድ ሳይሆን ፣ ታሪክ እየጠበቁ እና እየገነቡ ወደ ፊት መሄድ ነው ። የትውልድ ቅብብሎሽ እውን የሚሆነው ፣ ለውጥ ጥገናዊ ሲሆን ነው ። 

        ጥገናዊ ለውጥ የደግነት እና የትህትና ውጤት ነው ። ለመስጠት ደግነት ያስፈልጋል ። ለመቀበል ትህትና ግድ ይላል ። የሚሰጥ ደግ ኖሮ ፣ የሚቀበል ትሁት ከሌለ ችግር ነው ። የሚቀበል ትሁት ኖሮ ፣ የሚሰጥ ደግ ከሌለ ታሪክን ለመቀበልም ለማስቀጠልም ከባድ ነው ። ስለዚህ ቀዳሚው ትውልድ ለማስተማር እና ለመስጠት ደግ መሆን አለበት ። ተከታዩ ትውልድ ደግሞ ለመማር እና  ለመቀበል ትሁት መሆን አለበት ። ያኔ የትውልድ ቅብብሎሽ እውን ይሆናል ። 

    '' ጥገናዊ ለውጥ ለትውልድ ቅብብሎሽ አስፈላጊ ነው ። ''     

Saturday, April 19, 2025

እይታ | Perception

                                                           ንቃተ ህሊና

         ንቃተ ህሊና ያለው ሰው ነገሮችን በቅደም ተከተል ማስቀመጥ ይችላል ። ቀላል እና ከባድ ችግሮችን በቀላሉ መለየት ይሆንለታል ። ፍሬን ከገለባ ፣ ነገርን ከቁም ነገር ፣ ቆሻሻን ከንጹህ ፣ አጭበርባሪን ከሀቀኛ ለይቶ መመደብ መታወቂያው ነው ። ንቃተ ህሊና የእውቀት ብቻ ሳይሆን ፣ የልምድ እና ያወቁትን የመኖር ውጤት ነው ። ሰው የቱንም ያህል ቢያውቅ ፣ ሺ መጽሐፍ ቢያነብ ፣ ያወቀውን በተግባር እስካልኖረው ድረስ ፣ አወቀ እንጅ ነቃ አይባልም ። የእውቀት መኖሪያ መሆን ሳይሆን ፣ እውቀትን መኖር ነው ንቃተ ህሊናን የሚፈጥረው ። ብዙ ማወቅ ትንሽ መኖር ንቃተ ህሊናን አያጎለብትም ። ትንሽም ቢሆን ያወቁትን ያህል መኖር ነው ፣ የንቃተ ህሊና ባለቤት የሚያደርገው ። 

          ብዙ ያወቁ ግን ያልነቁ ሰዎች አሉ ። ምክንያቱ ምንም አይደለም ፣ ያወቁትን በአግባቡ መኖር አለመቻላቸው ነው ። እውቀትን የማይኖሩ ሰዎች ፣ በንቃት ከመኖር ይልቅ በንቀት ይሞላሉ ። ያወቁትን የሚኖሩ ሰዎች ግን በንቃት ያድጋሉ ። ንቃት ማበላሸት ሳይሆን ማስተካከል ነው ። ማደፍረስ ሳይሆን ማጥራት እና ማጣራት ነው ። ማጣመም ሳይሆን ማቃናት ነው ። ብዙ እናውቃለን የሚሉ ግን ያልነቁ ሰዎች ፣ ማበላሸት እንጅ ማስተካከል አይችሉም ። ለማደፍረስ እንጅ ለማጥራት ጊዜ የላቸውም ። ለማጣመም እንጅ ለማቃናት የሚሆን ህሊና የላቸውም ። ምክንያቱም ንቀት ስላለባቸው ቀና ማሰብ አይችሉም ። ተንኮለኛ እንጅ ጥበበኛ መሆን አይችሉም ። ንቃት ጥበበኛ ያደርጋል ። ንቀት ደግሞ ተንኮለኛ ያደርጋል ። 

