Wednesday, July 30, 2025

እይታ | Perception

                                             ዋናው ኮንቴክስቱ ( አውዱ )

     ሁለት መታወቂያ የተሰኘው ፊልም ላይ ፣ ዳዊት አባተ ወይም በገጸ ባህሪ ስሙ ቢኒያም እንዲህ ሲል ይደመጣል ‘’ በህይወት እውነት ወይም ውሸት ፣ ጥሩ ወይም መጥፎ ፣ ሞራላዊ ወይም ኢ ሞራላዊ የሚባል ነገር የለም ፣ ዋናው አውዱ ( ኮንቴክስቱ ) ነው ። ’’ አውድ ሲባል በዋናነት ሁኔታ ማለት ነው ። ሰው ህይወቱን በአውድ ወይም በሁኔታ የሚመራ ከሆነ ፣ እውነትን በእውነትነቱ ሳይሆን የሚመዝነው ፣ እውነት በሚያመጣው ውጤት ላይ ተመስርቶ ነው ፣ እውነትን የሚለካው ። ይህ ደግሞ የሰውን ልጅ ውጤት ተኮር እንጅ ሂደት ተኮር አያደርገውም ። ነጮቹ ሰው ከውጤቱ በላይ ሂደቱ ላይ ትኩረት እንዲያደርግ ሲመክሩ ‘’ Trust the process! ‘’ ይላሉ ። 

   ከውጤቱ በላይ ለሂደቱ ትኩረት የሚሰጡ ሰዎች በመርህ የሚመሩ ናቸው ። ከሂደቱ በላይ ለውጤቱ ዋጋ የሚሰጡ ሰዎች ግን አብዛኛውን ጊዜ መርህ አልባ ናቸው ። ያው የትም ፍጪው ዱቄቱን አምጪው ይመቻቸዋል ። አብዝተው ውጤት የሚፈልጉ ሰዎች ፣ መርዝን መድሃኒት ነው እስከማለት ይደርሳሉ ። በእውነት መንገድ ውጤት ከሚያጡ ፣ በውሸት ተጉዘው ውጤት ላይ መድረስ ምርጫቸው ነው ። ለእነርሱ እውነት ከሁኔታ በልጦ አያውቅም ። ሁኔታ ነው ከእውነት የሚበልጥባቸው ። ስለ እውነት ማጣት መራብ መጠማት መዋረድ ፣ ለእነርሱ የጀግና ሳይሆን የቀሽም ሰው ተግባር ነው ። 

    በእርግጥ አውዳዊ ፍቺ የሚያስፈልገው እውነት አለ ። ነገር ግን ሁሉም እውነት አውዳዊ ፍቺ አያስፈልገውም ። ለምሳሌ የወል እውነት አውዳዊ ፍቺ አያስፈልገውም ። የወል እውነት ቦታ ጊዜ ሁኔታ የማይቀያይሩት እውነት ነው ። ጸሀይ በምስራቅ ወጥታ በምራብ ትጠልቃለች ። ይህ የሰፈር እውነት ሳይሆን የዓለም እውነት ነው ። ውሀ ውሀ እንጅ ነዳጅ አይሆንም ። ነዳጅም እንደዚሁ ውሀ ሊሆን አይችልም ። ይህ እውነት የሆኑ ቡድኖች ያጸደቁት ሳይሆን ፣ ሁሉም ሰው አምኖ የተቀበለው እውነት ነው ። ውጤት ተኮር የሆኑ ሰዎች ግን ፣ ከቻሉ ውሀ እና ነዳጅን ቀላቅለው ፣ ነዳጅ ነው ብለው ይሸጣሉ ። ምክንያቱም ከሂደቱ በላይ የሚተማመኑት በውጤቱ ነው ። ለዚህ ደግሞ ማሳመኛ ይሆናቸው ዘንድ ፣ ውሸትን ብቻ ይዘው አይቀርቡም ። ውሸትን በእውነት ሸፍነው ያቀርባሉ ።

   ውጤት ተኮር መሆን በራሱ ስህተት አይደለም ። ስህተት የሚሆነው ለውጤቱ ሲባል የማጭበርበር ስራ ሲሰራ ነው ። ውጤቱን ጥሩ ለማድረግ ሂደቱን መጥፎ ማድረግ ትክክል አይደለም ። ከሆነ ወይም ከተቻለ ውጤቱንም ጥሩ ሂደቱንም ትክክል ማድረግ ተገቢ ነው ። ካልሆነ ግን ውጤቱ ምንም ቢሆን ፣ ሂደቱን ትክክል ማድረግ ነው የሚያስፈልገው ። አንድ አንድ ሁኔታዎች ፣ የሰው ልጆች እስከሆንን ድረስ ፣ ሂደቱን በማበላሸት ውጤቱን ማሳመር እንደሚቻል ይጠቁሙናል ። ያኔ የገጠመን እውነት የወል ሳይሆን አንጻራዊ ስለሆነ ፣ ውሳኔያችንን እንደሁኔታው ማድረግ ግድ ይላል ።

    አንጻራዊ እውነት በአማራጭ የተሞላ ነው ። እንደ ሰው ፍጹም ስላልሆንን ፣በዚህ ጊዜ ውሳኔያችን ከሂደቱ በላይ በውጤቱ ላይ ቢመሰረት መልካም ነው ። ምርጫችንም የተሻለ ይሆናል ። በስህተት መንገድ ትክክል የሆነ ውጤት ማምጣት ባይቻልም ፣ በአንጻሩ ጥሩ ነገር ማድረግ ይቻላል ። እንደዚህ አይነት ሁኔታ ሲገጥመን ፣ ውሸት ወይም እውነት ፣ ትክክል ወይም ስህተት ሚዛን አይሆኑም ። ሚዛን የሚሆኑት ማዳን ወይም መግደል ፣ ማጥፋት ወይም ማልማት ፣ ማበላሸት ወይም ማስተካከል ናቸው ። በእርግጥ የሀገሬ ሰው '' ካልደፈረሰ አይጠራም ። '' ይላል ። የደፈረሰ ሁሉ ይጠራል ማለት ግን አይደለም ። አንዳንድ ነገሮች ላይጠሩ ይደፈረሳሉ ። ላይቃኑ ይጣመማሉ ፣ ላይስተካከሉ ይበላሻሉ ፣ ላይመለሱ ይለወጣሉ ። ስለዚህ በህይወት ስንኖር ፣ ከውሳኔ በፊት ሁኔታን በጥልቀት መፈተሽ እና መመዘን ያስፈልጋል ። ምክንያቱም ማዳን የምንችለውን ልንገድል እንችላለን ። መስተካከል የሚችለው እንደተበላሸ ሊቀር ይችላል ። መቆም ያለበት ወድቆ እንክትክቱ ሊወጣ ይችላል ። ሰዎች ነን ፍጹም ልንሆን አንችልም ። ስለዚህ ሁኔታን በአንጻራዊ እውነት ከምንመዝን ፣ አንጻራዊ እውነትን በሁኔታ ( context) ብንመዝን የተሻለ ነው ።

   እውነት ከእውነት ይለያያል ። ሁሉም እውነት እኩል መታየት የለበትም ። የሚጠቅም እውነት ከሚጎዳ እውነት ጋር እኩል መታየት አይኖርበትም ። የሚያጣላ እውነት ከሚያፋቅር እውነት ጋር ሊስተካከል አይገባውም ። ጥቁር ታሪክ የተሸከመ እውነት ፣ የጀግንነት ታሪክ ከተሸከመ ታሪክ ጋር እኩል ትኩረት ሊሰጠው አይገባም ። ምክንያቱም ጥቁር ታሪክ ጸጸትን በቀልን ቁጭትን ነው የሚወልደው ። የጀግንነት ታሪክ ግን ሞራልን አሸናፊነትን አንድነትን ነው የሚወልደው ። ስለዚህ ለሁሉም እውነት መታመን ታማኝ አያደርግም ። ትክክለኛ ታማኝነት ፍቅርን ፍትህን አንድነትን ለሚያሰፍን እውነት መታመን ነው ። ለሁሉም እውነት መታመን ጅልነት ነው ። ለምርጥ እውነት መታመን ግን ጀግንነት ነው ። በነገራችን ላይ ሰውን ለመጉዳት እውነተኛ የሚሆኑ ሰዎች አሉ ፣ እነዚህ ሰዎች ክፉዎች ናቸው ። ምክንያቱም የእነርሱ እውነት ፍቅር የለውም ። ፍቅር የሌለው እውነት ደግሞ የሞተ ነው ። ሰውን ለመጉዳት እውነተኛ ከመሆን ፣ ሰውን ለማዳን ውሸታም መሆን ይሻላል ። ነገርን ከሰው አንጻር እንጅ ፣ ሰውን ከነገር አንጻር መመልከት ልክ አይደለም ። የሚጎዳን እውነት ይዞ መኖር ፣ ሰውን ከነገር አንጻር መመልከት ነው ። 

