Saturday, June 28, 2025

እይታ | Perception

                                                              ስንፍና

  ስንፍና እየቻሉ አለመስራት ነው ። የማይችሉትን አለመስራት ግን ስንፍና አይደለም ። ምክንያቱም የሰው ልጅ ሁሉን መስራት አይችልም ። ሁሉን ቻይ ፈጣሪ ብቻ ነው ። ደካማ ጎን የሌለው ፣ ጠንካራ ጎኑ ብቻ የሚነገርለት አካል ፈጣሪ ብቻ ነው ። የሰው ልጅ ግን ደካማ እና ጠንካራ ጎን አለው ። አንዱ ጠንካራ በሆነበት ሌላው ደካማ ሊሆን ይችላል ። ሌላው ጠንካራ በሆነበት አንደኛው ደግሞ ደካማ ነው ። በቃ ይህ የህይወት እውነታ ነው ። በአንድ ነገር ደካማ መሆን ግን ስንፍና አይደለም ። ስንፍና መስራት አለመቻል ብቻ ሳይሆን ፣ ምንም መስራት አለመቻል ነው ። መስራት እየቻሉ መለገም ፣ ማንበብ እየቻሉ ማሳበብ ፣ መድረስ እየቻሉ መቅረት ፣ መራመድ እየቻሉ መቆም ፣ መቆም እየቻሉ መቀመጥ ፣ መቀመጥ እየቻሉ መቆመጥ ነው ስንፍና ።

 ድክመት የተፈጥሮ ውጤት ነው ። ስንፍና ግን የምርጫ ውጤት ነው ። ሰው መርጦ ደካማ መሆን አይችልም ። መርጦ ግን ሰነፍ መሆን ይችላል ። ድክመትን ማሻሻል ይቻላል ፣ ማስወገድ ግን በፍጹም አይቻልም ። ስንፍናን ማስወገድ ግን ይቻላል ። ድክመትን ለማሻሻል ፈጣሪን መማጸን ግድ ነው ። ስንፍናን ለማስወገድ ግን ራስን ማሳመን በቂ ነው ። ድክመትን መቀበል እንጅ መቃወም አይቻልም ። ስንፍናን መቀበልም መቃወምም ይቻላል ። ጠንካራ ሰው ስንፍናን መቃወም የሚችል ነው ። በዚያው ልክ ድክመቱን አምኖ መቀበል የሚችል ነው ። ዳተኛ ሰው ግን ስንፍናን መቃወም አይችልም ። ድክመቱንም አምኖ መቀበል አይችልም ። ለሚያደርገው የስንፍና ድርጊት ሰበብ መፍጠር ነው የሚችለው ።

ለችግሩ መፍትሄ የማያጣ ሳይሆን ፣ ለስንፍናው ምክንያት የማያጣ ፍጥረት ነው ። ሰነፍ ማለት ደክሞ ሳይሆን አውቆ የተኛ ነው ። ’’ አውቆ የተኛን ቢቀሰቅሱት አይነቃም ። ‘’ ይል የለ ያገሬ ሰው ፣ ሰነፍ እንደዛ ነው ። እየቻለ የማያደርግ እያወቀ ዝም የሚል ነው ።

  ንግግር አለመቻል ስንፍና አይደለም ድክመት ነው ። መናገር እየቻሉ ዝም ማለት ነው ስንፍና ። በተፈጥሮ ንግግር ላይ ደካማ የሆነ ሰው ፣ በጥረት የንግግር ችሎታውን ማሻሻል ቢችልም ፣ በፍጹም አንደበተ ርቱዕ ሊሆን አይችልም ። አንደበተ ርቱዕ ካልሆንኩ ብሎ ከሚታገል ፣ ድክመቱን አምኖ ቢቀበል ይሻለዋል ። ‘’  Change the changeable, accept the unchangeable. ‘’ እንዳለው የህይወት ክህሎት አሰልጣኙ ፣ የሚለወጠውን መለወጥ ፣ የማይለወጠውን መቀበል የተሻለ ነው ። የሚችሉት ላይ አድምቶ መስራት ፣ የማይችሉትን ለሚችሉት አሳልፎ መስጠት ብልሀት ነው ። ሁሉን ካልቻልኩ ማለት ፣ ምንም አለመቻልን ነው የሚፈጥረው ። ምንም አለመሞከር ደግሞ ስንፍናን ነው የሚፈጥረው ። መሞከር ሁሉን ወደ መቻል ሳይሆን ወደ መቻል ነው የሚወስደን ። አለመሞከር ግን ወደ ምንም አልመቻል ነው የሚወስደን ። ስንሞክር የምንችለውን እናውቃለን ፣ የማንችለውን እንለያለን ። ያኔ ድክመትን ከስንፍና እናጠራለን ።

