የማያዛልቅ ነገር
የማያዛልቅ ነገር ጊዜያዊ ነው ። መጨረሻ የሌለው ቅጽበታዊ ነገር ነው ። አለ ሲባል የሚጠፋ ፣ ጠፋ ሲባል የሚኖር አወዛጋቢ ነገር ነው ። የማያዛልቅ ነገር ስሜትን የመናጥ አቅም አለው ። ስሜትን ሰቅዞ በመያዝ ሰውን በቀላሉ ምርኮ ማድረግ ይችላል ። በቶሎ የሚለመድ ግን በቀላሉ የማይላቀቅ መንቻካ ነው ። አያዛልቅም ግን ደግሞ አይላቀቅም ። የማያዛልቅ ነገር ክብርን ፍቅርን ስሜትን ስልጣንን ጊዜያዊ ነው የሚያደርገው ። የማያዛልቅ ነገር መርህ አይመቸውም ። መርህ ደግሞ ለማያዛልቅ ነገር ቦታ የለውም ። መርህ የማይለዋወጥ ወጥ ነገር ነው ። የማያዛልቅ ነገር ግን ጋጠወጥ ነው ። በመርህ መኖር ፣ በህግና በስርዓት መኖር ነው ። ለማያዛልቅ ነገር መገዛት ፣ ህገወጥ እና ስርዓት አልበኛ ያደርጋል ።
መርህም ሆነ ስርዓት በሂደት ነው የሚገነቡት ። በአንድ ጀምበር የማይለመዱ ፣ ውድ ነገሮች ( quality ) ናቸው ። ወድ ስለሆኑ ሰውንም ውድ ክብሩንም ዘላለማዊ ማድረግ ይችላሉ ። ቅጽበታዊ ነገር ርካሽ ነው ። ለቅጽበታዊ ነገር መገዛት ርካሽነት ነው ። ጥራት የጎደለው እቃ ርካሽ እንደሚሆነው ፣ ለማያዛልቅ ነገር የሚገዛ ሰው ርካሽ ነው የሚሆነው ። ወርቅ መሆን የሚችለው መዳብ ይሆናል ። ሸክላ መሆን የነበረበት ገል ይሆናል ። ሊቅ መሆን የነበረበት ደቂቅ ይሆናል ። ምሁር መሆን የሚችለው መሀይም ይሆናል ። ባለጸጋ መሆን የሚችለው ደሀ ይሆናል ። ክቡር መሆን የሚችለው ወራዳ ይሆናል ። ምክንያቱም መርህ አልባ ሰዎች ጎደሎ ናቸው ።
ለማያዛልቅ ነገር መገዛት በጉድለት ውስጥ መኖር ነው ። እየጎደሉ ሙሉ መሆን አይቻልም ። እያነሱ መብዛት አይኖርም ። እየገደሉ ማዳን የማይታሰብ ነው ። በመርህ መኖር የጎደለን እየሞሉ መሄድ ነው ። በሂደት መልካም ነገርን ማሳደግ ፣ ክብርንም መጨመር ነው ። በመርህ ውስጥ የጎደለ ይሞላል ፣ ያነሰ ይበዛል ፣ የተዋረደ ከፍ ይላል ፣ የተበላሸ ሁሉ ይስተካከላል ። ለጊዜያዊ ነገር መገዛት ግን መስተካከል የሌለው መበላሸት ነው ፣ መመለስ የሌለው መውጣት ነው ፣ መዳን የሌለው መታመም ነው ፣ መነሳት የሌለው መውድቅ ነው ። በመርህ መኖር መጀመሪያ ያማል ፣ መጨረሻው ግን ያምራል ። ጊዜያዊ ነገር መጀመሪያ ያምራል ፣ መጨረሻ ለይ ግን ያማል ። ሰው ደግሞ መጀመሪያው አማረም አላመረም ችግር የለውም ። መጨረሻው ሲያምር ነው ደስ የሚለው ። ተከብሮ ከመዋረድ ፣ ተዋርዶ መከበር ይሻላል ። ይህ የሚሆነው በመርህ መኖር ሲቻል ነው ።
