Thursday, April 24, 2025

እይታ | Perception

           ያለ ጊዜው ያለቀ ትእግስት

  

           በብዛት ሰዎች መከራ ሲበዛባቸው ፣ ችግር ሲደራረብባቸው ፣ ለፍተው ደክመው ጠብ የሚል ነገር ሲያጡ አሁንስ ትእግስቴ አለቀ ይላሉ ። በርግጥ እውነት ነው ፣ የሰው ልጅ ትእግስቱ ውስን ነው እናም ማለቁ አይቀርም ። ያልቃል ማለት ግን አይታደስም ማለት አይደለም ፣ ህይወት አበቃላት ማለትም አይደለም ። የሰው ልጅ ትእግስቱ ቢያልቅ ይታደሳል ። ዳግም በትእግስት ሃይል ይሞላል ። ትእግስት የማያልቅበት ፈጣሪ ፣ እንደገና በአዲስ ትእግስት ይሰራዋል ።

     ዋናው ነገር የትእግስት ማለቅ ወይም አለማለቅ አይደለም ። ትእግስት በጊዜው ሲያልቅ እና ያለ ጊዜው ሲያልቅ ይለያያል ። ያለ ጊዜው የሚያልቅ ትእግስት ጉዳቱ የከፋ ነው ። የሚታደስ ሳይሆን ፣ ባለበት የሚቆም ወይም ጭልጥ ብሎ የሚጠፋ ነው ። ለዚህም ነው ትእግስት የሌላቸው ሰዎች ብዙ ጊዜ ሲጎዱ የሚታዩት ። ያለ ጊዜው የሚያልቅ ትእግስት ፣ ሰውን ትእግስተኛ ሳይሆን እልከኛ ነው የሚያደርገው ። ስለዚህ ለጥፋት እንጅ ለልማት አይሆንም ። ለውድቀት እንጅ ለስኬት አይዳርግም ። ለሃዘን እንጅ ለደስታ አይሆንም ። ወደ በቀል እንጅ ወደ ይቅርታ ልብን አይመራም ።

      ያለ ጊዜው ያለቀ ትእግስት ጥሩ ምልክት ሳይሆን የአደጋ ምልክት ነው ። አምቡላንስ ከሳይረን ድምጹ እና ከቀይ መብራቱ ጋር እንደማለት ነው ። ከጊዜው ያጠረ ትእግስት ማስጀመር እንጅ ማስጨረስ አይችልም ። ለማሳቀድ እንጅ ለማስፈጸም በቂ አቅም የለዉም ። ተስፋ ልማስቆረጥ እንጅ ሪቫን ለማስቆረጥ እድል አይሰጥም ።

            ትእግስት ያለጊዜው ሲያልቅ ነገን ብሩህ አድርጎ ሳይሆን አጨልሞ ነው የሚያሳየው ። እምነትን ገድሎ ጥርጣሬን በልባችን ላይ ይዘራል ። አስተሳሰባችንን አዎንታዊ ሳይሆን አሉታዊ ያደርገዋል ። ይሳካል ይሆናል ከማለት ይልቅ ፣ አይሳካም አይሆንም ማለት ቃላችን እና ልማዳችን ይሆናል ። የልቦናን አይን ሞራ ገፎ ከመጣል ይልቅ ፣ የስራ ሞራልን ገፎ ይጥላል ። የሰው ልጅን በእቅድ እንዳይኖር ፣ በዘፈቀደ እንዲኖር ያስገድደዋል ። ማቀድን ሞኝነት ተስፋ ማድረግን ጅልነት አድርጎ ያሳያል ። መኖርን ከንቱ ፣ መሞትን ምርጥ መፍትሔ ያደርጋል ። ስለዚህ የትእግስት ማለቅ ሳይሆን ዋናው ቁም ነገር ፣ ያለ ጊዜው ትእግስት እንዳያልቅ መጠንቀቅ ነው የሚያስፈልገው ።

              ያለ ጊዜው የሚያልቅ ትእግስት ፣ በጊዜው ከሚያልቅ ትእግስት የሚለይባቸው ነገሮች ብዙ ናችው ። ለምሳሌ ትእግስት በጊዜው ሲያልቅ ድክም ያደርጋል ።

