የጋራ ዓላማ
የጋራ ዓላማ ለአብሮነት እጅግ አስፈላጊ ነው
። ነገር ግን አንድ ግለሰብ ፣ የራሱ አላማ ከሌለው ፣ የጋራ አላማ ሊኖረው አይችልም ። አላማ የሌለው ሰው ፣ የአላማ ህልውና
አይገባውም ። የሰው ልጅ ለአላማ እንደተፈጠረ መረዳት አይችልም ። የሰው ልጅ ለመብላት ብቻ ሳይሆን ፣ ለማብላት ጭምር እንደተፈጠረ
አይታየውም ። በመልበስ ብቻ ሳይሆን ፣ በማልበስ መደሰት እንደሚችል አይሰማውም ። ያለ ዓላማ የሚኖር ሰው ፣ የማግኘት እንጅ የመገኘት
ትርጉም አይገባውም ። የሚበላውን ፣ የሚጠጣውን ፣ የሚለብሰውን ካገኘ በቃው ። መብላት መጠጣት መልበስ ፈልገው ፣ ለሚጣሩ ድምጾች
መገኘት መቻል ለእርሱ ዋጋ ቢስ ነው ። የእርሱ መኖር ለሌሎች ምን ያህል አስፈላጊ እንደሆነ አያውቅም ። በሌሎች መኖር ውስጥ ፣
የእርሱ እስትንፋስ እንዳለች አይረዳም ። ህይወትን በአጋጣሚ እንጅ በእቅድ መኖር አይችልም ። በእርግጥ ሰው በእቅዱ ልክ መኖር
አይችልም ። ያለእቅድ መኖር ግን ትልቅ ስንፍና ነው ። ሰው በአጋጣሚ ኖሮ ፣ በአጋጣሚ ሞተ ቢባል እጅግ ያሳዝናል ። በእቅድ ኖሮ
በአጋጣሚ ሞተ ቢባል ፣ የተፈጥሮ ሂደት ነው አምኖ ለመቀበል ብዙ አይከብድም ። ምክንያቱም አቅዶ የሚሞት ማንም የለም ። ምናልባት
በኑሮ ጫና ወይም በተለያየ ምክንያት ፣ ሰው ራሱን ለማጥፋት ካላሰበ በቀር ። ያም ቢሆን ታስቦ ታቅዶ ሳይሆን ፣ በስሜት የሚከወን
ድርጊት ነው ። ሰው አስቦ ራሱን ያድናል እንጅ ራሱን አይገድልም ። ማሰብ ማለት የሚጠቅመውን የተሻለውን መምረጥ ነው ። አለማሰብ
ደግሞ የሚጎዳውን የባሰውን መወሰን ወይም መምረጥ ነው ።
ያለ ዓላማ መኖር ያለ ማሰብ ውጤት ነው ። ሰውን ሰው የሚያደርገው
ማሰብ መቻሉ ነው ። በደመ ነፍስ ከመኖር የሚታደገው ማሰቡ ነው ። የማይታየውን ማየት ፣ የማይሰማውን መስማት ፣ ከቁሱ አለም ጀርባ
መንፈሳዊ አለም እንዳለ ማመን እና ማረጋገጥ የቻለው በማሰቡ ነው ። እንስሳት ለመኖር ምቹ ተፈጥሮ ይፈልጋሉ ። ምክንያቱም ተፈጥሮን
ምቹ የማድረግ ብቃት የላቸውም ። እነርሱ ጫካው ምድረ በዳ ሲሆን ጥለው ይሸሻሉ ። አልያ ሁሉም አንድ በአንድ ፣ የሞት ሲሳይ ይሆናሉ
። ይህ የሚሆነው ማሰብ ስለማይችሉ ነው ። ሰው ግን እንደዛ አይደለም ፣ ማሰብ ስለሚችል ተፈጥሮ ምቹ ባትሆንም ፣ ምቹ ተፈጥሮን
መፍጠር ይችላል ። ምድረበዳን ዉብ መኖርያ ማድረግ ይችላል ። ግን ይህን የማድረግ ብቃት ያለው ፣ ዓላማ ያለው ሰው ነው ። ዓላማ