   ዋናው አውዱ ( ኮንተክስቱ ) ማለት በምንም ጉዳይ ቢሆን ሰውን እናስቀድም ማለት ነው ። እውነትም አንጻራዊ እውነት ሰብአዊነትን ማስቀደም አለባቸው ። በእርግጥ የወል እውነት ፣ በምንም አይነት ሁኔታ ውስጥ ሰብአዊነትን ቢያስከብር እንጅ አያዋርድም ። አንጻራዊ እውነት ግን አስቸጋሪ ነው ። ፍትህን ለማዛባት ሰብአዊነትን ለመጣስ ሊውል ይችላል ። ስለዚህ አንጻራዊ እውነት ሲገጥመን መጠንቀቅ አለብን ። 

  '' ከሁኔታ የሚበልጠው እውነት የሰውን ልጅ ክብር የሚጨምር ነው ። በሁኔታ የሚገደብ እውነት ግን የሰውን ክብር ሊጨምርም ሊቀንስም ይችላል ። ''    

    

Tuesday, July 15, 2025

እይታ | Perception

                                                             ራስን መመርመር

  ራስን መመርመር ራስን መመልከት ነው ። አንድ የላቦራቶሪ ቴክኒሺያን በሰው ደም ውስጥ ፣ በሽታ አምጪ ህዋስ መኖሩን ለማረጋገጥ ፣ ማይክሮስኮፕን ይጠቀማል ። በተመሳሳይ የሰው ልጅ የስብእና በሽታ ሲገጥመው ፣ ራሱን ለመመርመር የስብእና ግድፈቱን የሚለይበት ማይክሮስኮፕ ያስፈልገዋል ። በሽታውን ለማወቅ ማይክሮስኮፑን በአግባቡ መጠቀም ግድ ይላል ። የሰው ልጅ የራሱን የስብእና በሽታ የሚያይበት ማይክሮስኮፕ አንዱ ጥሞና ነው ። ጥሞና የባህሪ በሽታን የመለየት ከፍተኛ አቅም አለው ። ጥሞና ሰውን ከፍተኛ መረጋጋት ውስጥ ይከታል ። ሰውን እንደ ፍሪጅ አቀዝቅዞ ፣ ባህሪን ከሚበክል ስሜት እና ሀሳብ ነጻ ያደርጋል ። ሰው በሽታውን አውቆ መድሀኒቱን እንዲፈልግ ፣ ጥሞና ብርሃን ይሆነዋል ። ጥሞና ዝምታ ነው ። ፈርቶ ዝም ማለት ሳይሆን አቅዶ ዝም ማለት ነው ።

  ፈርቶ ዝም ማለት ሁለት ገጽ አለው ። አንድም ለኪሳራ በሌላ በኩል ደግሞ ለትርፍ ሊዳርግ ይችላል ። የፍርሀት ዝምታ ከስሜታዊ ሰው ጥቃት ይጠብቀናል ። በስሜታዊ ሰው ፊት በፍርሀትም ይሁን በእውቀት ዝም ማለት ራስን ከአደጋ መከላከል ነው ። የፍርሀት ዝምታ ከዚህ አንጻር ሲታይ ጠቃሚ ነው ። ግን በሌላ ገጹ ሲታይ የፍርሀት ዝምታ ብዙ ነገር ያሳጣል ። ዝምታ ወርቅ ነው የሚባለውን ያህል ውድቅ የሚሆንበት ቦታም አለ ። መናገር ሲኖርብን ዝም ማለት ያሳጣል ። በእርግጥ ዝም ማለት ሲገባ መናገርም ያስቀጣል ። ሁለቱም እኩል ጉዳት አላቸው ። ከሁለቱም ጉዳት ነጻ የሚያወጣን ማስተዋል ነው ። ለዚህ ደግሞ መፍትሄው ጥሞና ነው ። 

 ጥሞና የነገርን ክብደት እና ቅለት ለመለየት ወሳኝ ነው ። ጥሞና የማስተዋል አቅምን ሲጨምር ፣ የፍርሀት ዝምታ ግን ማስተዋልን ይቀንሳል ። በጥሞና ውስጥ ነገርን በልኩ ማወቅ እና መረዳት ይቻላል ። ጤናማውን ከበሽተኛው ለመለየት ቀላል ይሆናል ። ይህ ደግሞ ራስን ለማስተካከል እድል ይሰጣል ። ጥሞና ራስን መመርመሪያ ምርጥ ማይክሮስኮፕ ነው ።

   ሌላኛው ራስን መመርመሪያ ማይክሮስኮፕ ተግባቦት ነው ። ከሰው ጋር መነጋገር ራስን ማያ መስተዋት ነው ። ሰው ፊቱ ላይ ያለውን ጉድፍ ለማጽዳት መስተዋት ይጠቀማል ። የባህሪ ግድፈቱን ለማጽዳት ደግሞ አጠገቡ ያለውን የቅርቤ የሚለውን ሰው ፣ እንደመስተዋት መጠቀም አለበት ። ሰው በምልአት ራሱን ማየት አይችልም ። ለእርሱ የተሰወረው አጠገቡ ላለ ሰው ግልጽ ሊሆን ይችላል ። በተለይ በሳል ሰው ካለ ፣ የማይታየውን ማየት የሚችል አቅም ስላለው ፣ ራስን ለመመርመር እና ለማስተካከል ጥሩ አቅም ይሆነናል ። ሰው ለብቻው ራሱን በመመርመር ውጤታማ አይሆንም ። የሚያግዘው እና የሚረዳው ሰው ያስፈልገዋል ።

   ሰው ራሱን ሲመረምር ሀቀኛ መሆን አለበት ። ስህተቱን ስህተት ፣ ልኩን ትክክል ነው ማለት አለበት ። ስህተቱን ልክ ልኩን ስህተት ካደረገ ግን ፣ ራሱን እየመረመረ ሳይሆን ራሱን እያባበለ ነው ። ራስን በማባበል ደግሞ አሉታዊ እንጅ አዎንታዊ ለውጥ ማምጣት አይቻልም ። እየባሱ መሄድ እንጅ መሻሻል አይኖርም ። ሰው ወደ ላይ የሚያድገው እውነትን መቀበል ሲችል ነው ። ወደ ታች የሚወርደው እውነትን መቀበል ሲያቅተው ነው ። ለስህተት ምክንያት እየሰጡ ራስን ከእውነት ማሸሽ ፣ መጨረሻው እድገት ሳይሆን ውርደት ነው ።

 ስለዚህ ራስን መርምሮ ለማሻሻል ፣ እውነትን መቀበል ቁልፍ ብቻ አይደለም ፣ የቁልፎች ሁሉ ቁልፍ ( Master key ) ነው ።

   ትክክለኛ ራሱን መርማሪ ፣ ተንኮል በመስራቱ ራሱን ደግ አደረክ ብሎ አያሞግስም ። ባይሆን በመጸጸት ራሱን ለማስተካከል ይጥራል ። ባደረገው መልካም ነገር ይደሰታል ራሱንም ይሸልማል ። በሰራው ስህተት ደግሞ ራሱን ይወቅሳል ። በልኩ ያዝናል በልኩ ደግሞ ይደሰታል ። ደስታው የበለጠ ተግቶ እንዲሰራ ሀይል ይሆነዋል ። ሀዘኑ ደግሞ ስህተቱን ይቀንስለታል ። በስህተት ማዘን በመልካም ስራ መደሰት ሰውነት ነው ። በተንኮል መደሰት በመልካም ስራ መከፋት አውሬነት ነው ። አንዳንድ ሰዎች ማታ ላይ ተኝተው ፣ የቀን ስራቸውን የሚያሰላስሉት ፣ በሰሩት ተንኮል ለመሳቅ እና ባደረጉት መልካም ነገር ለማዘን ነው ። ከዚያም በተጨማሪ የተሻለ ተንኮል ለማሰብ እና ለማቀድ ነው ።

