Wednesday, May 14, 2025

እይታ | Perception

                                                                         

                              ግጭት

     ‘’ ግጭት የህብረተሰብ አንቀሳቃሽ ሀይል ነው ‘’ ትላለች ህይወት ተፈራ ። በእርግጥ ይሄ ሀሳብ እውነትነት አለው ። ግጭት አንቀሳቃሽ ወይም አራማጅ ሀይል ነው ። ጦርነት አይደለም ግጭት ነው አንቀሳቃሽ ሀይል ። ጦርነትማ አንቀሳቃሽ ሀይል ሳይሆን አስለቃሽ ሀይል ነው ። ግጭት አስለቃሽ የሚሆነው መዳረሻው ጦርነት ሲሆን ነው ። መጨረሻው ጦርነት ካልሆነ ግን ፣ አዲስ ሀሳብ ወልዶ ፣እውቀት ጨምሮ ጥበብ አክሎ ነው የሚያልፈው ። ግጭት በሰው ልጅ ተፈጥሮ ውስጥ ያለ የሚኖር የሚቀጥል ነገር ነው ። ግጭት እንደ ውሀ ምግብ እና ልብስ ላያስፈልግ ይችላል ። ነገር ግን እኛ ባንፈልገውም ፣ ሰዎች እስከሆንን ድረስ በህይወት ስንኖር ሁል ጊዜ የሚገጥመን የህይወት ሀቅ ነው ።

    ሰው ከራሱ ፣ ከተፈጥሮ ፣ ከሰው እናም ከፈጣሪ ይጋጫል ። ሰው ከራሱ ሲጋጭ ፣ ግጭቱን መቆጣጠር ከቻለ አዲስ ሀሳብ ይወልዳል ። መቆጣጠር ካልቻለ ግን አዲስ ጭንቀት ይወልዳል ። መቆጣጠር ከቻለ ፣ ግጭቱን በጥበብ ይፈታል ። መቆጣጠር ካቃተው ግን በጥበብ ሳይሆን በጠብ ስራ ይፈታል ። ሰው ከተፈጥሮ እና ከፈጣሪ የሚጋጨው ፣ ከራሱ መታረቅ ሲያቅተው ነው ። ከሰው ጋር የሚጋጨው ግን ፣ በአብዛኛው በአንድ ሀሳብ ፣ ስራ ወይም ጉዳይ ላይ መስማማት ወይም መስማት ሲያቅተው ነው ። ከመስማማት መስማት ይቀድማል ። መስማት ከሌለ መስማማት አይኖርም ። በብዛት ሰው ከሰው የሚጋጨው ባለመስማማት ሳይሆን ባለመስማት ነው ማለት ይቻላል ። በመስማት ከባዱ ቀላል ይሆናል ።  

ባለ መስማት ግን ቀላሉ ከባድ ይሆናል ። ቀላሉ ነገር ከባድ ሲሆን ፣ ግጭት በቀላሉ ይፈጠራል ። ከባድ የመሰለው ነገር ቀለል ሲል ግን ፣ ግጭት በቀላሉ ይፈታል ።

      ግጭት ለድራማ እና ለፊልም ውበት ነው ። ለገሀዱ ዓለም ግን መፈታት ከቻለ ውበት ነው ። መፈታት ካልቻለ ግን ውበት ሳይሆን ወበቅ ነው ። ለልቦለድ የሚያሞቅ እሳት ነው ። ለገሀዱ አለም መፈታት ከቻለ ፣ በጨለማ ውስት ያለ ውብ የእሳት ብርሀን ነው ። ካልተፈታ ግን የእሳት ብርሀን ሳይሆን ትኩሳት ነው ። ግጭትን አንቀሳቃሽ ሀይል ማድረግ የሚቻለው በጥበብ ነው ። ግጭት በአብዛኛው የሚፈጠረው ፣ በነበረ ነገር ሳይሆን ፣ እንደ አዲስ በሚፈጠር ነገር ነው ። በታየ ነገር ሳይሆን ፣ ባልታየ ነገር ነው ። በተሞከረ ሳይሆን ባልተሞከረ ፣ በተለመደ ሳይሆን ባልተለመደ ነገር ነው ።

       ሰው አዲስ ነገርን በቀላሉ ለመቀበል ይቸገራል ። አዲስ ነገር ጠቃሚም ይሁን ጎጂ ፣ በቀላሉ በሰው ዘንድ ተቀባይነትን አያገኝም ። በእርግጥ ጎጂ ነገር ፣ ከጠቃሚ ነገር ይልቅ በፍጥነት የመለመድ እድል አለው ። በዚም ተባለ በዚያ አዲስ ነገር ግጭት መፍጠሩ አይቀርም ። ግጭትን በአግባቡ ማስተናገድ የቻለ ፣ ጎጂውን በመተው ጠቃሚውን አዲስ ነገር መቀበል እናም መጠቀም ይችላል ። በአግባቡ ማስተናገድ ያልቻለ ግን ፣ ጎጂውንም ጠቃሚውንም አዲስ ነገር ሳይቀበል እናም ሳይጠቀም ይቀራል ። ግጭትን መጠቀም የሚቻለው በአግባቡ ማስተናገድ ሲቻል ነው ። አልያ ግጭት ጥቅመ ቢስ አድርጎ ያስቀረናል ።