የሌለውማ ማሰብ ስለማይችል ፣ እንደ እንስሶቹ ምቹ ተፈጥሮን ይፈልጋል ። አልያ ሞት አፈፍ አድርጎ ይቀበለዋል ። የተሻለ ለማሰብ
ዓላማ ያስፈልጋል ። ሰው ዓላማ ከሌለው ደመነፍሳዊ ይሆናል ። በደመነፍስ ያለ ሰው ፣ በስሜት እንጅ በማስተዋል መኖር አይችልም
። በስሜት ደግሞ የተሻለ ማሰብ በፍጹም አይቻልም ።
አላማ አቅጣጫ ነው ። የህይወት መነሻም መድረሻም ነው ። አላማ
የሌለው ሰው አቅጣጫ ቢስ ነው ። መነሻም መድረሻም የለውም ። እድሜው እንዲሁ ይሄዳል ፣ እርሱ ግን መሄጃ የለውም ። ቀን ይመሻል
ይነጋል ፣ ለእርሱ ግን መሸም ነጋ ለውጥ የለውም ። ምክንያቱም መለወጥ አይፈልግም ። ለውጥ ጠላቱ ነው ። ከማላውቀው መልአክ ፣
የማውቀውን ሰይጣን የሙጥኝ ብል ይሻላል ብሎ የሚኖር ነው ።
ሰይጣን ስላወቅነው ደግ አይሆንም ። ባናውቀውም
ከክፋቱ ፈቀቅ አይልም ። ክፉ ሰውም እንደዛ ነው ። ስለቀረብነው የዋህ አይሆንም ። ስለራቅነውም ተንኮሉን መስራት አያቆምም ።
የለመድነው ክፉ ነገር ፣ እኛ ስለወደድነው መልካም አይሆንም ። ከጠላነው ግን ነገሩ ባይለወጥም ፣ እኛ እንለወጣለን ። ክፉን ነገር
መውደዳችን የነገሩ እስረኛ ያደርገናል ። መጥላታችን ግን ነጻ ያወጣናል ። ነጻ ለመውጣት ግን ዋጋ ያስከፍላል ። ያለ ዋጋ የሚገኝ
ነጻነት የለምና ። አላማ የሌለው ሰው ክፉን ወይም መጥፎን ነገር ለመተው በጣም ይከብደዋል ። በተመሳሳይ ጥሩውን ነገር ለመቀበል
እጅግ ይጨንቀዋል ። የጋራ አላማ ለውጥ ይፈልጋል ። መለወጥ የማይችል ሰው ለጋራ አላማ እንቅፋት ነው ። አላማ የሌለው ሰው ፣
ለውጥን ለመቀበል ዝግጁ ስላልሆነ ፣ ለጋራ አላማ መሰናክል ነው ።
ዓላማ ያለው ሰው ግን ቢያውቅም ባያውቅም መልአክን አይጠላም ።
መልካም ነገርን አይተውም ። መልአክ መልአክ
ነው ፣ እኛ ስለፈራነው መልካምነቱ አይቀየርም ብሎ ያምናል ። ከዘመድ ሰይጣን ፣ ባዳ መልአክ ይሻላል የሚል እይታ አለው ። ሁሌም
አዲስ ነገር የማወቅ ጉጉት አለው ። ለመለወጥ ዝግጁ ነው ። በጋራ መስራት በአንድነት ወደፊት መሄድ ደስታው ነው ። ነገር ግን
የጋራ መልካም አላማ እንጅ ፣ ክፉ አላማ ካላቸው ጋር በፍጹም አይተባበርም ። አብረን እንስራ ከሚሉት ጋር እንጅ ፣ አብረን እናጭበርብር
ከሚሉት ጋር ህብረት የለውም ። ሰርተን እንገባ እንጅ ፣ ሰርቀን እንገባ አይመቸውም ። እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል የሚል ሳይሆን