በሁሉም ነገር ላይ ጎበዝ መሆን አይቻልም ። በምንም ነገር ላይ ጎበዝ አለመሆን ግን እርሱ ስንፍና ነው ። ሰው ያለችሎታ አይፈጠርም ። ችሎታውን ማወቅ ግደታው ነው ። ምንም ችሎታ የሌለው ሰነፍ ነው ። ሁሉም ሰው የሚችለውን አለመቻልም ስንፍና ነው ።የሰው ልጅ ሁሉ መማር ማንበብ መጻፍ እንዲችል ተደርጎ ነው የተፈጠረው ። እኔ ትምህርት ንባብ ፅሁፍ አይሆነኝም ማለት ትልቅ ስንፍና ነው ። እኔ ስእል አይሆነኝም ማለት ይቻላል ። ምክንያቱም ስእል ልዩ ተሰጥኦ ይፈልጋል ። ለአንድነት የሚሰጥ ሳይሆን ለልዩነት የሚቸር ነው ። በደፈናው እኔ ትምህርት አይሆነኝም ማለት ግን ስንፍና ነው ።

   ችሎታ በሁለት ይከፈላል ። ለልዩነት የሚሰጥ እና ለአንድነት የሚሰጥ ችሎታ ነው ። ሁሉም ሰው የሚችለው ነገር የአንድነት ችሎታ ነው ። የተወሰኑ ሰዎች ሊያደርጉት የሚችሉት ነገር ግን ለልዩነት የተሰጠ ነው ። መናገር መቻል ለሁሉ የተሰጠ ነው ። አሳምሮ መናገር ግን በልዩነት የሚሰጥ ነው ። ቀላል ሂሳብን መስራት ሁሉም ሰው ይችለዋል ። ከባድ እና ውስብስብ ሂሳብን መስራት ግን ልዩ የተፈጥሮ ዝንባሌን ይጠይቃል ። መኪናን መንዳት ለሁሉም ሰው ይቻላል ። መኪናን መስራት ግን ሁሉም ሰው አይችለውም ። ስለዚህ የአንድነት ችሎታን ማጣት ስንፍና ነው ። የልዩነት ችሎታን ማጣት ግን ድክመት ነው ወይም ያለቦታ የመገኘት ውጤት ነው ። 

   ‘’ ለሚያምን ሁሉ ይቻለዋል ። ‘’ ይላል ታላቁ መጽሀፍ ። ለጣረ ሁሉ ይቻለዋል ግን አላለም ። ምክንያቱም ከጥረት እምነት ይበልጣል ። ሰው ሁሉን ማድረግ ባይችልም ፣ ሁሉን ማድረግ በሚችለው ፈጣሪ ፣ በእምነቱ ምንም ማድረግ ይችላል ። ይህ የሚሆነው ስለጣረ ስለለፋ ሳይሆን ስላመነ ነው ። እዚህ ጋር ከሰው ችሎታው በላይ እምነቱ በጣም ወሳኝ ነው ። ለዚህም ነው የእምነት ሰዎች ፣ የጥረት ሰዎች ብዙ የሚደክሙበትን ፣ በቀላሉ የሚያከናውኑት ።

 የሰው ልጅ ደካማ ጎኑ የሚሸፈነው በእምነት ነው ። ስንፍናው ግን በምንም አይሸፈንም ። ባይሆን በቅጣት ይወራረዳል ።

   አንዳንድ ነገሮችን ማድረግ አለመቻል ፣ ስንፍና ስላልሆነ ብዙ መጨነቅ ተገቢ አይደለም ። ሰው መጨነቅ ያለበት ማድረግ እየቻለ ባለማድረጉ ነው ። ምንም አለመጨነቅ ልክ አይደለም ለስንፍና ይዳርጋል ። በሁሉም ነገር መጨነቅም ልክ አይደለም ፣ ለአእምሮ ህመም ይዳርጋል ። ሰው የሚችለውን ለማድረግ በመጠኑ መጨነቅ አለበት ። የማይችለውን ለማድረግ ግን ማመን እንጅ መጨነቅ የለበትም ። የሚችለውን ለመስራት በመጨነቁ ስንፍናውን ያስወግዳል ። የማይችለውን ለማድረግ ማመኑ ፣ ድክመቱን አምኖ ለመቀበል ይረዳዋል ።

  ‘’ ስንፍና ልዩነትን መፍጠር አለመቻል ነው ። ድክመት ልዩነትን አምኖ መቀበል ነው ። ‘’                            

Monday, June 16, 2025

እይታ | Perception

                                                     

                              ራስን ማጣት

     

       ራስን ማጣት መልከ ብዙ ነው ። ሰው ራሱን የሚያጣበት ምክንያት ብዙ ነው ። ራስን ከሚያሳጡ ነገሮች መሀል አንዱ ስሜታዊነት ነው ። ስሜታዊነት ሰውን ሌላ ሰው የማድረግ አቅም አለው ። ሰው ሲቆጣ ሲያዝን ሲፈራ እና ሲደሰት ፣ ከነበረው ማንነቱ የተለየ ማንነትን ይላበሳል ። ለዚህ ነው ስሜታዊ የሆኑ ሰዎች ፣ ባህሪያቸው በቀላሉ የማይለይ ፣ ስብእናቸው ተለዋዋጭ እየሆነ የሚያስቸግረው ። ስሜታዊ ሰዎች ሲደሰቱ ሌላ ፣ ሲያዝኑ ሌላ ሰው ናቸው ። በቀላሉ ራሳቸውን ያጣሉ ። ሲጀመር ዋስትና ያለው ባህሪ ወይም ስብእና ስለማይኖራቸው ፣ እንደ እስስት በቀላሉ የመለዋወጥ ባህሪ ይኖራቸዋል ። ለእነርሱ ከባዱ ራስን ማጣት ሳይሆን ራስን ማግኘት ነው ። በስሜት ለመገንባት ብርቱ ናቸው ። የዚያኑ ያህል በንዴት ለማፍረስ ጎበዝ ናቸው ። ሆ ብሎ መስራት ወዲያው ደግሞ ሆ ብሎ ማበላሸት መለያ ባህሪያቸው ነው ። ባጭሩ በስሜታዊነት ራስን ማጣት እንጅ ራስን ማግኘት ፣ ወደ ራስ መመለስ አይኖርም ።

ሌላኛው ራስን የሚያሳጣ ነገር ዝለት ነው ። ዝለት ሲባል የመንፈስም የአካልም ነው ። በእርግጥ የአካል ዝለት ፣ ያን ያህል የባህሪ ወይም የስብእና መዛባትን አይፈጥርም ። የመንፈስ ዝለት ግን ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ፣ የባህሪ መረበሽን ፣ የስሜት መቃወስን ፣ የስብእና መዛባትን ያስከትላል ። ዝለት ቀላሉን ነገር ከባድ ያደርጋል ። ተግባቢ የነበረውን ነጭናጫ ያደርገዋል ። ትእግስተኛ የነበረውን ቁጡ ያደርገዋል ። ትሁት የነበረውን ትእቢተኛ ያደርገዋል ። ብርቱ የነበረውን ደካማ ያደርገዋል ።

 በዝለት ውስጥ ስራ በጥረት እንጅ በጥራት አይሰራም ።በዝለት ውስጥ ለመጣር የተወሰነ አቅም ይኖራል ፣ ለማጣራት ግን በቂ አይሆንም ። ምክንያቱም ዝለት አቅላችንን ያስተናል ፣ ራሳችንንም ያሳጣናል ። ዝለት የስራ መብዛት ውጤት ነው ። ከአቅም በታች መስራት ዘልዛላ ያደርጋል ። ከአቅም በላይ መስራት ደግሞ ለዝለት ይዳርጋል ። ስለዚህ ሰው ራሱን ላለማጣት አቅሙን ማወቅ አለበት ። በአቅሙ ልክ መስራት አለበት ።  