        እውቀት ልህቀት የሚሆነው ስንነቃ ነው ። አልያ ግን ሊቅነት ሳይሆን ልቅነት ይፈጠራል ። ሊቆች ሳይሆኑ ፣ ልቅ የሆኑ አዋቂዎች እውቀትን ማኖር እንጅ መኖር አይችሉም ። ሀቀኛ ሳይሆኑ አስመሳይ ናቸው ። የሚኖሩት ከአንጀታቸው ሳይሆን ከአንገታቸው ነው ። ወሬ እንጅ ወረት የላቸውም ። ለእነርሱ መናገር ቀላል ነው ። መኖር ግን እጅግ ከባድ ነው ። የወሬ አዋርድ ቢኖር ፣ የመጀመሪያ ተሸላሚ የሚሆኑት እነርሱ ናቸው ። ወሬ እና አውሬ ውስጣቸው አለ ። እውነት እና ፍቅር ግን ውስጣቸው የለም ። እውነተኛ ሰይጣን የት ነው መገኛው ? ቢባል ፣ ምንም አያጠራጥርም አስመሳይ ሰው ውስጥ ነው ። ሰይጣን አዋቂ በሆኑ አስመሳይ ሰዎች ይቀናል ። በተንኮላቸው ሰይጣንን የሚያስቀኑ ብቸኛ ፍጥረት ፣ አስመሳይ ሰዎች ናቸው ። እነርሱ ደግሞ ንቀት እንጅ ንቃት የላቸውም ። 

       ንቃተ ህሊና ያላቸው ሰዎች ጨለማን የሚገፉ ብርሃን ናቸው ። ጨለማን የሚያስፋፉ ክፉ ሰዎች ግን ፣ ንቃተ ህሊና ሳይሆን ንቀተ ህሊና ነው ያላቸው ። ማስለቀስ እንጅ ማጽናናት አይችሉም ። እነርሱ ለምድር ደራሽ ጎርፍ ፣ ለሰዎች ደግሞ የሀዘን ጎርፍ ናቸው ። ለገንዘብ የሚሳሱትን ያህል ፣ ለሰው ነፍስ አይሳሱም ። መሰብሰብ እና ማከማቸት ይችላሉ ። መስጠት እና ማካፈል ግን በዞሩበት አይዞሩም ። እነርሱ ትርፋቸው የሌሎች ኪሳራ ነው ። ስኬታቸው የሌሎች ውድቀት ነው ። ክብራቸው የሌሎች ውርደት ነው ። ደስታቸው የሌሎች ሃዘን ነው ። 

       የነቁ ብርሀን የሆኑ ሰዎች ግን ፣ የሌላው ሀዘን ሀዘናቸው ነው ። በደስታቸው ይደሰታሉ ፣ ሲያጡ ይከፋሉ ፣ ሲራቡ ከልብ ያዝናሉ ። እነርሱ ምግብ ሲያጡ ሳይሆን ፣ ሰው ሲያጡ ነው የሚራቡት ። ውሀ ሲያጡ ሳይሆን ፍቅር ሲያጡ ነው ከልብ የሚጠሙት ። ሰው ሲቸገር ሳይሆን መከራን ሲሻገር ደስ ይላቸዋል ። ካወቁት ማካፈል ፣ ካገኙት መስጠት የህሊና እርካታ ይሰጣቸዋል ። የሚገድሉ መርዝ ሳይሆኑ ፣ የሚፈውሱ መድሀኒት ናቸው ። መድሀኒት በመስጠት ፣ እርዳታም በመስጠት ፣ ሰውን ከከፉ በሽታም ሆነ ከክፉ ነገር ያድናሉ ። እነርሱ ዉስጣቸውም ውጪያቸውም ያው አንድ ነው ። ውስጣቸው ቦሌ ፣ ውጪያቸው ጉለሌ አይደለም ። ያወሩትን ይኖራሉ ፣ የኖሩትን ያወራሉ ። ስራ መፍጠር እንጅ ወሬ መፍጠር ብዙ አይችሉበትም ። ማስመሰል ጠላታቸው ፣ እውነተኝነት ደግሞ ወዳጃቸው ነው ። አስመስለው ከሚኖሩ ፣ ከእውነት ጋር ቢቀበሩ ይመርጣሉ ። ግዴታ ከሆነ ፣ ሰውን ለማዳን ሲሉ ሊያስመስሉ ይችላሉ ። በተረፈ ሰው እንዲሞት ብለው በፍጹም አያስመስሉም ። ለፍቅር ያስመስላሉ ፣ ለጥላቻ ግን አይደለም ቦታ ፣ ትርፍ ቦታም የላቸውም ። የእነርሱ ማስመሰል ለሰዎች መርዝ ሳይሆን መድሀኒት ነው ። ሁከት ሳይሆን ሰላም ነው ። ውድቀት ሳይሆን ስኬት ነው ። 

