ስሜታዊነት እና እምነት
እምነት በስሜት አይገነባም ። እምነት ሲሞቀን የምንገነባው ፣ ሲበርደን ደግሞ የምናፈርሰው ወረት አይደለም ። ስናገኝም ስናጣ ፣ ቢደላንም ባይደላንም ፣ በክፉም ሆነ በበጎ ሁኔታ ውስጥ ይዘን የምንገኘው ማንነት ነው ። ድህነትም ባለጸግነትም ፣ መሀይምነትም ምሁርነትም እምነትን አያስጥልም ። እምነት በፈተና ብዛትም አይፈርስም ። እንዲያውም ፈተና እምነት የሚጠነክርበት ወጌሻ ነው ። ስሜታዊነት የእምነት ተቃራኒ ነው ። ስሜታዊ ሰዎች ሲያገኙ ሌላ ፣ ሲያጡ ደግሞ ሌላ ሰው ናቸው ። ሲያተርፉ አመስጋኝ ሲከስሩ ወቃሽ ናቸው ። ሲሞላ እብሪተኛ ሲጎድል ደግሞ ትሁት ናቸው ። ስሜታዊ ሰዎች ሲደሰቱ ይሆናል ፣ ሲያዝኑ ደግሞ አይሆንም ማለት ይቀናቸዋል ። እምነት ግን በሀዘንም ሆነ በደስታ ይሆናል ማለት ነው ። ስሜታዊነት መለወጥ ሳይሆን መለዋወጥ ነው ። እምነት በሂደት አንድ ጊዜ ሊለወጥ ይችላል ። በአንድ ቀን ግን ሺ ጊዜ አይለዋወጥም ። ስሜታዊነት በአንድ ጀምበር ብዙ ጊዜ መለዋወጥ ነው ። በአንድ ቀን ውስጥ ሶስት ወይም አራት ሰው መሆን ነው ። በአንድ አካል ውስጥ ብዙ ሰው መሸከም ነው ። ጥዋት እና ማታ ፣ ቀንና ጨለማ ሲፈራረቁ አብሮ መፈራረቅ ነው ስሜታዊነት ። ስሜታዊ ሰዎች በአጭሩ እምነት የለሽ ናቸው ማለት ይቻላል ።
እምነት ሙሉነት ነው ። የሚያምን ሰው ልበ ሙሉ ነው ። በወዳጅም በጠላትም ፊት ያው ነው ። ለጠላት ፈርቶ የሚቀይረው ነገር አይኖርም ። ለወዳጅ አዝኖ የሚለውጠው ነገር የለም ። ምክንያቱም እምነት እውቀት ላይ ነው የሚመሰረተው ። እውቀት ደግሞ እውነት ላይ ነው የሚመሰረተው ። ስለዚህ በእምነት መኖር ለማንም ሳይሆን ለእውነት መወገን ነው ። እውነት ሁል ጊዜም እውነት ነው ። በጊዜ መቀየር ውስጥ አብሮ አይቀየርም ። ጥዋት እውነት የነበረው ከሰአት ውሸት አይሆንም ። ትላንት እውነት የነበረው ነገ ውሸት አይሆንም ። በዘመን ብዛት እውነት አያረጅም ። ከዚህ በተቃራኒ ስሜታዊነት ባዶነት ነው ። ነፋስ ወደ ፈለገው አቅጣጫ እንደሚወስደው ባዶ ፈስታል መሆን ነው ። በስሜታዊነት ውስጥ ይዞ መልቀቅ እንጅ ይዞ መጽናት የለም ። ለቆ መያዝ ፣ ይዞ መልቀቅ የተለመደ ነው ። በአንዴ ሙሉ መሆን ፣ ከዚያ ደግሞ ወዲያው ባዶ መሆን የሜታዊነት ውጤት ነው ። በጣም የሚያሳዝነው ስሜታዊ ሰዎች ፣ መርጦ መያዝም ሆነ መልቀቅ አይችሉም ። ሲይዙም ሲለቁም ሳይመርጡ ነው ። ወይ ባዶ አልያም ሙሉ የሚሆኑትም ለዚያ ነው ። ስለዚህ በአግባቡ መቀበልም ሆነ መስጠት አይችሉም ።
ስሜታዊ ሰዎች ዘመድ ሲያዩ ሙሉ ይሆናሉ ። ባዳ መሀል ሲገኙ ባዶ ይሆናሉ ። ሲያገኙ ልባቸውን ያሳብጣሉ ። ሲያጡ ደግሞ ይጎብጣሉ ። በሰው መተማመን ይችላሉ ፣ በራሳቸው መተማመን ግን አይችሉም ። አይደለም የማይችሉትን የሚችሉትን መስራት ይፈራሉ ። ሰዎች በእነርሱ ችሎታ እያመኑ ፣ እነርሱ ግን ያላቸውን ችሎታ አምነው አይቀበሉም ። ሁል ጊዜም ውጪያዊ ማረጋገጫ ( external validation ) ይፈልጋሉ ። በራስ ሞራል ሳይሆን በሰው ሞራል መስራት ይወዳሉ ። የሚያሞግስ ሲኖር ወዲያው ይሞቃሉ ። ሲወቀሱ በቅጽበት ቅዝቅዝ ይላሉ ። ሲደነቁ በፍጥነት ይሮጣሉ ። ሲተቹ ደግሞ ለመራመድ ይዘገያሉ ። ጥንቸል የነበሩት ኤሊ ይሆናሉ ። ስሜታዊ ሰዎች ፎርጅድ ባትሪ ናቸው ። ቻርጅ ሲደረግ ወዲያው የሚሞላ ፣ ሲነቀል ደግሞ ዜሮ የሚሆን የደከመ ባትሪ ናቸው ። ወለል ብሎ የተከፈተ ወይም ጥርቅም ብሎ የተዘጋ በራፍንም ይመስላሉ ። ልባቸውን ገርበብ ማድረግ አይችሉም ። የመጣውን ነገር ወይ በሙሉ ይቀበሉታል አልያም ምኑንም አይቀበሉትም ። በእምነት መኖር ግን ልብን ገርበብ ማድረግ ነው ። መርጦ መቀበል እና መጣል ነው ። እንደፍላሽ የሚጫነውን ሁሉ መቀበል ሳይሆን ፣ እንደወንፊት እያጣሩ መውሰድ ነው ። ጉድለትን እየሞሉ መሄድ እንጅ በአንዴ ሙሉ ወይም ባዶ መሆን አይደለም ።
እምነት ሚዛናዊነት ነው ። እምነት ውስጥ እውነትነት አለ ። እውነትነት ውስጥ ደግሞ ሚዛናዊነት አለ ። በእምነት መኖር ፍትሀዊ ያደርጋል ። ምክንያቱም ሰው በእምነት ሲኖር በአጀብም ብዛት ሆነ ፣ በወጀብም ፍርሀት ከእውነት አይሸሽም ። በአጀብ ብዛት ጽንፍ አይዝም ። በወጀብ ፍርሀት ጥግ አይዝም ። መሀል ላይ እውነትን ይዞ ነው የሚገኘው ። እውነት ደግሞ ከምንም በላይ ወሳኝ ሚዛን ነው ። ያለ እውነት ሚዛናዊ ያለ እምነት ፍትሀዊ መሆን ከባድ ነው ። ከዚህ በተቃራኒ ስሜታዊነት ኢ-ሚዛናዊነት ነው ። ስሜታዊ ሰዎች አጀብ ሲበዛ እውነቱን ሳያጣሩ ጽንፍ ይይዛሉ ። ወጀብ ሲገጥማቸው ደግሞ እውነቱን ሽምጥጥ አድርገው ይክዳሉ ። እነርሱ ወደ ነፈሰው የሚነፍሱ ነፍስ አልባ ፈጥረቶች ናቸው ። ለእነርሱ ሚዛን እውነት ሳይሆን ብዛት ነው ። እውነት ደግሞ በብዙ ልብ ውስጥ ሳይሆን በንጹህ ልብ ውስጥ ነው የሚገኘው ። ስሜታዊ ሰዎች ንጹህ ልብ የላቸውም ። ምክንያቱም መርጠው መቀበል አይችሉም ። መምረጥ አለመቻል ንጽህናን ያሳጣል ። ንጽህና በሌለበት ሚዛናዊነት ፈጽሞ አይታሰብም ። ሚዛናዊ ለመሆን ከዘረኝነትም ከጽንፈኝነትም ንጹህ መሆን ያስፈልጋል ። ስሜታዊነት ወይ ዘረኛ አልያም ጽንፈኛ ያደርጋል ፣ ሚዛን ያስታል ።
የስሜት ብስለት የእምነት ውጤት ነው ። ምክንያቱም የሚያምን ሰው ከጊዜያዊ ስሜት ይልቅ ለዘላቂ ስሜት ተገዥ ነው ። ዘላቂ ስሜት የስሜት ብስለት ማሳያ ነው ። ጊዜያዊ ስሜት ግን የስሜት ብስለት ሳይሆን የስሜት ስለት ነው ። በጊዜያዊ ስሜት ተነሳስተው ያለሙ ሳይሆን ያጠፉ ብዙ ናቸው ። የገነቡ ሳይሆን ያፈረሱ ጥቂት አይደሉም ። በግ ሳይሆን ሰው ያረዱ ቁጥራቸው ቀላል አይደለም ። በስሜት ለመብሰል በእምነት መጠንከር ግድ ነው ። በትእግስት የሚያምን ሰው በንዴት ቶሎ ቱግ አይልም ። በትህትና የሚያምን ሰው ለቁጣ አይቸኩልም ። በየዋህነት የሚያምን ሰው በቂም ራሱን ሲመርዝ አይኖርም ። በቅንነት የሚያምን ለነገር ፈጣን አይሆንም ። በልባምነት የሚያምን ሁሉን በመቀበል እና በመስጠት አይኖርም ጠንቃቃ ነው ። እምነት የቀደመው ስሜት ጠቃሚ ነው ። እምነትን የቀደመ ስሜት ግን ጎጂ ነው ። ስሜት ለእምነት ሲገዛ የሰው ልጅ ክብሩ ከፍ ይላል ። እምነት ለስሜት የተገዛ እለት ግን የሰው ልጅ ክብሩ ዝቅ ይላል ። ስለዚህ ስሜትን ለእምነት እንጅ ፣ እምነትን ለስሜት አናስገዛ ።
'' ስሜታዊነት በአንድ እግር መቆም ነው ። እምነት ግን በሁለት እግር መቆም ነው ። ''