   ራሳቸውን የሚያጡ ሰዎች ብዙ ጊዜ ራሳቸውን የማያውቁ ሰዎች ናቸው ። ራስን ማወቅ የራስን አቅም ስሜት ድክመት ጥንካሬ እና ሀሳብ ወይም አላማ ማወቅ ነው ። እነዚህን የራሱ የሆኑትን ነገር ያላወቀ ሰው ፣ በስራ ቦታ ፣ በማህበራዊ ግንኙነት ውስጥ በቀላሉ ራሱን ያጣል ። ምክንያቱም ችግር ሲገጥመው የሚታገስለት አላማ የለውም ። ድክመቱን አውቆ ነገርን  በማሸሽ ወይም በመሸሽ ፣ ከራሱ አያርቅም ። ራሱን ለማሸነፍም ጠንካራ ጎኑ ምን እንደሆነ መለየት አይችልም ። በመጨረሻም ራሱን በማጣት ብዙ ነገሩን ያጣል ። በእርግጥ ራስን ከማጣት በላይ ከባድ ችግር የለም ። ሰው ያለውን ሁሉ ቢያጣ ችግር የለውም ። ከባድ ችግር የሚፈጠረው ግን ራሱን ያጣ እለት ነው ።       

   ራስን ማጣት የነበረንን መጥፎ ነገር ማጣት ሳይሆን ፣ ያለንን ጥሩ ነገር ማጣት ነው ። ሰው ያለውን መጥፎ ነገር ቢያጣማ መልካም ነው ። ያኔ ራሱን አጣ ሳይሆን ፣ ራሱን አገኘ ነው የሚባለው ። የነበረውን ቁጣ ትቶ ፣ ያልነበረውን ትእግስት ቢላበስ እሰየው ነው ። ትእቢቱን ረስቶ ትህትናን ከያዘ ፣ ይህ መልካም ነው ። ስስትን ትቶ ደግ መሆን ከጀመረ ፣ ያኔ ወደ ጥንተ ተፈጥሮው ፣ ወደ ሰውነቱ ተመለሰ ማለት ነው ። ራስን ማጣት መልካም ነገርን ማጣት ነው ። ትእግስትን ትህትናን እምነትን እውነትን ደግነትን ማጣት ነው ። ሰው እንደ ድሮ  አይደለህም ተለውጠሃል ፣ ወደራስህ ተመለስ የሚባለው ፣ የነበረውን መልካም ነገር ሲያጣ ነው ።

   አንዳንድ ሰው ገንዘብ ሲያገኝ ትህትናውን ያጣል ። በነገራችን ላይ ማግኘት የሚያስከትለው ማጣት በሽታ ነው ። ሰው ራሱን ከሚያጣ ገንዘብን ቢያጣ ይሻለዋል ። ምክንያቱም ገንዘብ ሲያገኝ ራሱን የሚያጣ ከሆነ ፣ ገንዘብ መልሚያው ሳይሆን መጥፊያው ይሆናል ። ማግኘት ማንነትን ሊያጠነክር እንጅ ሊያፈርስ አይገባም ። ሰው በገንዘቡ የተሻለ ነገር ለመስራት ፣ ራሱን ላለማጣት በተጠንቀቅ መጠበቅ ይኖርበታል ። ገንዘብ ራስን ከሚያሳጡ ነገሮች ዋነኛው ነው ።