     ተንኮል ለማቀድ ራሱን ከሚመረምር ሰው ፣ ራሱን የማይመረምር ብኩን ይሻላል ። ምክንያቱም ስህተትን ሆን ብሎ ሳይሆን ፣ ባለማወቅ ነው የሚሰራው ። አስቦ ራሱን መመርመር ባይችልም ፣ በሂደት በህይወት ልምድ ስህተቱን መቀነሱ አይቀርም ። ይህች ምድር ትልቅ ጥፋትን የምታስተናግደው ፣ ሳያውቁ ስህተት በሚሰሩት ሳይሆን አውቀው ሆን ብለው ስህተት በሚሰሩት ነው ። ክፉ ለማድረግ ራስን መመርመር ፣ ራስን መመርመር ሳይሆን ራስን መራር ማድረግ ነው ። ( Weak acid ) ደካማ አሲድን ጠንካራ አሲድ ( Strong acid ) ማድረግ ነው ። ይህ ደግሞ ከጎጂነት ወደ አጥፊነት መቀየር ነው ። ሰው ራሱን የሚመረምረው አጥፊ ከሆነ አልሚ ለመሆን ነው ። ተንኮለኞች ግን ራሳቸውን የሚመረምሩት የበለጠ አጥፊ ለመሆን ነው ።

   ራሳችንን መመርመር  ለክፋት ሳይሆን መልካም ለማድረግ መሆን አለበት ። ስህተትን ለመቀነስ እንጅ ስህተትን ወደ ተንኮል ለመቀየር መሆን የለበትም ። ራስን ለማረም እንጅ አረም ለማድረግ ራስን መፈተሽ አያስፈልግም ። ስራን ለማስተካከል እንጅ ለማበላሸት ራስን መመርመር አስፈላጊ አይደለም ። በዚህች ምድር ስንኖር ራስን መመርመር እጅግ በጣም አስፈላጊ ነው ። ነገር ግን ራሳችንን መመርመር ያለብን ምድርን ለማልማት እንጅ ለማጥፋት አይሁን ።

    ‘’ ራስን ለማስተካከል ራስን መመርመር ነው ቁልፉ ። ‘’                 

Saturday, July 5, 2025

እይታ | Perception

                                                       

                       መቅናት እና ማስቀናት

      ‘’ የቀናም ያስቀናም ሁሉም ቤት ያፈርሳል ። ‘’ አለ ዘፋኙ ። ምክንያቱም መቅናትም ማስቀናትም የትዳር ማነቆዎች ናቸው ። ትዳርን የማፍረስ አቅም አላቸው ። መቅናት እኔ ብቻ ልወደድ ባይነት ስለሆነ ፣ በፍቅር ውስጥ መጋራትን እንጅ ማጋራትን አይፈቅድም ። ቅናት ከመስጠት ይልቅ መቀበል ላይ ትኩረት ያደርጋል ። ዞሮ ዞሮ ቅናት የፍቅር ተቃራኒ ነው ። ምክንያቱም ፍቅር ከመቀበል ይልቅ ለመስጠት ከፍ ያለ ቦታ መስጠት ነው ። መስጠት ባነሰበት ሁሉ ፍቅር ያንሳል ። በመቀበል ብቻ ደግሞ ፍቅርን ማጎልበት አይቻልም ። መስጠትም መሰጠትም ባለበት ግን ፍቅር ያድጋል ይበዛል ። ያኔ መቅናትም ማስቀናትም አቅም ያጣሉ ። ለመስጠት ዝግጁ የሆነ ልብ ለቅናት ቦታ የለውም ።

   ቀናተኛ ሰው ለሰው ሲሰጥ ከእርሱ ላይ የተወሰደበት ይመስለዋል ። ካገኘው ይልቅ ያጣው ይታየዋል ። ከተሰጠው ይልቅ የተነፈገው ይጎላበታል ። ከፍቅር ይልቅ ለጥላቻ ምክንያት ይፈልጋል ። ቅናት ልብን ስለሚሰውር ፣ በቀናተኛ ሰው ዘንድ ከእርሱ ውጪ ሌላ ሰው ልክ ሆኖ አያውቅም ። ለእርሱ ልኩ ስህተት ፣ ስህተቱ ደግሞ ልክ ይሆናል ። ይህ ብቻ አይደለም ስህተትን ማጉላት ፣ ልክ የሆነውን ስራ ማኮሰስ ይችላል ። ለራስ መኖር እንጅ ለሌላው መኖር በቀናተኛ ሰው ዘንድ አይታሰብም ። ለሰዎች ሲኖር የማይደሰት ፣ ሰዎች ሲኖሩለት ብቻ የሚደሰት ራስ ወዳድ ፍጥረት ነው ። መኖር ሳይሆን ምን ጊዜም ማኖር ነው የሚፈልገው ። ከራሱ ውጪ ማየት የማይችል እውር ነው ። ቀናተኛ ሰው የራስ መንገድ እንጅ የጋራ መንገድ አይመቸውም ።

የራስ መንገድ አስፈላጊ ቢሆንም ፣ ለጋራ መንገድ ግን ክፍት መሆን አለበት ። የጋራ መንገድን ማስተናገድ የማይችል የራስ መንገድ ግትር ነው የሚያደርገው ። ይህ ደግሞ ከስምምነት ይልቅ ለግጭት ይዳርጋል ። በቀላሉ የሚፈታ ሳይሆን የማይፈታ ግጭት ነው የሚፈጥረው ።

   መቅናት መቃጠልም ማቃጠልም ነው ። መጀመሪያ በሰው ድርጊት መቃጠል ነው ። ሲቀጥል ነገር ማቀጣጠል ነው ። ሲለጥቅ በራስ ድርጊት ሌላውን ማቃጠል ነው ። በቅናት ቤቱን ያፈረሰ እንጅ የገነባ የለም ። ግንኙነቱን የተወ እንጅ በግንኙነቱ ፍሬ ያፈራ የለም ። ያፈረ እንጅ የኮራ ሊኖር አይችልም ። በጥርጣሬ እየተወጉ ሰላምን ማፍረስ እንጅ መገንባት በቅናት ፈጽሞ አይቻልም ። ‘’ ተጠራጥሮ ትዳር ኑሮ መች ያሞቃል ፣ የቀናም ያስቀናም ሁሉም ቤት ያፈርሳል ። ‘’ እንዲል ዘፋኙ ። ቅናት እና ጥርጣሬ የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታ ናቸው ። ቅናት ባለበት ጥርጣሬ ሊኖር ግድ ነው ። ጥርጣሬ ባለበት ቅናት ሊጠፋ አይችልም ። ሁለቱ ተባብረው ነው ሰውን አንድደው አመድ የሚያደርጉት ። ቅናት እና ጥርጣሬ!

   መቅናት ብቻ አይደለም ማስቀናትም በሽታ ነው ። ለማቃናት ሳይሆን ለማስቀናት የሚለፉ ሰዎች አሉ ። ማስቀናት የሚወዱ ሰዎች ፣ በማስደሰት ሳይሆን በማናደድ የሚያምኑ ናቸው ። በሰው ንዴት የሚደሰቱ ሲበዛ ራስ ወዳድ ናቸው ። ዉድ መሆናቸውን ለማሳየት ፣ ርካሽ መንገድ የሚጠቀሙ ብኩኖች ናቸው ። በማስቀናት ፍቅርን ለማጎልበት የሚጥሩ ጅሎች ናቸው ። ፍቅር በቅናት ይላላል እንጅ አይጠነክርም ። ቅናት በፍቅር ውስጥ የእርጎ ዝንብ ነው ። ልብን የሚበክል ባክቴሪያ ነው ።

ቅናትን በማስቀናት ጎትቶ ማምጣት ፣ ንጹህ ልብን መበከል ነው ። የተበከለ ልብ ደግሞ ከፍቅር ይልቅ ለጥላቻ ምቹ ነው ። የቅናትም የማስቀናትም መጨረሻ ጥላቻ ነው ። ሁለቱም የልብ በካይ ጋስ ( Carbon di oxide ) ናቸው ። ስለዚህ ለማቃናት እንጅ ለማስቀናት አንኑር ።