ዓላማ እና የማያዛልቅ ነገር አይዋደዱም ፣ ሆድና ጀርባ ናቸው ። የማያዛልቅ ነገር ለዓላማ እንቅፋት ነው ። ዓላማ ደግሞ ለጊዜያዊ ነገር አለርጂ ነው ። በዓላማ መኖር ሩቅ አስቦ ሩቅ ለማደር መታገል ነው ። ለማያዛልቅ ነገር መገዛት ቅርብ አስቦ ቅርብ ማደር ነው ። ዓላማ የማይታየውን ማሳየት ይችላል ። በዓላማ መኖር ከሚታየው በላይ ለማይታየው ነገር ዋጋ መስጠት ነው ። በማያዛልቅ ነገር መሸነፍ ለማይታየው ሳይሆን ለሚታየው ነገር ዋጋ መስጠት ነው ። ለሚታይ ነገር መገዛት እንጭጭነት ነው ። ለማይታይ ነገር መገዛት ግን ብስለት ነው ። ሰው እምነተ ጠንካራ የሚሆነው ፣ እምነቱን በሚያየው ነገር ላይ ሲመስርት ሳይሆን ፣ በማይታይ ነገር ላይ ሲመሰርት ነው ። እምነተ ደካሞች በሚታይ ነገር ያምናሉ ። እምነተ ጠንካሮች በሚታይም በማይታይም ነገር ያምናሉ ። ተጠራጣሪዎች በሚታየውም በማይታየውም ቶሎ አያምኑም ።
በጊዜያዊ ነገር ማመን ፣ እምነተ ደካማ መሆን ነው ። የዓላማ ሰዎች ግን እምነተ ጠንካሮች ናቸው ። ለዓላማ መኖር ከቅርቡ ይልቅ የሩቁን መመልከት ነው ። ለማያዛልቅ ነገር እጅ መስጠት የሩቁን ሳይሆን የቅርቡን ማየት ነው ። የቅርቡን ማየት ሙሉ በሙሉ ስህተት ነው ማለት አይደለም ። የቅርብ ነገሮች ዋጋ የሚኖራቸው ፣ ለሩቁ ነገር ግብዓት ሲሆኑ ነው ። ሩቅ ላለ ነገር ግብዓት መሆን ያልቻለ ቅርብ ነገር ፣ ዋጋ ያሳጣል እንጅ ዋጋ አያሰጥም ። ዋጋው ይወርዳል እንጅ ከፍ አይልም ። ወርቅ የሚሆነው መዳብ ይሆናል ። አልማዝ የሚሆነው ተራ የመንደር ድንጋይ ይሆናል ። የሩቁን ነገር አጥርቶ መመልከት ፣ የቅርቡን ነገር በአግባቡ ለመጠቀም ይረዳል ። በአላማ ስንኖር እጃችን ላይ ያለውን ነገር ትክክለኛ ዋጋ እናውቃለን ። የማያዛልቅ ነገር ዓላማን የሚጋርድ ጥቁር መጋረጃ ነው ።
የማያዛልቅ ነገር ደማቅ ነው ፣ አይነ ግቡ ነው ። ከፍተኛ የስበት ሀይል ( gravitational force ) አለው ። የማያዛልቅ ነገርን መከላከል እንጅ መጋፈጥ ብዙ አያዋጣም ። '' ታሞ ከመማቀቅ አስቀድሞ መጠንቀቅ '' እንደሚባለው ፣ ለጊዜያዊ ነገር ቅድመ ጥንቃቄ ነው የሚያስፈልገው ። ለምሳሌ ጫትን ብንወስድ ለብዙ ወጣቶች