 ያለ ጊዜው ሲያልቅ ቱግ ያደርጋል ። በጊዜው ሲሆን ይታደሳል ፣ የወደፊት ጉዞን እንድንቀጥል ያደርገናል ። ያለ ጊዜው ሲሆን በፍጹም አይታደስም ፣ የወደፊት ጉዞን እንድንቀጥል ሳይሆን እንድናቆም ያስገድደናል ። ከመሄድ መመለስ አምራጭ የሌለው ምርጫ ይሆናል ። በጊዜው ትእግስት ሲያልቅ መጨረሻው አቅም ማጣት ነው ። ያለ ጊዜው ሲያልቅ ግን መጨረሻው ተስፋ ማጣት ነው ። አቅም ስናጣ ፈጣሪ አቅም ይሆነናል ። ተስፋ ስናጣ ግን ፈጣሪ አቅም አይሆነንም ። ምክንያቱም ተስፋ ስናጣ ፣ በእርሱ ላይ ያለንን እምነት ነውና የምናጣው ። መንፈሰ ጠንካራ ሰዎች አቅም ሊያጡ ይችላሉ ። በፍጹም ግን በፈጣሪ ላይ ያላቸውን እምነት እና ተስፋ አያጡም ። መንፈሰ ጠንካራ ያልሆኑ ሰዎች ግን ፣ አቅም አጥተው ሳይሆን አቅም እያላቸው በፈጣሪ ተስፋ ይቆርጣሉ ፣ እምነታቸውን ያጣሉ ። አዲስ አቅም አያገኙም ፣ ባይሆን የነበራቸውን አቅም ያጣሉ ። ስለዚህ ትእግስት በጊዜው ሲያልቅ መንፈሰ ጠንካራ ያደርጋል ። ያለ ጊዜው ሲያልቅ ግን መንፈሰ ደካማ ያደርጋል ።

         ያለ ጊዜው ትእግስት ሲያልቅ ውጤቱ ስሜታዊነት ነው ። ሳያስቡ ሳያሰላስሉ ሳያመዛዝኑ ፣ ዘሎ ውሳኔ ላይ መድረስ ቀላል ይሆናል ። በጊዜው ትእግስት ሲያልቅ ግን መጨረሻው ምክንያታዊነት ነው ። ከመወሰን በፊት ማሰብን ማስቀደም መርህ ይሆናል ። ማሰብን መወሰን ሲቀድም ስሜታዊነት ነው ።

 ውሳኔን ሀሳብ ሲቀድም ምክንያታዊነት ነው ። ውሳኔ ሲፈጥንም ሲዘገይም ችግር ይፈጠራል ። ሲፈጥን የስሜት ውጤት ስለሆነ ራሳችንን ያሳጣናል ። ሲዘገይ ደግሞ ፍጹምነትን ( perfectionism ) መፈለግ ስለሆነ የምንፈልገውን ያሳጣናል ። ራሳችንንም ሆነ የምንፈልገውን እንዳናጣ ፣ ትእግስታችን ያለ ጊዜው ሳይሆን በጊዜው እንዲያልቅ ጥንቃቄ እናድርግ ። ችግር በገጠመን ቁጥር ቱግ አንበል ፣ ድክም እስኪለን እንታገስ ። ያኔ ለውሳኔ ያልፈጠነ ግን ደግሞ ያልዘገየ ምርጥ ሰው እንሆናለን ።

              ትእግስት ያለ ጊዜው ሲያልቅ መማሪያ ያደርጋል ። በጊዜው ሲያልቅ ግን አርአያ ያደርጋል ። ሰው መማሪያ ሲሆን ፣ ሌላ ሰው ከእርሱ ምን ማድረግ እንደሌለበት ይማራል ። አርአያ ሲሆን ግን ፣ ሌላ ሰው ከእርሱ ምን ማድረግ እንዳለበት ይማራል ። አርአያ ሲሆን የስኬት ተምሳሌት ይሆናል ። መማሪያ ሲሆን ደግሞ የውድቀት ምሳሌ ይሆናል ። ድክም እስኪለን ከታገስን ብንወድቅም እንንሳለን ። ቱግ ካልን ግን ላንነሳ እንወድቃለን ። እስከ መጨረሻው የታገሰ ጥሩ ታሪክ ትቶ ያልፋል ። እስከ መጨረሻው ያልታገሰ ግን መጥፎ ታሪክ ጥሎ ያልፋል ። ትእግስት መጨረሻ አለው ። ለዚህም ነው ታላቁ መጽሐፍ ‘’ እስከ መጨረሻው የጸና ይድናል የሚለው ’’ ።  ቱግ ማለት የትእግስት መጨረሻው ሳይሆን ያለማለቁ ምልክት ነው ። ድካም ግን የትእግስት መጨረሻ ማሳያ ነው ። ስንናደድ ልንጠፋ ነው ። ስንደክም ግን ልንድን ነው ።

 መዳን ማለት መትረፍ መትረፍረፍ ፣ የጥሩ ነገር ምሳሌ ፣ የስኬት ተምሳሌት መሆን ነው ። መጥፋት ማለት ደግሞ የመጥፎ ነገር ፣ የውድቀት ምሳሌ መሆን ነው ። ስለዚህ ሀደራ ትእግስታችን ያለ ጊዜው እንዳያልቅብን ፣ቱግ አንበል ፣ ድክም እስኪለን እንታገስ ። መጨረሻችን መዳን እንጅ መጥፋት አይሆንም ።

          ‘’ ትእግስት የህይወት ቁልፍ መርህ ነው ። ’’                                                


No comments:

Post a Comment

እይታ | Perception

                                                                ስንፍና   ስንፍና እየቻሉ አለመስራት ነው ። የማይችሉትን አለመስራት ግን ስንፍና አይደለም ። ምክንያቱም የሰው ልጅ ሁሉ...