   በአርአያ ( Role model ) መቅናት ክፋት የለውም ። ይህ ቅናት በጎ ነው ። በሰው ልብ ውስጥ ክፋትን ሳይሆን ፣ ለስራ መነሳሳትን ( Motivation ) ነው የሚፈጥረው ። መጥፎው ቅናት ግን ለስራ ሳይሆን ለነገር ነው ሚያነሳሳው ። እኔ እንደሱ በሆንኩ ማለት እና እኔ ተከብሬ እርሱ በተዋረደ ማለት ይለያያል ። በጎ ቅናት ራስን ለማክበር መመኘት ነው ። መጥፎ ቅናት ደግሞ ሌላውን ለማዋረድ መጣር ነው ። በጎ ቅናት ከሰው እኩል ለመሆን መጣር ነው ። መጥፎ ቅናት ግን ከሰው ሁሉ በልጦ ለመገኘት መታገል ነው ። በሰው ጉብዝና በበጎ የቀና ሰው ፣ እንደሰውየው ጎበዝ ይሆናል ። በክፋት የቀና ሰው ግን ጎበዝ ሳይሆን ግብዝ ነው የሚሆነው ። በነገራችን ላይ በቅናት የሰውን ነገር የራስ ማድረግ አይቻልም ። ነገር ግን በበጎ ቅናት ካደረብን ፣ ቅናቱ በፈጠረው መነሳሳት ፣ ትጉ በመሆን የሰውን ሳይሆን ፣ የራስን ህልም ልክ እንደሌላው እውን ማድረግ ይቻላል ። በክፋት ግን የሰውን ነገር የራስ ለማድረግ ከጣርን ያለንን እናጣለን ።

 እንደ አልበርት አንስታይን የፊዚክስ ሊቅ ብሆን ብሎ መቅናት ችግር የለውም ። እንደ አልበርት አንስታይን ለምን እኔም እኩል ችሎታ አልተሰጠኝም ብሎ መቅናት ግን ትርፉ በሽታ ነው ። ምክንያቱም ህይወት አንተ ራስህን በትጋት ስታገኝ እንጅ የምታከብርህ ፣ በቅናት ስትንጨረጨር ዞር ብላ አታይህም ።

የስኬት ምስጥሩ ሰውን ማየት ሳይሆን ፣ በሰው ውስጥ ራስን ማየት ነው ። እዚች ምድር ላይ ሰውን በማየት ብቻ የከበረ የለም ። በጎ ቅናት በሰው ውስጥ ራስን ማየት ነው ። መጥፎ ቅናት ግን ከሰው ጋር ራስን ማነጻጸር ነው ። ከሰው መማር እንጅ በሰው መማረር አያዋጣም ። መማር ወይ ከሰው እኩል አልያም ከፍ ያደርገናል ። መማረር ግን በምንም ሂሳብ ከሰው እኩል አይደርገንም ። በጎ ቅናት መማር ነው ። መጥፎ ቅናት መማረር ነው ። ስለዚህ በበጎ እንቅና ፣ በክፋት ከመቅናት ግን እንጠንቀቅ ።

   ‘’ መቅናትም ማስቀናትም በሽታ ነው ፣ በበጎ መቅናት ግን መልካም እይታ ነው ። ‘’

Saturday, June 28, 2025

እይታ | Perception

                                                              ስንፍና

  ስንፍና እየቻሉ አለመስራት ነው ። የማይችሉትን አለመስራት ግን ስንፍና አይደለም ። ምክንያቱም የሰው ልጅ ሁሉን መስራት አይችልም ። ሁሉን ቻይ ፈጣሪ ብቻ ነው ። ደካማ ጎን የሌለው ፣ ጠንካራ ጎኑ ብቻ የሚነገርለት አካል ፈጣሪ ብቻ ነው ። የሰው ልጅ ግን ደካማ እና ጠንካራ ጎን አለው ። አንዱ ጠንካራ በሆነበት ሌላው ደካማ ሊሆን ይችላል ። ሌላው ጠንካራ በሆነበት አንደኛው ደግሞ ደካማ ነው ። በቃ ይህ የህይወት እውነታ ነው ። በአንድ ነገር ደካማ መሆን ግን ስንፍና አይደለም ። ስንፍና መስራት አለመቻል ብቻ ሳይሆን ፣ ምንም መስራት አለመቻል ነው ። መስራት እየቻሉ መለገም ፣ ማንበብ እየቻሉ ማሳበብ ፣ መድረስ እየቻሉ መቅረት ፣ መራመድ እየቻሉ መቆም ፣ መቆም እየቻሉ መቀመጥ ፣ መቀመጥ እየቻሉ መቆመጥ ነው ስንፍና ።

 ድክመት የተፈጥሮ ውጤት ነው ። ስንፍና ግን የምርጫ ውጤት ነው ። ሰው መርጦ ደካማ መሆን አይችልም ። መርጦ ግን ሰነፍ መሆን ይችላል ። ድክመትን ማሻሻል ይቻላል ፣ ማስወገድ ግን በፍጹም አይቻልም ። ስንፍናን ማስወገድ ግን ይቻላል ። ድክመትን ለማሻሻል ፈጣሪን መማጸን ግድ ነው ። ስንፍናን ለማስወገድ ግን ራስን ማሳመን በቂ ነው ። ድክመትን መቀበል እንጅ መቃወም አይቻልም ። ስንፍናን መቀበልም መቃወምም ይቻላል ። ጠንካራ ሰው ስንፍናን መቃወም የሚችል ነው ። በዚያው ልክ ድክመቱን አምኖ መቀበል የሚችል ነው ። ዳተኛ ሰው ግን ስንፍናን መቃወም አይችልም ። ድክመቱንም አምኖ መቀበል አይችልም ። ለሚያደርገው የስንፍና ድርጊት ሰበብ መፍጠር ነው የሚችለው ።

ለችግሩ መፍትሄ የማያጣ ሳይሆን ፣ ለስንፍናው ምክንያት የማያጣ ፍጥረት ነው ። ሰነፍ ማለት ደክሞ ሳይሆን አውቆ የተኛ ነው ። ’’ አውቆ የተኛን ቢቀሰቅሱት አይነቃም ። ‘’ ይል የለ ያገሬ ሰው ፣ ሰነፍ እንደዛ ነው ። እየቻለ የማያደርግ እያወቀ ዝም የሚል ነው ።

  ንግግር አለመቻል ስንፍና አይደለም ድክመት ነው ። መናገር እየቻሉ ዝም ማለት ነው ስንፍና ። በተፈጥሮ ንግግር ላይ ደካማ የሆነ ሰው ፣ በጥረት የንግግር ችሎታውን ማሻሻል ቢችልም ፣ በፍጹም አንደበተ ርቱዕ ሊሆን አይችልም ። አንደበተ ርቱዕ ካልሆንኩ ብሎ ከሚታገል ፣ ድክመቱን አምኖ ቢቀበል ይሻለዋል ። ‘’  Change the changeable, accept the unchangeable. ‘’ እንዳለው የህይወት ክህሎት አሰልጣኙ ፣ የሚለወጠውን መለወጥ ፣ የማይለወጠውን መቀበል የተሻለ ነው ። የሚችሉት ላይ አድምቶ መስራት ፣ የማይችሉትን ለሚችሉት አሳልፎ መስጠት ብልሀት ነው ። ሁሉን ካልቻልኩ ማለት ፣ ምንም አለመቻልን ነው የሚፈጥረው ። ምንም አለመሞከር ደግሞ ስንፍናን ነው የሚፈጥረው ። መሞከር ሁሉን ወደ መቻል ሳይሆን ወደ መቻል ነው የሚወስደን ። አለመሞከር ግን ወደ ምንም አልመቻል ነው የሚወስደን ። ስንሞክር የምንችለውን እናውቃለን ፣ የማንችለውን እንለያለን ። ያኔ ድክመትን ከስንፍና እናጠራለን ።

በሁሉም ነገር ላይ ጎበዝ መሆን አይቻልም ። በምንም ነገር ላይ ጎበዝ አለመሆን ግን እርሱ ስንፍና ነው ። ሰው ያለችሎታ አይፈጠርም ። ችሎታውን ማወቅ ግደታው ነው ። ምንም ችሎታ የሌለው ሰነፍ ነው ። ሁሉም ሰው የሚችለውን አለመቻልም ስንፍና ነው ።የሰው ልጅ ሁሉ መማር ማንበብ መጻፍ እንዲችል ተደርጎ ነው የተፈጠረው ። እኔ ትምህርት ንባብ ፅሁፍ አይሆነኝም ማለት ትልቅ ስንፍና ነው ። እኔ ስእል አይሆነኝም ማለት ይቻላል ። ምክንያቱም ስእል ልዩ ተሰጥኦ ይፈልጋል ። ለአንድነት የሚሰጥ ሳይሆን ለልዩነት የሚቸር ነው ። በደፈናው እኔ ትምህርት አይሆነኝም ማለት ግን ስንፍና ነው ።