       '' ንቃተ ህሊና ለህሊና ለአካባቢ ለሰዎች ሰላም ወሳኝ ነው ። ''     

Friday, April 18, 2025

እይታ | Perception

                                                           ጽኑዕ እምነት

       ጽኑዕ እምነት ከጥርጣሬ የነጻ ነው ። ከጥርጣሬ በፊት ያለ ጽኑዕ እምነት ፣ የየዋህነት ውጤት ነው ። መጠራጠር ከሌለ መመራመር አይቻልም ። ማሰብ ማሰላሰል ማመዛዘን አይኖርም ። ሁሉም ነገር ማሰብ ማሰላሰል ላያስፈልገው ይችላል ። ሁሉንም ሳያሰላስሉ እንዲሁ መቀበል ደግሞ መዘዙ ከባድ ነው ። ቀላል እና ግልጽ ነገርን በየዋህነት ማመን ብዙ ጉዳት አይኖረውም ። ከባድ እና ውስብስብ ነገርን በየዋህነት መቀበል ግን ዋጋ ማስከፈሉ አይቀርም ። የዋህነት የሚወልደው ጽኑዕ እምነት ደካማ ነው ። ልብን ለሌላ አዲስ እይታ ክፍት እንዳይሆን ቆልፎ ይይዛል ። ልብን የሚቆልፍ እይታ ደግሞ ጽንፈኛ ያደርጋል ። ልብን የሚከፍት እምነት ግን መጽናኛ ያደርጋል ። ልብ ቆላፊ እምነት ትክክለኛ እምነት ሳይሆን አጉል እምነት ነው ። አጉል እምነት ደግሞ በእውቀት ላይ ሳይሆን ፣ በልማድ ላይ ነው የሚመሰረተው ። ልማድ እውቀትን ሲቀድም በአብዛኛው ጥሩ አይሆንም ። እውቀትን ተከትሎ የሚገነባ ልማድ ግን ፣ ሁል ጊዜ ባይሆንም በብዛት ጥሩ ነው ። 

