Monday, April 28, 2025

እይታ | Perception

                                                   ጭንቀትን መርሳት  

 

      ለሰው የጭንቀት ምክንያቱ ብዙ ነው መራብ መጠማት መክሰር ስራ ማጣት የኑሮ ውድነት ከሰው ጋር መቀያየም እና ሌሎች ብዙ ምክንያቶች ሊጠቀሱ ይችላሉ የጭንቀትን ምክንያቶች በጠቅላላው የተፈጥሮ እና ሰው ሰራሽ ብለን ልንመድባቸው እንችላለን ። ውስጣዊ እና ውጫዊ ምክንያቶች ተብለው ሊፈረጁ ይችላሉ ሰው ራሱ ያመጣውን ጭንቀት ሲመልስም መመለስ ሲሳነውም ይስተዋላል ተፈጥሮ የሚያመጣበትን ጭንቀት ግን ቀድሞ ካልተከላከለ በስተቀር አንዴ ከሆነ አምኖ መቀበል እንጅ መልሶ መቀልበስ ፈጽሞ አይችልም ለምሳሌ የአየር ንብረትን አዛብቶ ዶፍ ዝናብ እንዳይዘንብ የጎርፍ አደጋ እንዳይከሰት ማድረግ አይችልም ከሂማሊያ ተራራ በረዶ እንዳይቀልጥ መመከት አይችልም ደሃው ህዝብ በድርቅ እንዳይጎዳ መከላከል ከባድ ይሆንበታል ይህንን መቀበል እንጅ መቀልበስ አይችልም መከላከል ግን ይችላል በምን ? ከተባለ ተፈጥሮን በመንከባከብ እና በመጠበቅ አልያ ምድር በጸሃይ መጋል ብቻ ሳይሆን በካንሰር ህመምተኛ ትሞላለች ይህ በሽታ ደግሞ ፍቱን መፍትሔ ያልተገኘለት የበሽታዎች ሁሉ በኩር ነውና ለእርሱ እጅ መስጠት እንጅ መታገል እና መጋፈጥ ትርፉ ከንቱ ድካም ነው ሲቀጥል ሞትን በቀጠሮ መጠበቅ ግድ ይሆናል

ሞትን በቀጠሮ መጠበቅ ደግሞ ጭንቀትን እጅግ ከባድ ያገርገዋል ይህ በቀላሉ የሚረሳ ሳይሆን የማይረሳ ጭንቀት ነው

     ይህን መርሳት ማለት ለመማር ዝግጁ አለመሆን ነው አለመማር ደግሞ መቅለል የሚችለውን ችግር ይበልጥ ከባድ ያደርገዋል በየጊዜው ለአንድ ችግር ተመሳሳይ መልስ እንድንሰጥ ያስገድደናል አንድ ሰው ለቀድሞ ችግሩ መልስ መስጠት ከከበደው ከችግሩ ተምሮ ሳይሆን በችግሩ ተማሮ ነው ያለፈው መልስ መስጠት ከቀለለው ግን ፣ በችግሩ ተማሮ ሳይሆን ከችግሩ ተምሮ ነው ያለፈው ለዚህ ነው የተማሩ ሰዎች ምን ጊዜም ችግርን አክብደው ሳይሆን አቅልለው የሚመለከቱት ዩኒቨርስቲ ገብተው የተማሩ ሳይሆን ከህይወት የተማሩ ያልተማሩ ሰዎች ደግሞ ሁል ጊዜ ችግርን አቅልለው ሳይሆን አክብደው የሚመለከቱት ፣ ዩኒቨርስቲ ገብተው መማር ስላልቻሉ ሳይሆን ፣ ከህይወት መማር ስላልቻሉ ነው ችግርን አቅልሎ ለመመልከት ከህይወት መማር ግድ ነው

          ከህይወት ለመማር ጭንቀትን ሙሉ በሙሉ መርሳት ተገቢ አይደለም ምክንያቱም ችግር ጭንቀትን ይወልዳል ጭንቀት ሀሳብን ይወልዳል ሀሳብ ፣ ጥበብ እና እውቀትን ይወልዳል ጥበብ እና እውቀት ደግሞ ችግርን ወደ መፍትሔ ፈተናን ወደ እድል ይቀይራሉ ያኔ በመጀመሪያ የከበደው ችግር ዳግም ሲከሰት ቀላል ይሆናል መቶ ኪሎ የነበረው አስር ኪሎ ይሆናል ማለት ነው  

ግን ጭንቀት ሁሉ የመፍትሔ ሀሳብ ይወልዳል ማለት አይደለም ጭንቀት በመጠኑ ሲሆን እና ከመጠን በላይ ሲሆን ይለያያል

 ጭንቀት በመጠኑ ሲሆን የሚያሞቅ እሳት ነው ከመጠን በላይ ሲሆን የሚያነድ እሳት ነው ስለዚህ ጭንቀት በመጠኑ ሲሆን ነው የመፍትሔ ሀሳብ የሚወልደው አልያ የመፍትሔ ሀሳብ ሳይሆን የህመም ወይም የእብደት ሀሳብ ነው የሚወልደው አሙቆ የሚያነሳሳ ሳይሆን አግሎ የሚገድል ይሆናል ።            