ደምቆ ነው የሚታየው ፣ በጣም ያስጎመጃል ነገር ግን እድሜን ይፈጃል ። ጫት ለጊዜያዊ ደስታ እንጅ ለዘላቂ ደስታ ምንም አስተዋጸኦ የለውም ። መጀመሪያ ያደምቃል መጨረሻ ላይ ግን ያደቃል ። ጅማሬው ደስታ ነው ፣ ፍጻሜው ግን ሀዘን ነው ። ሱሰኛ ነገን ዛሬ አይኖርም ። ነገን ዛሬ ይገድላል ። በዛሬ ውስጥ የሞተ ነገ ደግሞ እድሜን በእጥፉ ነው የሚቀንሰው ። የማያዛልቅ ነገር እድሜ ማባከኛ እንጅ ፣ እድሜ ማራዘሚያ ወይም መጠቀሚያ ሊሆን አይችልም ። የማያዛልቅ ነገርን የሙጥኝ ማለት መጨረሻው ብክነት ነው ።
የማያዛልቅ ነገር ቅድሚያ የሚሰጠው ነገር አይደለም ። ነገር ግን ስሜት ለማያዛልቅ ነገር ቅድሚያ በመስጠት የተካነ ነው ። ሰው ደግሞ ከምንም በላይ ለስሜቱ ተገዥ ነው ። ስሜቱን መቆጣጠር የቻለ ሰው ፣ ለማያዛልቅ ነገር ፊት አይሰጥም ። ስሜታቸውን መግዛት የተሳናቸው ሰዎች ግን ፣ ፊታቸውን ብቻ አይደለም ልባቸውን ጭምር ነው ለማያዛልቅ ነገር አሳልፈው የሚሰጡት ። ሰው ልቡ ለጊዜያዊ ነገር ሲገዛ ፣ ማክበር ያለበትን ይንቃል ፣ መያዝ ያለበትን ይለቃል ። መገንባት ያለበትን ያፈርሳል ። ማንሳት ያለበትን ነገር ይጥላል ። መተው ያለበትን ነገር የሙጥኝ ይላል ። የሚጎዳውን እየተከተለ ፣ የሚጠቅመውን እየሸሸ ይኖራል ። ጥሩ ነገር የሚያመው ፣ መጥፎ ነገር የሚያስደስተው ብላሽ ይሆናል ። ለማያዛልቅ ነገር ፊት መስጠት መጨረሻው መበላሸት ነው ።
የማያዛልቅ ነገር ከጤና ይልቅ በሽታ ነው ። ክብር ሳይሆን ውርደት ነው ። ነጻነት ሳይሆን ባርነት ነው ። ሱስ ህመም ነው ፣ ሀሜት ውርደት ነው ፣ ሌብነት ባርነት ነው ። አለው አለው ባይነት መጨረሻው ባዶነት ነው ። ስርዓት ማጣት ፍጻሜው ሰውነትን ማጣት ነው ። መዝናናት ማብዛት መጨረሻው መጉላላት ነው ። ፊልም ሲበዛ ህይወትን ቅዠት ያደርጋል ። አሉባልታ ሲበዛ ህይወትን ጣዕም አልባ ያደርጋል ። በጠቅላላው ለማያዛልቅ ነገር መገዛት ፣ የህይወትን ጉዞ የከፍታ ሳይሆን የቁልቁለት ነው የሚያደርገው ። ለሁሉ ነገር ትክክለኛ ዋጋ እንዲኖረን የህይወት ዓላማ ይኑረን ። በመርህ እንኑር ። ያኔ መዳቡ ወርቅ ይሆናል ። ተራ ድንጋይ የመሰለን የከበረ አልማዝ ይሆናል ።
'' የሁሉም ነገር ዋጋ ያለው አላማ ውስጥ ነው ። አላማ ከሌለን አይደለም የሌላን ነገር ዋጋ ፣ የራሳችንን ዋጋ አናውቅም ። ''