   ችሎታ በሁለት ይከፈላል ። ለልዩነት የሚሰጥ እና ለአንድነት የሚሰጥ ችሎታ ነው ። ሁሉም ሰው የሚችለው ነገር የአንድነት ችሎታ ነው ። የተወሰኑ ሰዎች ሊያደርጉት የሚችሉት ነገር ግን ለልዩነት የተሰጠ ነው ። መናገር መቻል ለሁሉ የተሰጠ ነው ። አሳምሮ መናገር ግን በልዩነት የሚሰጥ ነው ። ቀላል ሂሳብን መስራት ሁሉም ሰው ይችለዋል ። ከባድ እና ውስብስብ ሂሳብን መስራት ግን ልዩ የተፈጥሮ ዝንባሌን ይጠይቃል ። መኪናን መንዳት ለሁሉም ሰው ይቻላል ። መኪናን መስራት ግን ሁሉም ሰው አይችለውም ። ስለዚህ የአንድነት ችሎታን ማጣት ስንፍና ነው ። የልዩነት ችሎታን ማጣት ግን ድክመት ነው ወይም ያለቦታ የመገኘት ውጤት ነው ። 

   ‘’ ለሚያምን ሁሉ ይቻለዋል ። ‘’ ይላል ታላቁ መጽሀፍ ። ለጣረ ሁሉ ይቻለዋል ግን አላለም ። ምክንያቱም ከጥረት እምነት ይበልጣል ። ሰው ሁሉን ማድረግ ባይችልም ፣ ሁሉን ማድረግ በሚችለው ፈጣሪ ፣ በእምነቱ ምንም ማድረግ ይችላል ። ይህ የሚሆነው ስለጣረ ስለለፋ ሳይሆን ስላመነ ነው ። እዚህ ጋር ከሰው ችሎታው በላይ እምነቱ በጣም ወሳኝ ነው ። ለዚህም ነው የእምነት ሰዎች ፣ የጥረት ሰዎች ብዙ የሚደክሙበትን ፣ በቀላሉ የሚያከናውኑት ።

 የሰው ልጅ ደካማ ጎኑ የሚሸፈነው በእምነት ነው ። ስንፍናው ግን በምንም አይሸፈንም ። ባይሆን በቅጣት ይወራረዳል ።

   አንዳንድ ነገሮችን ማድረግ አለመቻል ፣ ስንፍና ስላልሆነ ብዙ መጨነቅ ተገቢ አይደለም ። ሰው መጨነቅ ያለበት ማድረግ እየቻለ ባለማድረጉ ነው ። ምንም አለመጨነቅ ልክ አይደለም ለስንፍና ይዳርጋል ። በሁሉም ነገር መጨነቅም ልክ አይደለም ፣ ለአእምሮ ህመም ይዳርጋል ። ሰው የሚችለውን ለማድረግ በመጠኑ መጨነቅ አለበት ። የማይችለውን ለማድረግ ግን ማመን እንጅ መጨነቅ የለበትም ። የሚችለውን ለመስራት በመጨነቁ ስንፍናውን ያስወግዳል ። የማይችለውን ለማድረግ ማመኑ ፣ ድክመቱን አምኖ ለመቀበል ይረዳዋል ።

  ‘’ ስንፍና ልዩነትን መፍጠር አለመቻል ነው ። ድክመት ልዩነትን አምኖ መቀበል ነው ። ‘’                            

Monday, June 16, 2025

እይታ | Perception

                                                     

                              ራስን ማጣት

     

       ራስን ማጣት መልከ ብዙ ነው ። ሰው ራሱን የሚያጣበት ምክንያት ብዙ ነው ። ራስን ከሚያሳጡ ነገሮች መሀል አንዱ ስሜታዊነት ነው ። ስሜታዊነት ሰውን ሌላ ሰው የማድረግ አቅም አለው ። ሰው ሲቆጣ ሲያዝን ሲፈራ እና ሲደሰት ፣ ከነበረው ማንነቱ የተለየ ማንነትን ይላበሳል ። ለዚህ ነው ስሜታዊ የሆኑ ሰዎች ፣ ባህሪያቸው በቀላሉ የማይለይ ፣ ስብእናቸው ተለዋዋጭ እየሆነ የሚያስቸግረው ። ስሜታዊ ሰዎች ሲደሰቱ ሌላ ፣ ሲያዝኑ ሌላ ሰው ናቸው ። በቀላሉ ራሳቸውን ያጣሉ ። ሲጀመር ዋስትና ያለው ባህሪ ወይም ስብእና ስለማይኖራቸው ፣ እንደ እስስት በቀላሉ የመለዋወጥ ባህሪ ይኖራቸዋል ። ለእነርሱ ከባዱ ራስን ማጣት ሳይሆን ራስን ማግኘት ነው ። በስሜት ለመገንባት ብርቱ ናቸው ። የዚያኑ ያህል በንዴት ለማፍረስ ጎበዝ ናቸው ። ሆ ብሎ መስራት ወዲያው ደግሞ ሆ ብሎ ማበላሸት መለያ ባህሪያቸው ነው ። ባጭሩ በስሜታዊነት ራስን ማጣት እንጅ ራስን ማግኘት ፣ ወደ ራስ መመለስ አይኖርም ።

ሌላኛው ራስን የሚያሳጣ ነገር ዝለት ነው ። ዝለት ሲባል የመንፈስም የአካልም ነው ። በእርግጥ የአካል ዝለት ፣ ያን ያህል የባህሪ ወይም የስብእና መዛባትን አይፈጥርም ። የመንፈስ ዝለት ግን ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ፣ የባህሪ መረበሽን ፣ የስሜት መቃወስን ፣ የስብእና መዛባትን ያስከትላል ። ዝለት ቀላሉን ነገር ከባድ ያደርጋል ። ተግባቢ የነበረውን ነጭናጫ ያደርገዋል ። ትእግስተኛ የነበረውን ቁጡ ያደርገዋል ። ትሁት የነበረውን ትእቢተኛ ያደርገዋል ። ብርቱ የነበረውን ደካማ ያደርገዋል ።

 በዝለት ውስጥ ስራ በጥረት እንጅ በጥራት አይሰራም ።በዝለት ውስጥ ለመጣር የተወሰነ አቅም ይኖራል ፣ ለማጣራት ግን በቂ አይሆንም ። ምክንያቱም ዝለት አቅላችንን ያስተናል ፣ ራሳችንንም ያሳጣናል ። ዝለት የስራ መብዛት ውጤት ነው ። ከአቅም በታች መስራት ዘልዛላ ያደርጋል ። ከአቅም በላይ መስራት ደግሞ ለዝለት ይዳርጋል ። ስለዚህ ሰው ራሱን ላለማጣት አቅሙን ማወቅ አለበት ። በአቅሙ ልክ መስራት አለበት ።  

   ራሳቸውን የሚያጡ ሰዎች ብዙ ጊዜ ራሳቸውን የማያውቁ ሰዎች ናቸው ። ራስን ማወቅ የራስን አቅም ስሜት ድክመት ጥንካሬ እና ሀሳብ ወይም አላማ ማወቅ ነው ። እነዚህን የራሱ የሆኑትን ነገር ያላወቀ ሰው ፣ በስራ ቦታ ፣ በማህበራዊ ግንኙነት ውስጥ በቀላሉ ራሱን ያጣል ። ምክንያቱም ችግር ሲገጥመው የሚታገስለት አላማ የለውም ። ድክመቱን አውቆ ነገርን  በማሸሽ ወይም በመሸሽ ፣ ከራሱ አያርቅም ። ራሱን ለማሸነፍም ጠንካራ ጎኑ ምን እንደሆነ መለየት አይችልም ። በመጨረሻም ራሱን በማጣት ብዙ ነገሩን ያጣል ። በእርግጥ ራስን ከማጣት በላይ ከባድ ችግር የለም ። ሰው ያለውን ሁሉ ቢያጣ ችግር የለውም ። ከባድ ችግር የሚፈጠረው ግን ራሱን ያጣ እለት ነው ።       