 አዲስ ነገር አዲስ ሀሳብ ፣ አዲስ ቦታ ፣ አዲስ ልብስ ፣ አዲስ ቁስ ፣አዲስ ቁርስም ሊሆን ይችላል ።

 የሰው ልጅ በዚህ የቴክኖሎጂ እና የመረጃ ዘመን ፣ ብዙ አዲስ ነገር ይገጥመዋል ። በቅርብ ቀን አዲስ ፊልም ፣ አዲስ ፕሮግራም ፣ አዲስ እንግዳ ፣ ምን አዲስ ነገር የሚሉ የሚዲያ ልፈፋዎች ፣ ሆን ተብለው የሰው ጆሮ ለማደንቆር የሚፈጠሩ ይመስላሉ ። ነገር ግን ከሁሉም አዲስ ነገር ፣ ከባዱ አዲስ ነገር ቢኖር ፣ አዲስ ሀሳብ ነው ። ሀሳብ ከግጭት ቀጥሎ ነው ተግባር የሚሆነው ። ያለ ግጭት የሚተገበር ሀሳብ ያለ አይመስለኝም ፣ ተራ ሀሳብ ካልሆነ በስተቀር ። ተራ ሀሳብ ግጭት አያስፈልገውም ። ተራ ሀሳብ ግጭት የሚፈጥረው ፣ በነገር አካባጆች መካከል ነው ። በነገር አቅላዮች ዘንድ ፣ ተራ ሀሳብ ቦታ የለውም ። የነገር አቅላይነት ( simplicity ) አንዱ ጥቅም ፣ በተራ ሀሳብ ጊዜን አለማጥፋት ነው ።

      የሰውን ልጅ ጊዜ ከሚበሉ ነገሮች መካከል አንዱ ነገርን ማካበድ ነው ። ትንሹን ነገር ትልቅ ማድረግ ፣ ቀላሉን ነገር ማወሳሰብ ። ነገርን ማካበድ በሀሳብ እና በተግባር መካከል ያለ ግድግዳ ነው ። ሀሳብ እንዳይተገበር አመድ የሚያደርግ አሲድ ነው ። በሀሳብ እና በተግባር መሀል ከባድ ግጭት የሚፈጥረው ፣ ነገርን ማካበድ ነው ። ከራሳቸውም ከሰውም በመጋጨት በብዛት የሚታወቁት ፣ ነገርን የሚያከብዱ ሰዎች ናቸው ። ግጭት ለእነዚህ ሰዎች ፣ ወደፊት አራማጅ ሳይሆን ፣ ነገርን አላማጅ ነው ። የሚማሩበት ሳይሆን የሚኮሩበት ነው ። ግጭት ለእነርሱ የበላይነትን ማሳያ እንጅ ፣ የተሻለ ነገር ማሳያ መስታወት አይደለም ። ሌሎችን አስለቃሽ ጭስ እነርሱን አስነጋሽ ዘውድ ነው ለእነርሱ ግጭት ። ስለዚህ ለግጭት ምክንያት ናቸው ተብለው ከሚጠቀሱ ነገሮች መካከል አንዱ ፣ ነገርን ማካበድ ነው ማለት ይቻላል ። ነገርን በማካበድ ከግጭት ጋር ወደፊት መሄድ አይቻልም ።

          ነገርን ማቅለል የሚችሉ ሰዎች ናቸው ፣ ግጭትን እንደመስታወት የሚጠቀሙት ። ለእነርሱ ግጭት አንቀሳቃሽ ሀይል ነው ማለት ይቻላል ። በግጭት ውስጥ ራሳቸውን ያያሉ ይማራሉ ። ለእነርሱ ሀሳብ እና ተግባር አይን እና አፍንጫ ናቸው ። በሀሳብ እና በተግባር መሀል ግጭት ቢፈጠር በቀላሉ ስለሚፈቱት ፣ ሀሳብን መኖር አይከብዳቸውም ። ነገርን ማቅለል ካለ ሀሳብ ተግባር ነው ። በተቃራኒው ነገር የሚካበድ ከሆነ ፣ ሀሳብ ተግባር ሳይሆን ሀሳር ነው የሚሆነው ። በነገር ማቅለል ውስጥ ግጭት ጠቃሚ ነው ። በነገር አካባጅነት ውስጥ ግን ግጭት ጎጂ ነው ።

      ‘’ ነገርን ማቅለል ካለ ግጭት አንቀሳቃሽ ሀይል ነው ። ‘’

No comments:

Post a Comment

እይታ | Perception

                                                                ስንፍና   ስንፍና እየቻሉ አለመስራት ነው ። የማይችሉትን አለመስራት ግን ስንፍና አይደለም ። ምክንያቱም የሰው ልጅ ሁሉ...