Saturday, August 9, 2025

እይታ | Perception

                                                             አጋጣሚን መፍጠር 

    አጋጣሚ ያልታሰበ ነገር ነው ። የታሰበ ነገር ሁሉ አጋጣሚ ሊሆን አይችልም ። አጋጣሚ ድንገቴ ነው ። በድንገት ማጣት መሞት መለያየት መክሰር መጎዳት አጋጣሚዎች ናቸው ። ማጣት ብቻ አይደለም ፣ ማግኘትም ድንገተኛ ከሆነ አጋጣሚ ነው ። አጋጣሚ ሀዘንም ደስታም ነው ። ዕጣም ጣጣም ነው ። መርገምም በረከት ነው ። ስኬትም ውድቀትም ነው ። ክብርም ውርደትም ነው ። አጋጣሚ ብዙ ነገር ነው ። አጋጣሚ የምን ውጤት ነው ቢባል ፣ በቀላሉ መልስ የማይገኝለት ጥያቄ ነው ። በቃ አጋጣሚ የእጣ ፈንታ ጉዳይ ነው ። በአጋጣሚ የማያምኑ ሰዎች ፣ አጋጣሚ የሚባል ነገር የለም ይላሉ ፣ ነገር ግን እነርሱ የለም ስላሉ አጋጣሚ አይኖርም ማለት አይደለም ። አጋጣሚ የፈጣሪ ድንቅ ጥበብ መገለጫ ነው ። አጋጣሚ የለም ማለት ሰው የተጻፈለት ታሪክ እንጅ ራሱ የሚጽፈው ታሪክ የለውም ማለት ነው ። የራሱ አሻራ ( legacy ) አይኖረውም ። የመምረጥ ነጻነትም ሊኖረው አይችልም ። የሰው ልጅ የነጻነቱ ማሳያ አንዱ አጋጣሚ ነው ። ፈጣሪ የሰው ልጅ የተጻፈለትን ብቻ እንዲኖር ሳይሆን ፣ አዲስ ታሪክ ጽፎ እንዲኖር ነጻ አድርጎ ነው የፈጠረው ። በዚህ የነጻነት ጉዞ ውስጥ ፣ አጋጣሚ ለሰው ልጅ ፈተና እና እድል ሆኖ ይከሰታል ። 

   አጋጣሚ ጥሩም መጥፎም ሊሆን ይችላል ። ጥሩ አጋጣሚ እድል ነው ። መጥፎ አጋጣሚ ፈተና ነው ። ብልሆች መጥፎ አጋጣሚን ወይም ፈተናን ወደ እድል መቀየር ይችሉበታል ። ጥሩ አጋጣሚን ወይም እድልን በአግባቡ መጠቀምም ያውቁበታል ። ሰነፎች ግን ፈተናን ወይም መጥፎ አጋጣሚን ወደ እድል መቀየር አይችሉም ። እድልን ወይም ጥሩ አጋጣሚን መጠቀምም አይችሉም ። ሰነፎች እድልን ወደ ፈተና ፣ በረከትን ወደ መርገም ፣ መፍትሄን ወደ ችግር ፣ ዕጣን ወደ ጣጣ መለወጥ ነው የሚችሉት ። ድንገት ያገኙትን ምርጥ ወዳጅ ጠላት ያደርጉታል ። እድል ሆኖ የመጣላቸውን ገንዘብ ሱስ ይገዙበታል ። መኪና የሚገዙበትን እድል ቁማር ላፍ ያደርግባቸዋል ። የሚከበሩበትን እድል አላግባብ በመጠቀም ይዋረዱበታል ። ፍቅሩን ጥላቻ ፣ ፈውሱን በሽታ ፣ መድሀኒቱን መርዝ ያደርጋሉ ። አጋጣሚ ከምንም በላይ መማሪያ ነው ። ጥሩ አጋጣሚ ማለፊያ ነው ። መጥፎ አጋጣሚ ደግሞ መማሪያ ነው ። እንዲህ የሚሆነው ግን ለሰነፎች ሳይሆን ለብልሆች ነው ። ለሰነፎች ጥሩ አጋጣሚ መዋረጃ ፣ መጥፎ አጋጣሚ ደግሞ መማሪያ ሳይሆን መማረሪያ ነው ። 

   ህይወት አጋጣሚ ባይኖር የሆነ አይነት ጣዕም ይጎድላታል ። አጋጣሚ የህይወት ቅመም ማጣፈጫ ነው ። በመጥፎም ይሁን በጥሩ ፣ መጠቀም ለቻለ አጋጣሚ ቅመም ነው ። መጠቀም ላልቻለ ግን ቅመም ሳይሆን ቂም ነው የሚሆነው ። ቂም ደግሞ የህይወት ማምረሪያ ሬት ነው ። ምክንያቱም ይህ ቂም የሚሆነው በፈጣሪ ላይ ነው ። ሰው ያለምንም እድል እና ፈተና ፣ እቅዱን ማሳካት መቻሉ ደስታውን ሙሉ አያደርግለትም ። እቅድ አጋጣሚን ይወልዳል ፣ አጋጣሚ ደግሞ ደስታን ሙሉ ያደርጋል ። በአጋጣሚ ያልተፈተነ ወይም በእድል ያልታገዘ እቅድ ፣ በሰው ውስጥ አዲስ ስሜትን የመፍጠር አቅም አይኖረውም ። ስለዚህ ህይወት ወይ በድል አሊያም በእድል ነው ሙሉ የምትሆነው ። ስላቀድን ብቻ ህይወት ሙሉ አትሆንም ፣ ሙሉነትም አይሰማንም ። ለዚህም ነው '' plan for expected as well as un expected. '' የሚባለው ። ለምንጠብቀው ብቻ ሳይሆን ለማንጠብቀውም ነገር መዘጋጀት ግድ ነው ። ያኔ አጋጣሚን ለመጠቀም በቂ ስነ ልቦናዊ አቅም ይኖረናል ። አልያ በአጋጣሚ ምክንያት አቅም ሳይሆን የሚፈጠረው ፣ ቅስም ነው የሚሰበረው ።