   ራስን ማጣት የነበረንን መጥፎ ነገር ማጣት ሳይሆን ፣ ያለንን ጥሩ ነገር ማጣት ነው ። ሰው ያለውን መጥፎ ነገር ቢያጣማ መልካም ነው ። ያኔ ራሱን አጣ ሳይሆን ፣ ራሱን አገኘ ነው የሚባለው ። የነበረውን ቁጣ ትቶ ፣ ያልነበረውን ትእግስት ቢላበስ እሰየው ነው ። ትእቢቱን ረስቶ ትህትናን ከያዘ ፣ ይህ መልካም ነው ። ስስትን ትቶ ደግ መሆን ከጀመረ ፣ ያኔ ወደ ጥንተ ተፈጥሮው ፣ ወደ ሰውነቱ ተመለሰ ማለት ነው ። ራስን ማጣት መልካም ነገርን ማጣት ነው ። ትእግስትን ትህትናን እምነትን እውነትን ደግነትን ማጣት ነው ። ሰው እንደ ድሮ  አይደለህም ተለውጠሃል ፣ ወደራስህ ተመለስ የሚባለው ፣ የነበረውን መልካም ነገር ሲያጣ ነው ።

   አንዳንድ ሰው ገንዘብ ሲያገኝ ትህትናውን ያጣል ። በነገራችን ላይ ማግኘት የሚያስከትለው ማጣት በሽታ ነው ። ሰው ራሱን ከሚያጣ ገንዘብን ቢያጣ ይሻለዋል ። ምክንያቱም ገንዘብ ሲያገኝ ራሱን የሚያጣ ከሆነ ፣ ገንዘብ መልሚያው ሳይሆን መጥፊያው ይሆናል ። ማግኘት ማንነትን ሊያጠነክር እንጅ ሊያፈርስ አይገባም ። ሰው በገንዘቡ የተሻለ ነገር ለመስራት ፣ ራሱን ላለማጣት በተጠንቀቅ መጠበቅ ይኖርበታል ። ገንዘብ ራስን ከሚያሳጡ ነገሮች ዋነኛው ነው ።

   ስልጣን ሲያገኙ ጨካኝ የሚሆኑ አሉ ። መራራት እስኪያቅታቸው ድረስ ራሳቸውን የሚያጡ አሉ ። ከስልጣን በፊት ሰው የነበሩ ፣ ስልጣን ሲሰጣቸው ወደ አውሬነት ይቀየራሉ ። ለሰው የሚራሩ ምርጥ የነበሩ ፣ በሰው የሚጨክኑ ምጥ ይሆናሉ ። በስልጣን ምክንያት ራሳቸውን ያጡ ፣ ብዙ የድርጅት የማህበረሰብ የሀይማኖት እና የሀገር መሪዎች አሉ ። የነበራቸውን መልካም ነገር አጥተው ፣ ያልነበራቸውን ክፉ ነገር የታጠቁ ብዙ ናቸው ። በስብእናቸው ይመሩናል ተብለው ተመርጠው ፣ በስልጣን ምክንያት ስብእናቸውን በማጣት ፣በትክክል የመሩን ሳይሆን በትግል የመረሩን ብዙ ናቸው ። በስልጣናችሁ ክቡር ፣ በመሪነታችሁ ምስጉን ለመሆን ፣ ስልጣን ስታገኙ ራሳችሁን ላለማጣት መጠንቀቅ አለባችሁ ። ያልነበራችሁን እውቀትና ልምድ የምታገኙበት እንጅ ፣ የነበራችሁን መልካም ስብእና የምታጡበት መሆን የለበትም ።

   እውቀት ሲያገኙ ራሳቸውን በደምብ ማወቅ ሲገባቸው ፣ በተቃራኒው ራሳቸውን የሚያጡ ብዙ ናቸው ። መሃይምነት ከምሁርነት ይሻላል የሚያስብሉ ፣ እውቀት ሲያገኙ ራሳቸውን ያጡ ምሁራን ብዙ ናቸው ። እውቀት ሰይጣን ያደረጋቸው ብዙ አዋቂዎች አሉ ። ለሰው በእውቀታቸው መድሃኒት ሳይሆን ፣ መርዝ እስከ መስራት የደረሱ ብዙ ናቸው ። መፍትሄ ሳይሆን ችግር የፈበረኩ ብዙ ናቸው ። አዋቂነት አውሬነት የሆነባቸው ተማራማሪዎች ቁጥራቸው ቀላል አይደለም ። በእውቀታቸው ዓለምን የጦርነት ማእከል ያደረጉ ፣ የፖለቲካውን አለም የሴራ ማምረቻ እንዲሆን የቀረጹ ፣ ትምህርት ቤቶችን የዝሙት ማስፋፊያ ያደረጉ ብዙ ናቸው ። እውቀት ሰውን ወደ ሰውነት እንጅ ወደ ሰይጣንነት ሊወስደው አይገባም ። ወደ ራሱ ሊመልሰው እንጅ ራሱን ሊያሳጣው አይገባም ። ለዚህ ደግሞ እውቀትን መምረጥ ተገቢ ነው ። ፈጣሪ የፈቀደውን መልካሙን ሁሉ ማወቅ ፣ ክፉውን መተው አስፈላጊ ነው ።

      ‘’ ለማግኘት ራስን ማጣት ልክ አይደለም ። ከክፉ ነገር ራስን መጠበቅ ፣ ማጣት ሳይሆን ራስን ማግኘት ነው ። ‘’    

Friday, June 6, 2025

እይታ | Perception

                                        ራስን ይቅር አለማለት

 

  ራስን ይቅር አለማለት የከባድ ጸጸት ውጤት ነው ። በነገራችን ላይ ለሰው ይቅርታ ከማድረግ በላይ ፣ ለራስ ይቅርታ ማድረግ ከባድ ነው ። ምክንያቱም እዚህ ጋር ጥፋት የራስ ነው ። በደል ማድረስ ህመምን ከባድ ያደርገዋል ። የሰው ልጅ ህሊናውን አሽከር ካላደረገ በስተቀር ፣ ጥፋት በመስራቱ የሚደርስበት ህመም ቀላል እይደለም ። አብዝተው ለሰው የሚጨነቁ ሰዎች ፣ ጥፋት ከሰሩ ለራሳቸው ይቅርታ ለማድረግ በጣም ይቸገራሉ ። በተለይ ሰው በእነርሱ ምክንያት ብዙ ከተጎዳ ፣ የሚደርስባቸውን የህሊና ስቃይ መሸከም ይከብዳቸዋል ። ለሰው የሚጨነቁ ሰዎች ፣ ለሰው የሚሳሱ ሲበዛ ስስ ፍጥረቶች ናቸው ። ሰው ተቸግሮ እያዩ ማለፍ አይችሉም ። ምናልባት ገንዘብ እያዩ ጥለው ሊያልፉ ይችላሉ ። ምክንያቱም እነርሱ ለሰው እንጅ ለገንዘብ አይሳሱም ። ገንዘብን እያዩ ማለፍ ካልፈለጉም ፣ ለራሳቸው ብለው ሳይሆን መርዳት የሚፈልጉት ሰው ስላለ ይሆናል ።

   ለሰው የሚጨነቁ ሰዎች ፣ ሰው እንዳይጎዳባቸው በጣም ጥንቃቄ ያደርጋሉ ። ጥንቃቄያቸው ከፍቅር ይመነጫል ። በእርግጥ አንዳንድ ሰዎች አሉ ፣ ሰው እንዳይታመም የሚጨነቁት ፣ ለሰውየው ሳስተው ሳይሆን ፣ ስራቸው እንዳይታጎል ወይም የሚያገኙትን እንዳያጡ ነው ። እነዚህ ግን ትላንት ላወቁትም ፣ እድሜ ልክ ለሚያውቁትም ያላቸው ስሜት ተመሳሳይ ነው ።  ለስራቸው ወይም ለጥቅማቸው ሳይሆን ፣በቃ እንዲሁ ለሰው በጣም ይሳሳሉ ። ለእነርሱ ማንም ይጎዳ ፣ ሰው እስከሆነ ድረስ ይጨነቃሉ ። የተቸገረ ሰው ሲያዩ ሀዘናቸው ጥልቅ ነው ።