   ስልጣን ሲያገኙ ጨካኝ የሚሆኑ አሉ ። መራራት እስኪያቅታቸው ድረስ ራሳቸውን የሚያጡ አሉ ። ከስልጣን በፊት ሰው የነበሩ ፣ ስልጣን ሲሰጣቸው ወደ አውሬነት ይቀየራሉ ። ለሰው የሚራሩ ምርጥ የነበሩ ፣ በሰው የሚጨክኑ ምጥ ይሆናሉ ። በስልጣን ምክንያት ራሳቸውን ያጡ ፣ ብዙ የድርጅት የማህበረሰብ የሀይማኖት እና የሀገር መሪዎች አሉ ። የነበራቸውን መልካም ነገር አጥተው ፣ ያልነበራቸውን ክፉ ነገር የታጠቁ ብዙ ናቸው ። በስብእናቸው ይመሩናል ተብለው ተመርጠው ፣ በስልጣን ምክንያት ስብእናቸውን በማጣት ፣በትክክል የመሩን ሳይሆን በትግል የመረሩን ብዙ ናቸው ። በስልጣናችሁ ክቡር ፣ በመሪነታችሁ ምስጉን ለመሆን ፣ ስልጣን ስታገኙ ራሳችሁን ላለማጣት መጠንቀቅ አለባችሁ ። ያልነበራችሁን እውቀትና ልምድ የምታገኙበት እንጅ ፣ የነበራችሁን መልካም ስብእና የምታጡበት መሆን የለበትም ።

   እውቀት ሲያገኙ ራሳቸውን በደምብ ማወቅ ሲገባቸው ፣ በተቃራኒው ራሳቸውን የሚያጡ ብዙ ናቸው ። መሃይምነት ከምሁርነት ይሻላል የሚያስብሉ ፣ እውቀት ሲያገኙ ራሳቸውን ያጡ ምሁራን ብዙ ናቸው ። እውቀት ሰይጣን ያደረጋቸው ብዙ አዋቂዎች አሉ ። ለሰው በእውቀታቸው መድሃኒት ሳይሆን ፣ መርዝ እስከ መስራት የደረሱ ብዙ ናቸው ። መፍትሄ ሳይሆን ችግር የፈበረኩ ብዙ ናቸው ። አዋቂነት አውሬነት የሆነባቸው ተማራማሪዎች ቁጥራቸው ቀላል አይደለም ። በእውቀታቸው ዓለምን የጦርነት ማእከል ያደረጉ ፣ የፖለቲካውን አለም የሴራ ማምረቻ እንዲሆን የቀረጹ ፣ ትምህርት ቤቶችን የዝሙት ማስፋፊያ ያደረጉ ብዙ ናቸው ። እውቀት ሰውን ወደ ሰውነት እንጅ ወደ ሰይጣንነት ሊወስደው አይገባም ። ወደ ራሱ ሊመልሰው እንጅ ራሱን ሊያሳጣው አይገባም ። ለዚህ ደግሞ እውቀትን መምረጥ ተገቢ ነው ። ፈጣሪ የፈቀደውን መልካሙን ሁሉ ማወቅ ፣ ክፉውን መተው አስፈላጊ ነው ።

      ‘’ ለማግኘት ራስን ማጣት ልክ አይደለም ። ከክፉ ነገር ራስን መጠበቅ ፣ ማጣት ሳይሆን ራስን ማግኘት ነው ። ‘’    

Friday, June 6, 2025

እይታ | Perception

                                                  ራስን ይቅር አለማለት

 

  ራስን ይቅር አለማለት የከባድ ጸጸት ውጤት ነው ። በነገራችን ላይ ለሰው ይቅርታ ከማድረግ በላይ ፣ ለራስ ይቅርታ ማድረግ ከባድ ነው ። ምክንያቱም እዚህ ጋር ጥፋት የራስ ነው ። በደል ማድረስ ህመምን ከባድ ያደርገዋል ። የሰው ልጅ ህሊናውን አሽከር ካላደረገ በስተቀር ፣ ጥፋት በመስራቱ የሚደርስበት ህመም ቀላል እይደለም ። አብዝተው ለሰው የሚጨነቁ ሰዎች ፣ ጥፋት ከሰሩ ለራሳቸው ይቅርታ ለማድረግ በጣም ይቸገራሉ ። በተለይ ሰው በእነርሱ ምክንያት ብዙ ከተጎዳ ፣ የሚደርስባቸውን የህሊና ስቃይ መሸከም ይከብዳቸዋል ። ለሰው የሚጨነቁ ሰዎች ፣ ለሰው የሚሳሱ ሲበዛ ስስ ፍጥረቶች ናቸው ። ሰው ተቸግሮ እያዩ ማለፍ አይችሉም ። ምናልባት ገንዘብ እያዩ ጥለው ሊያልፉ ይችላሉ ። ምክንያቱም እነርሱ ለሰው እንጅ ለገንዘብ አይሳሱም ። ገንዘብን እያዩ ማለፍ ካልፈለጉም ፣ ለራሳቸው ብለው ሳይሆን መርዳት የሚፈልጉት ሰው ስላለ ይሆናል ።