፣ እኔ ኖሬ ሰርዶ ላብቅል የሚል ነው ። ለዛሬ ሲል ነገን አያፈርስም ። ለነገ ዛሬ ይኖራል ።
የእርሱ ማጣት ሳይሆን ፣ የልጆቹ ማግኘት
ይታየዋል ። የልጆቹ መጥገብ በምናብ ስለሚታየው ፣ የእርሱ መራብ ብዙ አይስጨንቀውም ። አላማ ያለው ሰው ፣ በዛሬ ዉስጥ ነገ ስለሚታየው
ለጋራ አላማ ምቹ ፍጥረት ነው ።
ምቾትን የሚፈልጉ ሰዎች ፣ ዓላማ ቢኖራቸውም ለጋራ ዓላማ ብዙ አይመቹም
። ትራፊ ለመስጠት ፣ ትርፍ መኪናቸውን ማጣት ይፈራሉ ። ልብሳቸውን ከመስጠት ይልቅ ፣ ቁም ሳጥናቸውን የልብስ ሙዚየም ማድረግ
ይመርጣሉ ። ሀኪም ካላዘዛቸው ፣ ባዶ እግር መሄድ ይፈራሉ ። በባዶ እግር የሚሄዱትንም ይፈራሉ ። መኖር እንጅ ማኖር አይችሉም
። መስራት እንጅ ማሰራት አይሆንላቸውም ። መቀመጥ እንጅ ማስቀመጥ ህመማቸው ነው ። ሲደመጡ ደስ ይላቸዋል ። ሲያዳምጡ የበታችነት
ስሜት ይሰማቸዋል ። ሲከበሩ ጮቤ ይረግጣሉ ። ሲናቁ መብት ይረግጣሉ ። ለመከበር የተፈጠሩ እንጅ ፣ ለማክበር የተፈጠሩ አይመስላቸውም
። ለጥቅማቸው ይሽቆጠቆጣሉ ። ለክብራቸው ግን ያንቀጠቅጣሉ ። ምርጥ እና ቆንጆው የእነርሱ ፣ መጥፎ እና ቆሻሻው የሌላ ይመስላቸዋል
። አላማቸው ፍቅርን ማብዛት ሳይሆን ፣ ገንዘብን ቁስን ጌጥን ማብዛት ነው ። ራሳቸውን ጭምር ማብዛት አይፈልጉም ። ያወቁትን በማሳወቅ
፣ የቻሉትን በማሳየት ፣ እነርሱን የሚመስሉ ሌሎች እንዲፈጠሩ ምንም ጥረት አያደርጉም ። በአጭሩ ለምቾት የሚኖሩ ፣ ለጋራ አላማ
አይመቹም ።
የጋራ አላማ የተስተካከለ የግለሰብ አላማን ይፈልጋል ። በፓፒዮ መጽሐፍ
ላይ ፣ እንደ ተተረከው ታሪክ አላማን ማስተካከል ያስፈልጋል ። ፓፒዮ ከእስር ቤት እንደ ወጣ ፣ ዓላማው ገንዘብ ማግኘት ነበር
።
ይህ ዓላማው ግን ህገ ወጥ እንዳደረገው ፣
በብዙ ውጣ ውረድ ዉስጥ መረዳት ቻለ ። በመቀጠል አላማውን አስተካከለ ። በጀመሪያ ገነዘብ ሳይሆን ስራ ማግኘት እንዳለበት ራሱን
አሳመነ ። ከስራ ገንዘብን ካስቀደምን ፣ ሥርዓት አልበኛ ወይም ህገወጥ የመሆን እድላችን ሰፊ ነው ። ከገንዘብ ስራን ካስቀደምን
ግን ፣ ስርዓትም ይኖረናል ፣ ህጋዊም እንሆናለን ። ልክ ፓፒዮ እንዳደረገው ፣ ገንዘብን ከስራ ካስቀደምን ፣ ሀሳባችን መስራት
ሳይሆን መስረቅ ይሆናል ። ስራን ከገንዘብ ካስቀደምን ግን ፣ ሀሳባችን መስራት እንጅ መስረቅ አይሆንም ።
‘’ የተስተካከለ አላማ ያለው የጋራ አላማን መፍጠር ይችላል ። ‘’
ክፍል 1
No comments:
Post a Comment