  በእነርሱ ምክንያት ሰው ችግር ላይ ወድቆ ቢያዩ ፣ ሀዘናቸው እጅግ ከባድ ነው የሚሆነው ። በጸጸት ምክንያት ለራሳቸው ይቅርታ ለማድረግ አቅም ያጣሉ ። ይቅርታ መጠየቅ አይከብዳቸውም ነገር ግን ራሳቸውን ይቅር ለማለት ፣ ከባድ ፈተና ይሆንባቸዋል ። ልባቸው ስስ ስለሆነ ይቅርታ ማድረግ ለእነርሱ በጣም ቀላል ነው ። ሰው ሆኖ ጥፋት የማይሰራ ፣ ስህተት የማይፈጽም የለም ። የእነርሱን ህሊና አንቆ የሚይዘው ግን ፣ ጥፋቱ የሚፈጥረው ጉዳት ነው ። ለዚህ ደግሞ የሰዎችን ጉዳት ለመቀነስ ፣ በቻሉት መጠን ስህተት ላለመስራት ጥረት ያደርጋሉ ። ከሰሩም ይቅርታቸው በቃል ብቻ የሚወሰን ሳይሆን ፣ በተለያየ ነገር ሰውን ለመካስ ይሞክራሉ ። አልያ በቃል ይቅርታ በመጠየቅ ብቻ ህሊናቸው እረፍት አያገኝም ። በጸጸት ምክንያት ራሳቸውን ሊጎዱ ይችላሉ ።

   ለራስ ይቅርታ ማድረግ ሰውነትን መቀበል ድክመትን ማመን ነው ። ይቅርታ ለማድረግ መቸገር ግን ፍጹም ለመሆን መታገል ነው ። ሰው ደግሞ በስራው ፍጹም ሊሆን አይችልም ። ሆን ብሎ ስህተትን መስራት ተንኮል ነው ። ሰውን ለመጉዳት አስበው አቅደው ጥፋት ወይም ስህተት የሚሰሩ አሉ ። ይህ ሰውነት ሳይሆን አውሬነት ነው ። ሰው ሆኖ አለመሳሳት አይቻልም ። ሆን ብሎ ስህተት መስራት ግን ሰው መሆን አይደለም ። ስምንተኛ ክፍል የስፖርት መምህራችን ‘’ Mistake is humanity, again mistake is stupidity ( ስህተት መስራት ሰብዓዊነት ነው ስህተትን መድገም ግን ደደብነት ነው ። ) ‘’ ይል ነበር ። ነገር ግን ማወቅ ያለብን ፣ አውቀንም ሆነ ሳናውቅ ስህተት መስራታችን ፣ ራስን ይቅር ከማለት ሊከለክል አይገባም ።

ሰው ስህተትን የማይደግመው ለራሱ ይቅርታ ማድረግ ሲችል ነው ። አልያ ስህተትን በሌላ ስህተት እየቀየረ ይኖራል ። ጥፋትን በሌላ ጥፋት እየተካ ይቀጥላል ። ለራሱ ይቅርታ ማድረግ ካቃተው ፣ ላለመሳሳት ከመጠን በላይ ይጨነቃል ። ላለመሳሳት ሲጨነቅ የበለጠ ስህተት ይሰራል ። በጸጸት ብዛት ስህተትን ማስቆም አይቻልም ። ጥፋትን መግታት አይታሰብም ። ስህተትን ማመን ፣ ለጥፋት ሀላፊነት መውሰድ ፣ ድክመትን መቀበል ነው ፣ ስህተትንም ጥፋትንም ባለበት የሚያስቆመው ።

   ይቅርታ እረፍት ነው ። መንፈስን የሚያድስ ሀይል ነው ። ያልታደሰ መንፈስ ደካማ ነው ። ስለዚህ ስህተትን ለመደጋገም ቅርብ ነው ። መንፈስ ሲታደስ ብርቱ ይሆናል ። ሰው ውስጡ ሲታደስ ስህተትን ላለመድገም አቅም ያገኛል ። ሰው የሚታደሰው በይቅርታ ስለሆነ ፣ ለራስም ለሌላውም ይቅርታ ማድረግ ወሳኝ ነው ። ሰዎች ልክ እንደተፈጥሮ ሀብት ( Natural resource ) በሁለት ይከፈላሉ ። ታዳሽ እና ታዳሽ ያልሆኑ በመባል ። የይቅርታ ሰዎች ታዳሽ ናቸው ። የበቀል ሰዎች ደግሞ ታዳሽ ያልሆኑ ፍጥረቶች ናቸው ። ታዳሽ የተፈጥሮ ሀብቶች ዘላለማዊ እንደሆኑ ሁሉ ፣ የይቅርታ ሰዎችም ዘላለማዊ ናቸው ። ታዳሽ ያልሆኑ የተፈጥሮ ሀብቶች ጊዜያዊ ( limited ) ናቸው ። በተመሳሳይ ታዳሽ ያልሆኑ የበቀል ሰዎች ጊዜያዊ ናቸው ። የይቅርታ ሰዎች ህይወትን የሚቀጥሉ ሀይሎች ናቸው ። የበቀል ሰዎች ደግሞ ወይ ህይወትን የሚጨርሱ አልያም ለራሳቸው የሚያልቁ ሀይሎች ናቸው ። ህይወትን የሚቀጥሉ በሰው ልብ ውስጥ ለዘላለም ይኖራሉ ። ህይወትን የሚያቃጥሉ ከሰው ልብ በቀላሉ ይሰረዛሉ ። ስለዚህ ህይወትን ለመቀጠል የይቅርታ ሰው እንሁን ።

   ከልብ ለመሆን ለራስ ይቅርታ ማድረግ ተገቢ ነው ። ለመበርታት ለመታደስ ይህ ግድ ነው ። በጸጸት ብዛት መኖር ራስን ማቃጠል ነው ። ዘላለማዊ ሳይሆን ጊዜያዊ መሆን ነው ። ይህ ደግሞ ራስን በራስ መግደል ነው ። ስህተት ሰውኛ መሆኑን አምነን ፣ ለራስ ይቅርታ በማድረግ አዲስ ሰው እንሁን ። ለምድር ታዳሽ ሀይል ፣ ለሰዎችም ለራሳችንም ህይወትን ቀጣይ እንሆን ዘንድ ፣ ለራስም ለሌላም ይቅርታ ማድረግን እንለማመድ ። የቱንም ያህል ስህተት ብንሰራም ፣ ለራስ ይቅርታ የማድረግ ሞራል ልናጣ አይገባም ።

    ‘’ ስህተትን ላለመድገም ለራስ ይቅርታ ማድረግ ቁልፍ ነው ። ‘’            

Saturday, May 31, 2025

እይታ | Perception

                                              ፍትህ

  ፍትህ የስራ ውጤት ነው ። ሰው የስራውን ካላገኘ ፍትህ የለም ማለት ነው ። ፍትህ ካለ ጥሩ የሰራ ይሸለማል ። መጥፎ የሰራ ደግሞ ይቀጣል ። በተቃራኒው ፍትህ ከሌለ ፣ መጥፎ የሰራ አይቀጣም ። ጥሩ የሰራ አይሸለምም ። አለመሸለም ብቻ አይደለም ፣ ጥሩ በመስራቱ ሊቀጣ ይችላል ። ፍትህ ከሌለ የዘሩትን ማጨድ አይቻልም ። መታጨድ እንጅ ማጨድ አይኖርም ። መልካም የሰሩ የዘሩትን ማጨድ ባይችሉም ፣ ክፉዎች ግን ያልዘሩትን ያጭዳሉ ። ያላበሰሉትን ይበላሉ ። ያልሰጡትን ይወስዳሉ ። ያልተንከባከቡትን ፍሬ ይመገባሉ ። ፍትህ በሌለበት ትጋት ከንቱ ነው ። ምክንያቱም ሰርቶ መከበር አይቻልም ። ሰርቆ መከበር ነው የሚቻለው ። ጥሮ ማሳካት እጅግ ከባድ ነው ። አጭበርብሮ ማሳካት ግን ቀላል ነው ። ያለፍትህ ስራ ዋጋው ዝቅ ይላል ። ሴራ ግን ዋጋው ከፍ ይላል ።