  ለሰው የሚጨነቁ ሰዎች ፣ ሰው እንዳይጎዳባቸው በጣም ጥንቃቄ ያደርጋሉ ። ጥንቃቄያቸው ከፍቅር ይመነጫል ። በእርግጥ አንዳንድ ሰዎች አሉ ፣ ሰው እንዳይታመም የሚጨነቁት ፣ ለሰውየው ሳስተው ሳይሆን ፣ ስራቸው እንዳይታጎል ወይም የሚያገኙትን እንዳያጡ ነው ። እነዚህ ግን ትላንት ላወቁትም ፣ እድሜ ልክ ለሚያውቁትም ያላቸው ስሜት ተመሳሳይ ነው ።  ለስራቸው ወይም ለጥቅማቸው ሳይሆን ፣በቃ እንዲሁ ለሰው በጣም ይሳሳሉ ። ለእነርሱ ማንም ይጎዳ ፣ ሰው እስከሆነ ድረስ ይጨነቃሉ ። የተቸገረ ሰው ሲያዩ ሀዘናቸው ጥልቅ ነው ።

በእነርሱ ምክንያት ሰው ችግር ላይ ወድቆ ቢያዩ ፣ ሀዘናቸው እጅግ ከባድ ነው የሚሆነው ። በጸጸት ምክንያት ለራሳቸው ይቅርታ ለማድረግ አቅም ያጣሉ ። ይቅርታ መጠየቅ አይከብዳቸውም ነገር ግን ራሳቸውን ይቅር ለማለት ፣ ከባድ ፈተና ይሆንባቸዋል ። ልባቸው ስስ ስለሆነ ይቅርታ ማድረግ ለእነርሱ በጣም ቀላል ነው ። ሰው ሆኖ ጥፋት የማይሰራ ፣ ስህተት የማይፈጽም የለም ። የእነርሱን ህሊና አንቆ የሚይዘው ግን ፣ ጥፋቱ የሚፈጥረው ጉዳት ነው ። ለዚህ ደግሞ የሰዎችን ጉዳት ለመቀነስ ፣ በቻሉት መጠን ስህተት ላለመስራት ጥረት ያደርጋሉ ። ከሰሩም ይቅርታቸው በቃል ብቻ የሚወሰን ሳይሆን ፣ በተለያየ ነገር ሰውን ለመካስ ይሞክራሉ ። አልያ በቃል ይቅርታ በመጠየቅ ብቻ ህሊናቸው እረፍት አያገኝም ። በጸጸት ምክንያት ራሳቸውን ሊጎዱ ይችላሉ ።

   ለራስ ይቅርታ ማድረግ ሰውነትን መቀበል ድክመትን ማመን ነው ። ይቅርታ ለማድረግ መቸገር ግን ፍጹም ለመሆን መታገል ነው ። ሰው ደግሞ በስራው ፍጹም ሊሆን አይችልም ። ሆን ብሎ ስህተትን መስራት ተንኮል ነው ። ሰውን ለመጉዳት አስበው አቅደው ጥፋት ወይም ስህተት የሚሰሩ አሉ ። ይህ ሰውነት ሳይሆን አውሬነት ነው ። ሰው ሆኖ አለመሳሳት አይቻልም ። ሆን ብሎ ስህተት መስራት ግን ሰው መሆን አይደለም ። ስምንተኛ ክፍል የስፖርት መምህራችን ‘’ Mistake is humanity, again mistake is stupidity ( ስህተት መስራት ሰብዓዊነት ነው ስህተትን መድገም ግን ደደብነት ነው ። ) ‘’ ይል ነበር ። ነገር ግን ማወቅ ያለብን ፣ አውቀንም ሆነ ሳናውቅ ስህተት መስራታችን ፣ ራስን ይቅር ከማለት ሊከለክል አይገባም ።

