ጭንቀትን መርሳት
ለሰው የጭንቀት ምክንያቱ ብዙ ነው ። መራብ መጠማት መክሰር ስራ ማጣት የኑሮ ውድነት ፣ ከሰው ጋር መቀያየም እና ሌሎች ብዙ ምክንያቶች ሊጠቀሱ ይችላሉ ። የጭንቀትን ምክንያቶች በጠቅላላው የተፈጥሮ
እና ሰው ሰራሽ ብለን ልንመድባቸው እንችላለን ። ውስጣዊ እና ውጫዊ ምክንያቶች ተብለው ሊፈረጁ ይችላሉ ። ሰው ራሱ ያመጣውን ጭንቀት ሲመልስም መመለስ ሲሳነውም
ይስተዋላል ። ተፈጥሮ የሚያመጣበትን ጭንቀት ግን ቀድሞ
ካልተከላከለ በስተቀር ፣ አንዴ ከሆነ አምኖ መቀበል እንጅ መልሶ መቀልበስ ፈጽሞ አይችልም ። ለምሳሌ የአየር ንብረትን አዛብቶ ዶፍ ዝናብ እንዳይዘንብ ፣ የጎርፍ አደጋ እንዳይከሰት ማድረግ አይችልም ። ከሂማሊያ ተራራ በረዶ እንዳይቀልጥ መመከት አይችልም ። ደሃው ህዝብ በድርቅ እንዳይጎዳ መከላከል ከባድ ይሆንበታል ። ይህንን መቀበል እንጅ መቀልበስ አይችልም ። መከላከል ግን ይችላል ። በምን ? ከተባለ ተፈጥሮን በመንከባከብ እና በመጠበቅ ። አልያ ምድር በጸሃይ መጋል ብቻ ሳይሆን ፣ በካንሰር ህመምተኛ ትሞላለች ። ይህ በሽታ ደግሞ ፍቱን መፍትሔ ያልተገኘለት የበሽታዎች ሁሉ በኩር ነውና ፣ ለእርሱ እጅ መስጠት እንጅ መታገል እና መጋፈጥ ትርፉ ከንቱ ድካም ነው ። ሲቀጥል ሞትን በቀጠሮ መጠበቅ ግድ ይሆናል ።
ሞትን በቀጠሮ መጠበቅ ደግሞ ጭንቀትን እጅግ ከባድ ያገርገዋል ። ይህ በቀላሉ የሚረሳ ሳይሆን የማይረሳ ጭንቀት ነው ።
ይህን መርሳት ማለት ለመማር ዝግጁ አለመሆን ነው ። አለመማር ደግሞ መቅለል የሚችለውን ችግር ይበልጥ ከባድ ያደርገዋል ። በየጊዜው ለአንድ ችግር ተመሳሳይ መልስ እንድንሰጥ ያስገድደናል ። አንድ ሰው ለቀድሞ ችግሩ መልስ መስጠት ከከበደው ፣ ከችግሩ ተምሮ ሳይሆን በችግሩ ተማሮ ነው ያለፈው ። መልስ መስጠት ከቀለለው ግን ፣ በችግሩ ተማሮ ሳይሆን ከችግሩ ተምሮ ነው ያለፈው ። ለዚህ ነው የተማሩ ሰዎች ምን ጊዜም ፣ ችግርን አክብደው ሳይሆን አቅልለው የሚመለከቱት ። ዩኒቨርስቲ ገብተው የተማሩ ሳይሆን ከህይወት የተማሩ ። ያልተማሩ ሰዎች ደግሞ ሁል ጊዜ ችግርን አቅልለው ሳይሆን አክብደው የሚመለከቱት ፣ ዩኒቨርስቲ ገብተው መማር
ስላልቻሉ ሳይሆን ፣ ከህይወት መማር ስላልቻሉ ነው ። ችግርን አቅልሎ ለመመልከት ከህይወት መማር ግድ ነው ።
ከህይወት ለመማር ጭንቀትን ሙሉ በሙሉ መርሳት ተገቢ አይደለም ። ምክንያቱም ችግር ጭንቀትን ይወልዳል ። ጭንቀት ሀሳብን ይወልዳል ። ሀሳብ ፣ ጥበብ እና እውቀትን ይወልዳል ። ጥበብ እና እውቀት ደግሞ ችግርን ወደ መፍትሔ ፣ ፈተናን ወደ እድል ይቀይራሉ ። ያኔ በመጀመሪያ የከበደው ችግር ዳግም ሲከሰት
ቀላል ይሆናል ። መቶ ኪሎ የነበረው ፣ አስር ኪሎ ይሆናል ማለት ነው ።
ግን ጭንቀት ሁሉ የመፍትሔ ሀሳብ ይወልዳል ማለት አይደለም ። ጭንቀት በመጠኑ ሲሆን እና ከመጠን በላይ ሲሆን ይለያያል።
ጭንቀት በመጠኑ ሲሆን የሚያሞቅ እሳት ነው ። ከመጠን በላይ ሲሆን የሚያነድ እሳት ነው ። ስለዚህ ጭንቀት በመጠኑ ሲሆን ነው የመፍትሔ ሀሳብ የሚወልደው ። አልያ የመፍትሔ ሀሳብ ሳይሆን የህመም ወይም የእብደት ሀሳብ ነው የሚወልደው ። አሙቆ የሚያነሳሳ ሳይሆን አግሎ የሚገድል ይሆናል ።