           የዋህነት በእውቀት ሲገዘገዝ ሳይሆን ሲታገዝ ጥሩ ነው ። የዋህነት ከተገዘገዘ ሁሉን ተጠራጣሪ ያደርጋል ። በእውቀት ከታገዘ ግን ሁሉን መርማሪ ያደርጋል ። ሰው ከጥርጥር ወደ ምርምር ከሄደ ትክክለኛ አማኝ ይሆናል ። ከጥርጥር ወደ ምርምር መሄድ ካልቻለ ግን ተንኮለኛ ከሀዲ ይሆናል ። ምንም ጭብጥ (fact) አለማግኘት ፣ የሰውን ልጅ ተጠራጣሪ ያደርጋል ። ጭብጥ (fact) ማግኘት ተመራማሪ ያደርገዋል ። ተመራማሪ ከጭብጥ (fact) ወደ ሙሉ እውነት (truth) ይሄዳል ። አጉል ተጠራጣሪ ግን መሄድ አይችልም ። ጭብጥ እምነትን ይፈጥራል ። እምነት ደግሞ በእውን የማይታየውን ሙሉ እውነት ፣ ግልጽ አድርጎ በምናብ ያሳየናል ። አጉል ተጠራጣሪ ግን ንባብ እንጅ ምናብ ስለሌለው  ለማመን ይቸገራል ። ለዚህ ደግሞ መፍትሔው ፣ የቱንም የህል ብናውቅ ፣ የዋህነትን ማጣት የለብንም ። የዋህነት እና እውቀት ሲደጋገፉ ፣ ትክክለኛ እምነት እና ጥሩ ልማድን ይፈጥራሉ ። የዋህነት እና እውቀት ሲነቃቀፉ ግን ፣ አጉል እምነት እና መጥፎ ልማድን ይፈጥራሉ ። የዋህነት እና ክፉ እውቀት አብረው አይሄዱም ። መልካም እውቀት ከየዋህነት ጋር ግን በጣም ይዋደዳሉ ። እምነታችሁ ትክክለኛ እና ጽኑዕ እንጅ አጉል እንዳይሆን ፣ መልካሙን ሁሉ እወቁ የዋህነታችሁንም ጠብቁ ። 

           ሰው በየዋህነቱ ከሚከፍለው ዋጋ በላይ ፣ የዋህነቱን በማጣቱ ይከፍላል ። በየዋህነት ብዙ መከራ ሊደርስብን ይችላል ። ነገር ግን ምንም ይሁን ምን ፣ የዋህነት መጨረሻው ክብር ነው ። የዋህነትን ማጣት ግን ፍጻሜው ውርደት ነው ። የባለጸጎች ትምክህት ፣ የዋህነትን ከማጣት የሚመጣ ነው ። የአዋቂዎች ተንኮል የዋህነትን የመተው ውጤት ነው ። የባለስልጣኖች ግፍ ፣ የዋህነትን ከመናቅ የመነጨ ነው ። እምነት እና ይቅር ባይነት የየዋህነት ውጤት ናቸው ። በዚህች ምድር ላይ መተማመን ከሌለ ፣ ህይወትም ስራም ከባድ ይሆናል ። በደልን መርሳት ከሌለ ፣ አብሮ መኖር ጭንቅ ይሆናል ። ማመን ፋታ ይሰጣል ። አለማመን ፋታ ይነሳል ። በደልን መርሳት ሰላም ያሰፍናል ። በደልን መያዝ ሁከት ይፈጥራል ። የሰላም ቁልፉ የዋህነት ነው ። ያለ የዋህነት ሰላምን ማሰብ በጣም ከባድ ነው ። የውጭ ሰላም የውስጥ ሰላም ነጸብራቅ ነው ። የውስጥ ሰላም ደግሞ በደልን የመርሳት ስጦታ ነው ። በደልን መርሳት የሚቻለው ፣ የዋህነትን ገንዘብ ማድረግ ሲቻል ነው ። ለሰላም የዋህነት ፣ ለጠንካራ እምነት ደግሞ ልባምነት አስፈላጊ ናቸው ። የዋህነት ብቻውን እምነትን ጠንካራ አያደርግም ። ጠንካራ እምነት የሚፈጠረው ፣ የዋህነት በልባምነት ሲደገፍ ነው ። 