ለስራ የሚተጉ ፍትህ ያሰፍናሉ ። ለሴራ የሚተጉ ደግሞ ፍትህ ያዛባሉ ። ለመስራት የሚተጉ ፍትህን ያረጋግጣሉ ። ለመስረቅ የሚተጉ ፍትህን ይረግጣሉ ። መስረቅም መስራትም ትጋት ይፈልጋሉ ። ልዩነቱ መስረቅ በአጭር ጊዜ ውስጥ ብዙ ገንዘብ ያስገኛል ። የደስታ ሰገነት ላይ ያስቀምጣል ። ግን ደግሞ የሀዘን አዘቅት ውስጥ መክተቱ ኣይቀርም ። ስራ በአንድ ጊዜ ብዙ ገንዘብ አያስገኝም ። ደስታውንም በመጠኑ ፣ ገንዘቡንም በልኩ እያሳደገ ነው የሚሄደው ። ሰው በመስረቁ የሰውን ደስታ ይቀማል ። ለዚያ ነው ደስታው ከልክ በላይ የሚሆነው ። የሚገርመው ሀዘኑም ከልክ በላይ መራር ነው ። ምክንያቱም የሚሸከመው ሀዘን የራሱን ብቻ ሳይሆን ፣ የሰውንም ጭምር ነው ።

ሰው በመስራቱ ግን ሀዘኑም ደስታውም በልኩ ነው ። ምክንያቱም የሚቀማው ደስታ የለም ። የሚሸከመውም ተጨማሪ ህዘን የለም ። እርሱ ፍትሐዊ ነው ።

ለመስራት እንጅ ለመስረቅ ፣ ለማስደሰት እንጅ ለማሳዘን ፣ ፍትህን ለማረጋገጥ እንጅ ለማዛባት አትትጉ ። ትጋት ደስ የሚለው ከቅንነት ጋር ነው ። ቅንቅንነት አይመቸውም ። ስኬት የትጋት ውጤት ነው ። ሰው ለፍትህ ከተጋ ፣ ስኬት የሀቀኞች ትሆናለች ። ፍትህን ለማዛባት ከተጋ ግን ፣ ስኬት የአጭበርባሪዎች ትሆናለች ። ፍትህ አለ ማለት የተጉ ስኬትን ይጎናጸፋሉ ፣ የአጭበረበሩ ይቀጣሉ ፣ የማይለፉ ሰነፎች ደግሞ ከሁለቱ ይማራሉ ። ፍትህ ከሌለ ስኬትም ቅጣትም የለም ። ስኬት ከሌለ አርአያ አይኖርም ። ቅጣት ከሌለ መማርያ አይኖርም ። ንቁ ሰው ከአርአያው ይማራል ። ያልነቃው በቅጣት ይማራል ። ፍትህ አለ ማለት በሁለቱም መንገድ መማር አለ ማለት ነው ። ከሌለ ግን መማረር እንጅ መማር አይቻልም ።

ፍትህ ለእውነት መቆም ነው ። በፍትህ ዘንድ ወገንተኝነት አይሰራም ። ጥፋተኛ ዘመድ ስለሆነ ከፍርድ አያመልጥም ። ሌባ ልጅ ስለሆነ ከቅጣት አይድንም ። ወንጀለኛ ወዳጅ ስለሆነ ከእስር አይተርፍም ። ፍትህ ስጋ ብሎ አያዳላም ። ለወዳጅ ብሎ ፍርደ ገምድል አይሆንም ። ለልጅ ብሎ እውነትን አይገፋም ። ለፍትህ መኖር ማለት ለእውነት እየቆሙ ፣ መከራን እየታገሱ መኖር ነው ። እውነት የለም ማለት ፍትህ የለም ማለት ነው ። ለፍትህ የእውነት መኖር ግድ ነው ። እውነት እና ፍትህ የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታ ናቸው ።

ለዚህ ነው ለመርማሪ እውነቱን ማወቅ ከባድ ፈተና የሚሆንበት ። የፍትህ መሰረቱ እውነት ስለሆነ ፣ ፍትህን የሚረግጡ እውነት እንዳትታወቅ ፣ ባለ በሌለ አቅማቸው ይታገላሉ ። ፍትህን ለማስፈን የሚተጉ ፣ እውነቱን ለማግኘት ከባድ ትግል ውስጥ ይገባሉ ። ‘’ እውነት እና ንጋት እያደር ይጠራል ። ‘’ እንዲባል ፣ እውነቱ ግን መታወቁ አይቀርም ። ፍትህን የነበሩት ቢያጡት ፣ የሚመጡት ማግኘታቸው አይቀርም ።

‘’ ለፍትህ እውነት እርቃኑን መሆን አልበት ። ‘’ አለች ፣ የስራና ክህሎት ሚኒስትር ወ/ሮ ሞፈሪያት ካሚል ። እውነትነት አለው ። ብዙውን ጊዜ እውነት ፣ ወይ ፍቅርን አሊያም ጥላቻን መልበሱ አይቀርም ። ጥላቻን ከሚለብስ ፍቅርን ቢለብስ የተሻለ ነው ። እውነት ጥላቻን ከለበሰ ጉዳቱ የከፋ ይሆናል ። በጥላቻ የሚነገር እውነት ፣ ሰው ውስጥ ሀይለኛ ቁጣን ይቀሰቅሳል ። ፍትህን ለማስፈን ከመጣር ይልቅ ለበቀል ያነሳሳል ። ፍትህ አላማው ማስተማር እና መካስ ነው ። በቀል ክፋትን በክፋት መመለስ ነው ። የፍትህ መጨረሻው ሰላም እና እርቅ ነው ። የበቀል መጨረሻው ግን መጨራረስ ነው ። እውነትን ጥላቻ ማልበስ ፣ ነገርን ወደ በቀል መውሰድ ነው ። ስለዚህ ከቻልን እውነትን ፍቅርን እናልብስ ። ካልሆነ እርቃኑን ይሁን ።

ለሰው ልጅ የሚሻለው ግን ፣ ያለምንም ጥርጥር እውነትን ፍቅርን ማልበስ ነው ። ያኔ ፍትህ ይረጋገጣል ፣ እንደ ሀብት ከትውልድ ትውልድ ፣ ሲሸጋገር የሚመጣን በቀል ማስቆም ይቻላል ። Genetic code ( የዘረ መል ውርስ ) እስኪመስል ፣ በቀልን በደም የሚዋረስ ህብረተሰብ አለ ። በቀል ለትውልድ የሚያወርሱት ሀብት ሳይሆን እርግማን ነው ።

 ምንም ጥቅም የሌለው ርካሽ ተግባር ነው ። የፈሰሰን ውሀ ለማፈስ መታገል ነው ። ይሄ ደግሞ የራስን ውድ አላማ መዘንጋት ነው ። ህልምን ቀብሮ ራእይን አፈር ድሜ ማብላት ነው ። በትላንት ታሪክ ዛሬን ለመኖር መታገል ነው ። ትላንት ለዛሬ ግብዓት እንጅ ግብ አይደለም ። በቀለኞች ግን ለዛሬ ወይም ለነገ የሚሆን ግብ የላቸውም ። የእነርሱ ግባቸውም ህልማቸውም ትላንት ነው ። የወላጅ ክፉ ሀሳብ ማስፈጸም ነው ራእያቸው ። ይሄ ሁሉ የሚሆነው እውነት ጥላቻን ሲለብስ ነው ። እውነት ፍቅርን ሲለብስ ግን በተቃራኒ ነው የሚሆነው ። ወደ ይቅርታ ይመራል ። ሰው የወላጁን ሳይሆን የራሱን ህልም እንዲኖር ይረደዋል ። የራሱ ግብ እንዲኖረው አስተሳሰቡን ይቀይረዋል ። ዛሬና ነገን በአግባቡ እንዲጠቀም ያግዘዋል ። በቀለኛ ሳይሆን ፍትሀዊ እንዲሆን ያስገድደዋል ። ከምንም በላይ ጎጅውን ጥላቻ ሳይሆን ፣ ጠቃሚውን ፍቅር እንዲያስቀድም ያደርገዋል ። ፍትህ የሚረጋገጠው በፍቅር እንጅ በጥላቻ አይደለም ። በቀል ፍትህ አይሆንም ። ፍትህ ይቅርታ ማድረግ ማስተማር መቅጣት እና መካስ ነው ።  

 

 ‘’ እውነትን ፍቅር አልብሱት ፣ ያኔ ፍትህ ይረጋገጣል ። ‘’     

እይታ | Perception

                                                    ስሜታዊነት እና እምነት     እምነት በስሜት አይገነባም ። እምነት ሲሞቀን የምንገነባው ፣ ሲበርደን ደግሞ የምናፈርሰው ወረት አይደለም ። ...