ጭንቀት አማራሪም አስተማሪም ገጽ አለው ። ከመፍትሔ ይልቅ ችግር ላይ ካተኮርን አማራሪ ገጹ ይበዛል ። ከችግሩ ይልቅ መፍትሔው ላይ ካተኮርን አስተማሪ ገጹ ይሰፋል ። ለዚህ ደግሞ የኛ እይታ ወሳኝ ነው ። ደራሲው እንዳለው ‘’ አረፍተ ነገር ሲነበብ ስርዓተ ነጥብ ይታያል እንጅ አይነበብም ። በተመሳሳይ በችግር ወይም በጭንቅ ጊዜ ፣ እንደ ስርዓተ ነጥቡ የሚታዩ እንጅ የማይነበቡ ነገሮች አሉ ። አረፍተ ነገር ስናነብ ፣ ነጠላ ሰረዝ እያልን ብናነብ ፣ በጀመሪያ ስሜት አይሰጥም ፣ ሲቀጥል አረፍተ ነገሩ ትርጉም
ያጣል። እንደዚሁም በችግር ወይም በጭንቅ ጊዜ ፣ የማይታዩ ድርጊቶች እና ክስተቶች ፣ የማይሰሙ ንግግሮች ቦታ ካገኙ ፣ ችግርን እድል አድርገው ሳይሆን በደል አድርገው ነው የሚያሳዩት ። ከዛ ህይወት ትርጉም አልባ ሆና ትሳላለች ። ስለዚህ በችግር ወይም በጭንቅ ጊዜ ፣ በንቀት የተሞሉ ድርጊቶች እና ክስተቶች ፣ አሉታዊ ንግግሮች ትኩረት እና ቦታ ሊሰጣቸው አይገባም ።
ነገር ግን ተስፋ የሚሰጡ ድርጊቶች እና ትእይንቶች ፣ እምነትን የሚያጠነክሩ አዎንታዊ ንግግሮች ትኩረት ሊሰጣቸው ይገባል ።
ምክንያቱም እነዚህ ነገሮች ፣ ችግርን በደል ሳይሆን እድል አድርገው ያሳዩናልና ። ስለዚህ እይታችንን እናስተካክል ከመጥፎው ይልቅ ጥሩውን፣ ከችግሩ ይልቅ መፍትሔውን ፣ ከፈተናው ይልቅ እድሉን በእምነት እና በተስፋ ለማየት እንጣር ። ያኔ የጭንቀት አማራሪ ገጹ ሳይሆን አስተማሪ ገጹ ጎልቶ ይታያል ። የእብደት ሀሳብ ሳይሆን የመፍትሔ ሀሳብ ይወለዳል ።
ጭንቀትን መርሳት ለዘላቂ ሰላም መፍትሔ አይሆንም ። ከችግር ወይም ከጭንቀት መማር ነው ዘላቂ ሰላም የሚያመጣው ። ጭንቀትን ለመርሳት የሚታገል ሰው ፣ ህይወቱን የሚጎዳ እርምጃ ይወስዳል ። ሲጨንቀው አልኮል ይታየዋል ። መርዝ መርዝ ይለዋል ። ተስፋ ቢስ ይሆናል ። ሞቱን ብቻ ይመኛል ። ለችግሩ ወይም ለጭንቀቱ ጊዜያዊ መፍትሔ እንጅ ዘላቂ መፍትሔ አይታየውም ።
ከጭንቀት ለመማር የሚጥር ሰው ግን ፣ ህይወቱን የሚጠቅም እርምጃ ነው የሚወስደው ። ፈጣሪውን ይማጸናል ። መልካም ሰዎችን እርዳታ ይጠይቃል ። መፍትሔ ፍለጋ መጽሐፍ ያገላብጣል ። ለጊዜ ጊዜ ሰጥቶ ይጠብቃል ። ትእግስትን መርሑ ያደርጋል ። በጽናትም በጥናትም ችግሩን ወይም ጭንቀቱን ይሻገራል ። ሁሌም ተስፋ ያደርጋል ። በእምነት መከራን ያልፋል ።
ስለዚህ ሰው ጭንቀቱን ለመርሳት ሳይሆን መታገል ያለበት ፣ ከችግር ወይም ከጭንቀት ለመማር ነው ጥረት ማድረግ ያለበት ። ከጭንቀት ለመማር ስንጥር ፣ የጭንቀት ማቅለያ ስልትን እናውቃለን ። ለአንድ ጊዜ ብቻ የሚያገለግል ሳይሆን ፣ ለህይወት ዘመን የሚያገለግል ስልት ይሆናል ። ጭንቀትን ለመርሳት ስንታገል ግን ራስን ማቅለያ ወይም ማጥፊያ ስልት ነው ፊታችን ላይ ድቅን የሚልብን ። ከጭንቀቱ የተማረ ኑሮው ይቀላል ። ጭንቀቱን ለመርሳት የታገለ ራሱ ይቀላል
። ከጭንቀት ከተማርን ጭንቀቱ ያልፋል ። ለሌላም ጊዜ ተሞኩሮ በመሆን ማለፊያ ይሆነናል ። ጭንቀትን ለመርሳት ከታገልን ግን ጭንቀቱ
ሳይሆን እኛ እናልፋለን።
‘’ ጭንቀትን ከመርሳት ከጭንቀት መማር የተሻለ ነው ። ‘’
ክፍል 1