            ልባምነት ጥንቃቄ ነው ። ሰውን ተማራማሪ የሚያደርገው ልባምነት ነው ። ስራ በጥንቃቄ ካልተሰራ ውጤቱ የከፋ ይሆናል ። ገንዘብ በጥንቃቄ ካልተያዘ ባክኖ ይቀራል ። በጥንቃቄ ያልተያዘ መድሀኒት መርዝ ይሆናል ። በጥንቃቄ ያልተያዘ ትዳር ፣ ልጆችን ልጎዳና ይዳርጋል ፣ ባል እና ሚስትን ላጤ አድርጎ ያስቀራል ። ጥንቃቄ የጎደለው የስልጣን አያያዝ ወህኒ ያስወርዳል ። ለዚህ ደግሞ የምንሰራውን ማወቅ ፣ የምናውቀውን መስራት መለማመድ አለብን ። ያኔ ልባም እንሆናለን ። አልያ ልበ ቢስ እንሆናለን ። የምንሰራውን የማናውቅ ፣ የምናውቀውን ለመስራት የማንፈልግ ከንቱዎች እንሆናለን ። አንድን ነገር አውቀን ከሰራን ፣ እምነታችን የልማድ ሳይሆን የልምድ ውጤት ይሆናል ። በደመነፍስ ከሰራን ግን እምነታችን የልማድ ውጤት ይሆናል ። ልምድ ጥሩ ልማድ ነው ። መጥፎ ልማድ ግን ልምድ ሳይሆን ለምድ ነው ። የሰውን ልጅ እውነተኛ ማንነት የሚጋርድ ሽፋን ነው ። ከእውቀት የመነጨ መጥፎ ልማድ ፣ የክፋት ውጤት ነው ። ባለ መገንዘብ የተፈጠረ ልማድ ግን የየዋህነት ውጤት ነው ። ልባምነት ከሁለቱም ነጻ የሚያወጣን ሀይል ነው ። ልባምነት የዋህነትን ከአደጋ የሚጠብቅ ወታደር ነው ። ሰው በየዋህነት ብቻ ሲኖር ፣ ሁል ጊዜ በጦርነት ቀጠና ውስጥ ይኖራል ። ልባም ከሆነ ግን ፣ ራሱን ከጦርነት ቀጠና ይጠብቃል ። ጽንፈኝነት ፣ ዘረኝነት ፣ አክራሪነት በአብዛኛው ማለት ይቻላል ፣ የዋህነት የወለዳቸው ጽኑዕ እምነቶች ናቸው ። ልብ የሚቆልፉ እምነቶች ። ከዚህ አጉል እምነት የሚታደገን ልባምነት ነው ። ጥሩውን ከመጥፎው ፣ ትክክሉን ከስህተቱ ፣ ገለባውን ከፍሬው የሚለይልን ወንፊት ነው ልባምነት ። የዋህነት እምነትን ይፈጥራል ። ልባምነት ደግሞ እምነትን ፍጹም ያደርጋል ። የዋህነት የእምነት መስረት ነው ። ልባምነት የእምነት ጉልላት ነው ። በየዋህነት እንዲሁ እናምናለን ። በልባምነት ግን አጥርተን እናምናለን ። የጠራ እምነት ደግሞ ልብን ዝግ ሳይሆን ክፍት ያደርጋል ። 

           ክፍት ልብ ትሁት ልብ ነው ። ከዘመድም ከባዳም ፣ ከሀብታምም ከደሀ ፣ ከባለስልጣንም ከተራ ፣ ከአዋቂም ከልጅም የተሻለ ሀሳብ ለመቀበል ዝግጁ ነው ። ትሁት ልብ ሚዛናዊ ነው ። ለራሱም ለማንም አያዳላም ። ለእውነት እና ለተሻለው ሀሳብ ያዳላል ። እምነታችን ጽኑዕ ብቻ ሳይሆን ፣ ጠንካራና ትክክለኛ እንዲሆን ፣ የዋህነት ብቻውን በቂ አይደለም ፣ ልባምነት በጣም ያስፈልጋል ። 

       '' እምነትን ለመፍጠር የዋህነት ግድ ይላል ፣ እምነትን ለማጠንከር ልባምነት ያስፈልጋል ። ''       

እይታ | Perception

                                                                ስንፍና   ስንፍና እየቻሉ አለመስራት ነው ። የማይችሉትን አለመስራት ግን ስንፍና አይደለም ። ምክንያቱም የሰው ልጅ ሁሉ...