          ጭንቀት አማራሪም አስተማሪም ገጽ አለው ከመፍትሔ ይልቅ ችግር ላይ ካተኮርን አማራሪ ገጹ ይበዛል ከችግሩ ይልቅ መፍትሔው ላይ ካተኮርን አስተማሪ ገጹ ይሰፋል ለዚህ ደግሞ የኛ እይታ ወሳኝ ነው ደራሲው እንዳለው ‘’ አረፍተ ነገር ሲነበብ ስርዓተ ነጥብ ይታያል እንጅ አይነበብም ። በተመሳሳይ በችግር ወይም በጭንቅ ጊዜ እንደ ስርዓተ ነጥቡ የሚታዩ እንጅ የማይነበቡ ነገሮች አሉ አረፍተ ነገር ስናነብ ነጠላ ሰረዝ እያልን ብናነብ በጀመሪያ ስሜት አይሰጥም ፣ ሲቀጥል አረፍተ ነገሩ ትርጉም ያጣል።  እንደዚሁም በችግር ወይም በጭንቅ ጊዜ የማይታዩ ድርጊቶች እና ክስተቶች  የማይሰሙ ንግግሮች ቦታ ካገኙ ችግርን እድል አድርገው ሳይሆን በደል አድርገው ነው የሚያሳዩት ከዛ ህይወት ትርጉም አልባ ሆና ትሳላለች ስለዚህ በችግር ወይም በጭንቅ ጊዜ በንቀት የተሞሉ ድርጊቶች እና ክስተቶች አሉታዊ ንግግሮች ትኩረት እና ቦታ ሊሰጣቸው አይገባም

ነገር ግን ተስፋ የሚሰጡ ድርጊቶች እና ትእይንቶች እምነትን የሚያጠነክሩ አዎንታዊ ንግግሮች ትኩረት ሊሰጣቸው ይገባል

 ምክንያቱም እነዚህ ነገሮች ችግርን በደል ሳይሆን እድል አድርገው ያሳዩናልና ስለዚህ እይታችንን እናስተካክል ከመጥፎው ይልቅ ጥሩውንከችግሩ ይልቅ መፍትሔውን ከፈተናው ይልቅ እድሉን በእምነት እና በተስፋ ለማየት እንጣር ያኔ የጭንቀት አማራሪ ገጹ ሳይሆን አስተማሪ ገጹ ጎልቶ ይታያል የእብደት ሀሳብ ሳይሆን የመፍትሔ ሀሳብ ይወለዳል ።  

        ጭንቀትን መርሳት ለዘላቂ ሰላም መፍትሔ አይሆንም ከችግር ወይም ከጭንቀት መማር ነው ዘላቂ ሰላም የሚያመጣው ጭንቀትን ለመርሳት የሚታገል ሰው ህይወቱን የሚጎዳ እርምጃ ይወስዳል ሲጨንቀው አልኮል ይታየዋል መርዝ መርዝ ይለዋል ተስፋ ቢስ ይሆናል ሞቱን ብቻ ይመኛል ለችግሩ ወይም ለጭንቀቱ ጊዜያዊ መፍትሔ እንጅ ዘላቂ መፍትሔ አይታየውም  

      ከጭንቀት ለመማር የሚጥር ሰው ግን ህይወቱን የሚጠቅም እርምጃ ነው የሚወስደው ፈጣሪውን ይማጸናል መልካም ሰዎችን እርዳታ ይጠይቃል መፍትሔ ፍለጋ መጽሐፍ ያገላብጣል ለጊዜ ጊዜ ሰጥቶ ይጠብቃል ትእግስትን መርሑ ያደርጋል በጽናትም በጥናትም ችግሩን ወይም ጭንቀቱን ይሻገራል ሁሌም ተስፋ ያደርጋል በእምነት መከራን ያልፋል          

  ስለዚህ ሰው ጭንቀቱን ለመርሳት ሳይሆን መታገል ያለበት ከችግር ወይም ከጭንቀት ለመማር ነው ጥረት ማድረግ ያለበት ከጭንቀት ለመማር ስንጥር የጭንቀት ማቅለያ ስልትን እናውቃለን ለአንድ ጊዜ ብቻ የሚያገለግል ሳይሆን ለህይወት ዘመን የሚያገለግል ስልት ይሆናል ጭንቀትን ለመርሳት ስንታገል ግን ራስን ማቅለያ ወይም ማጥፊያ ስልት ነው ፊታችን ላይ ድቅን የሚልብን ከጭንቀቱ የተማረ ኑሮው ይቀላል ። ጭንቀቱን ለመርሳት የታገለ ራሱ ይቀላል ። ከጭንቀት ከተማርን ጭንቀቱ ያልፋል ። ለሌላም ጊዜ ተሞኩሮ በመሆን ማለፊያ ይሆነናል ። ጭንቀትን ለመርሳት ከታገልን ግን ጭንቀቱ ሳይሆን እኛ እናልፋለን።

 

       ‘’ ጭንቀትን ከመርሳት ከጭንቀት መማር የተሻለ ነው ። ‘’   

                                 ክፍል 1

                                                                               

No comments:

Post a Comment

እይታ | Perception

                                                                ስንፍና   ስንፍና እየቻሉ አለመስራት ነው ። የማይችሉትን አለመስራት ግን ስንፍና አይደለም ። ምክንያቱም የሰው ልጅ ሁሉ...