   ሰው አስቦ አጋጣሚን መፍጠር ባይችልም ፣ አስቦ ማቀዱ ግን አጋጣሚ እንዲፈጠር ምክንያት ይሆናል ። መልካም አጋጣሚ የማቀድ ውጤት ነው ። '' ሰው ያቅዳል ፈጣሪ ይፈጽማል ። '' አይደል የሚባለው ። አጋጣሚ ፈጣሪ የሰው ልጅ እቅዱን እንዲያሳካ የሚቸረው ድንቅ ስጦታ ነው ። አጋጣሚ ዝግጁ ለሆነ ሰው እንጅ ፣ ዝግጁ ላልሆነ አይሰጥም ። እቅድ ዝግጅት ነው ። ማቀድ የቻለ ሰው አጋጣሚን ለመቀበል ዝግጁ ነው ። ማቀድ ያልቻለ ደግሞ አጋጣሚን ለመቀበልም ለመጠቀምም አቅም አይኖረውም ። ሰው በአጋጣሚ ብቻ ዘላቂ ለውጥ ሊያመጣ አይችልም ። እቅድ እና አጋጣሚ ተባብረው ነው ፣ ለውጥን ዘላቂ የሚያደርጉት ። አጋጣሚን ለመፍጠር በእቅድ መኖር አስፈላጊ ነው ። በአጋጣሚ እየኖረ የከበረ የለም ። በእቅድ እየኖረ በአጋጣሚ የከበረ ግን ብዙ ነው ። እቅድ አጋጣሚን ሲቀድም ለውጥ አዎንታዊ ይሆናል ። አጋጣሚ እቅድን ሲቀድም ግን ለውጥ አሉታዊም አዎንታዊም የመሆን እድል ይኖረዋል ። ይህ የሚወሰነው እንደየሰው አስተሳሰብ እና አቀባበል ነው ። ጎበዝ ሰዎች አጋጣሚን ይፈጥራሉ ይጠቀማሉ ። ሰነፎች ግን የተፈጠረን አጋጣሚ ያባክናሉ ። አጋጣሚ እንዳይባክን በእቅድ እና በዝግጅት እንኑር ።

  ጊዜን ማባከን አጋጣሚን ማባከን ነው ። ጊዜን በግባቡ መጠቀም አጋጣሚን መፍጠርም መጠቀምም ነው ። ጊዜም አጋጣሚም የፈጣሪ ችሮታዎች ናቸው ። በሁለቱም ላይ የሰው ልጅ ስልጣን የለውም ። ሁለቱንም መጠቀም እንጅ ማዘዝ አይችልም ። ለመጠቀም መታዘዝ ፣ ለመታዘዝ ትሁት መሆን አስፈላጊ ነው ። አጋጣሚ ለትሁታን በረከት ነው ። ለእብሪተኞች ግን መቅሰፍት ነው ። '' ለሀጥዓን የመጣ ለጻድቃን ይተርፋል '' እንዲባል ፣ መቅሰፍቱ ለመልካሞች  ሊተርፍ ይችላል ። አጋጣሚ መልካም እንዲሆን ፣ ጊዜን ለመልካም ነገር እናውል ። ጊዜ አጋጣሚን ይጠብቃል ፣ አጋጣሚም ጊዜን ይጠብቃል ። በጊዜው የሚከሰት አጋጣሚ ሸክም አቅላይ ነው ። ያለጊዜው የሚከሰት አጋጣሚ ግን ሸክም አቅላይ ሳይሆን ራሱ ሸክም ነው ። ሸክም አጋጣሚ ነገር የመሸከም ውጤት ነው ። ጥላቻን በቀልን ቂምን የመሸከም ማሳያ ነው ። ስለዚህ በህይወታችን መልካም ነገር እንዲገጥመን ፣ ጥላቻን ቂምን ብቀልን አንሸከም ። ፍቅርን ይቅርታን የዋህነትን እንሽከም ። ያኔ እድል በሆነው መልካም አጋጣሚ ህይወት ሰላም እና ቀላል ትሆናለች ። 

          '' ማቀድ የሰው ድርሻ ነው ። አጋጣሚ የፈጣሪ ችሮታ ነው ። ''   

                                                                

No comments:

Post a Comment

እይታ | Perception

                                                    ስሜታዊነት እና እምነት     እምነት በስሜት አይገነባም ። እምነት ሲሞቀን የምንገነባው ፣ ሲበርደን ደግሞ የምናፈርሰው ወረት አይደለም ። ...