ሰው ስህተትን የማይደግመው ለራሱ ይቅርታ ማድረግ ሲችል ነው ። አልያ ስህተትን በሌላ ስህተት እየቀየረ ይኖራል ። ጥፋትን በሌላ ጥፋት እየተካ ይቀጥላል ። ለራሱ ይቅርታ ማድረግ ካቃተው ፣ ላለመሳሳት ከመጠን በላይ ይጨነቃል ። ላለመሳሳት ሲጨነቅ የበለጠ ስህተት ይሰራል ። በጸጸት ብዛት ስህተትን ማስቆም አይቻልም ። ጥፋትን መግታት አይታሰብም ። ስህተትን ማመን ፣ ለጥፋት ሀላፊነት መውሰድ ፣ ድክመትን መቀበል ነው ፣ ስህተትንም ጥፋትንም ባለበት የሚያስቆመው ።

   ይቅርታ እረፍት ነው ። መንፈስን የሚያድስ ሀይል ነው ። ያልታደሰ መንፈስ ደካማ ነው ። ስለዚህ ስህተትን ለመደጋገም ቅርብ ነው ። መንፈስ ሲታደስ ብርቱ ይሆናል ። ሰው ውስጡ ሲታደስ ስህተትን ላለመድገም አቅም ያገኛል ። ሰው የሚታደሰው በይቅርታ ስለሆነ ፣ ለራስም ለሌላውም ይቅርታ ማድረግ ወሳኝ ነው ። ሰዎች ልክ እንደተፈጥሮ ሀብት ( Natural resource ) በሁለት ይከፈላሉ ። ታዳሽ እና ታዳሽ ያልሆኑ በመባል ። የይቅርታ ሰዎች ታዳሽ ናቸው ። የበቀል ሰዎች ደግሞ ታዳሽ ያልሆኑ ፍጥረቶች ናቸው ። ታዳሽ የተፈጥሮ ሀብቶች ዘላለማዊ እንደሆኑ ሁሉ ፣ የይቅርታ ሰዎችም ዘላለማዊ ናቸው ። ታዳሽ ያልሆኑ የተፈጥሮ ሀብቶች ጊዜያዊ ( limited ) ናቸው ። በተመሳሳይ ታዳሽ ያልሆኑ የበቀል ሰዎች ጊዜያዊ ናቸው ። የይቅርታ ሰዎች ህይወትን የሚቀጥሉ ሀይሎች ናቸው ። የበቀል ሰዎች ደግሞ ወይ ህይወትን የሚጨርሱ አልያም ለራሳቸው የሚያልቁ ሀይሎች ናቸው ። ህይወትን የሚቀጥሉ በሰው ልብ ውስጥ ለዘላለም ይኖራሉ ። ህይወትን የሚያቃጥሉ ከሰው ልብ በቀላሉ ይሰረዛሉ ። ስለዚህ ህይወትን ለመቀጠል የይቅርታ ሰው እንሁን ።

   ከልብ ለመሆን ለራስ ይቅርታ ማድረግ ተገቢ ነው ። ለመበርታት ለመታደስ ይህ ግድ ነው ። በጸጸት ብዛት መኖር ራስን ማቃጠል ነው ። ዘላለማዊ ሳይሆን ጊዜያዊ መሆን ነው ። ይህ ደግሞ ራስን በራስ መግደል ነው ። ስህተት ሰውኛ መሆኑን አምነን ፣ ለራስ ይቅርታ በማድረግ አዲስ ሰው እንሁን ። ለምድር ታዳሽ ሀይል ፣ ለሰዎችም ለራሳችንም ህይወትን ቀጣይ እንሆን ዘንድ ፣ ለራስም ለሌላም ይቅርታ ማድረግን እንለማመድ ። የቱንም ያህል ስህተት ብንሰራም ፣ ለራስ ይቅርታ የማድረግ ሞራል ልናጣ አይገባም ።

    ‘’ ስህተትን ላለመድገም ለራስ ይቅርታ ማድረግ ቁልፍ ነው ። ‘’            

እይታ | Perception

                                                                ስንፍና   ስንፍና እየቻሉ አለመስራት ነው ። የማይችሉትን አለመስራት ግን ስንፍና አይደለም ። ምክንያቱም የሰው ልጅ ሁሉ...